164

43
ቅዳሜ ህዳር 24 2004.ቁጥር 164

Upload: befkadu-getachew

Post on 28-Oct-2015

138 views

Category:

Documents


11 download

DESCRIPTION

a monthly news paper by Temesgen Desalgn

TRANSCRIPT

Page 1: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

Page 2: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

የዴሞክራሲው ተግዳሮቶች ኃይለመስቀል በሸዋምየለህ

ከጥቂት ወራት በፊት በሞት የተለዩት ..የሲአይኤው ሰው.. የሚል ቅፅል የተሰጣቸው አሜሪካዊው ዲፕሎማት ፖል ሄንዝ በደርግ የውድቀት ዋዜማ አቅራቢያ አቶ መለስ ሀገራቸውን እንዲጎበኙ እና ከአሜሪካ የተለያዩ ዲፕሎማቶችና የተቋማት ተወካዮች ጋር እንዲወያዩ ሁኔታዎችን ካመቻቹት ሰዎች ቀዳሚው ናቸው፡፡ የሽምቅ ውጊያውን እያሸነፈ የመጣውን ፓርቲ እንዲሁም ኢትዮጵያ የምትባለውን ገናና እና ታሪካዊ ሀገር ለመምራት ጥቂት የቀራቸውን የ35 ዓመቱ ጎልማሳ ሰው የሚሉትን ለመስማት እና የድህረ-ደርግ ስርዓት ምን ዓይነት መልክ እንደሚኖረው ለመረዳት የሚጠቅም አንዳች ነገር ይነግሩናል በሚል ተስፋ የመለስን ዋሽንግተን መድረስ በርከት ያሉ ጋዜጠኞች እና ዲፕሎማቶች በጉጉት እየተጠባበቁ ነው፡፡ ፓል ሄንዝ “Ethiopia in the find years of Derg” በሚል ርዕስ በሁለት ቅፅ ካሳተሙት ስራቸው በአንደኛው እንደሚተርኩት አቶ መለስ ማርክሲስት አለመሆናቸውን ለመናገር ጊዜ አያጠፋም፡፡ በተማሪነት ዘመኑ ዋነኛ ማርክሲስት ነበርኩ፤ በትግሉ ዘመን እና ከዛ በተከተሉት ዓመታት እንደተረዳሁት ግን ማርክሲዝም ሌኒንዝም እንደ ኢትዮጵያ ብዙ የፖለቲካ ፍላጎቶች ባሉባት ሀገር ዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ ስርዓት መገንባት አይቻለውም፡፡ ስለዚህም ርዕዮት ዓለሙን ትቼዋለሁ.. ሲሉ መናገራቸውን ዲፕሎማቱ ፖል ሄንዝ ፅፈዋል፡፡ ይህ ከፍተኛ የርዕዮተ-ዓለም ሽግግር ከደርግ ውድቀት በኋላ ያላቸውን ሀገር መሰረታዊ በሆነ መንገድ እንደሚቀይራት አቶ መለስ አሜሪካውያኑን ለማሳመን ሞክረዋል፡፡ የመድብለ ፖለቲካ ስርዓት መጀመር፣ ነፃ ፕሬስ እና ሲቪል ማህበረሰብ እንዲመሰረቱ መፍቀድ፤ ሰላማዊ ሰልፎችን ጨምሮ የነፃ ገበያ ጅማሮ ከ1983ዓ.ም በኋላ በምትኖረው ኢትዮጵያ የሚደረጉ መሰረታዊ የፖለቲካ-ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች እንደሚሆኑ በተገኙባቸው የምዕራባውያኑ መድረኮች ሁሉ ተናገሩሩ፡፡

በ1993ዓ.ም ሁለተኛ አጋማሽ ላይ በዋናነት በህወሓት አመራሮች መሀከል በተደረገው የስልጣን ሽኩቻ አቶ መለስ የራሳቸውን እና የተቀናቃኛቸውን ቡድን ትንቅንቅ በቦና ፓርቲዝም ሀልዮት በኩል መታየት እንዳለበት ለማሳመን ስለሀልዮቱ የሚያትቱ ፅሁፎቻቸውን ወደ አደባባይ ሲያመጡ ..ትቼዋለሁ.. ስላሉት ማርክሲዝም ጥያቄዎችን የሚያስነሱ ነገሮች ተፈጠሩ፡፡ እንደ እርሳቸው ክርክር ሌላኛው ቡድን ማርክሲዝም-ሌኒንዝምን እንደ እርሳቸው አለመረዳቱ ..ፓርቲውን ለመበስበስ.. ዳርጎታል፡፡ አቶ መለስ ..እንደገና ስለቦናፓርቲዝም.. በሚለው ባለ128 ገፅ ፅሁፋቸው ከማርክስ 17፣ ከኢንግልስ 19፣ ከሌኒን 22 በተጨማሪ ከስታሊን አንድ በጠቅላላው 59 የማርክሲስት ጥቅሶችን ተጠቅመዋል፡፡ ..ቦናፓርቲዝም..ን ለምን እንደመረጡም ሲያስረዱ ..ለህዝብ ቢሆን ባልተጠቀምን ነበረ እኛ ግን ማርክሲስት ሌኒንስት ስለሆንን..... የሚል ምክንያት ሰጥተዋል፡፡ ይህንኑ ፅሁፋቸውንም የደመደሙት ..ድል ለማሌ/ማርክሲስት-ሌኒኒስት/ እና ለአብዮታዊ ዴሞክራሲ.. በሚል መፈክር ነበር፡፡

ወደ ..የተረጋጋ ዴሞክራሲ..?

ኢህአዴግ በ2002ቱ ምርጫ ምልዑ ሊባል የሚችል አሸናፊነትን ካገኘ በኋላ የሀገሪቱ የፖለቲካ ስርዓት መገለጫ ከመድብለ

ፓርቲነት ወደ አውራ ፓርቲነት መቀየሩን ራሱ በሚያወጣቸው ድርሳኖች እና በፓርቲው ልሂቃን በኩል በተደጋጋሚ ተነግሯል፡፡ አሁን ፓርቲው እንደ ደረሰበት ብቸኛ ገዢነት ሁሉ ሌሎችም የአህጉሪቱ ገዢ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ከዴሞክራሲያዊ ሀዲድ ውጪ በመሄድ ለመድረስ ሞክረዋል፡፡ ከደቡብ አፍሪካ እስከ ዙምባቤ፣ ከቦትስዋና እስከ ኡጋንዳ ያሉትን አውራ ፓርቲዎች ያጠኑ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁራን፤ በአውራ ፓርቲ የሚመራ የፖለቲካ ስርዓት የሚያመጣውን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ በተመለከተ ሁለት ክርክሮችን ያስነብባሉ፡፡

የመጀመሪያው ዕይታ በጠንካራ መሰረት ላይ የተገነባ የዴሞክራሲ ስርዓት ባለባቸው ሀገራት የአውራ ፓርቲነት ሁነት ሲከሰት በጎ ሀገራዊ ሁኔታዎች ይፈጠራሉ የሚለው ነው፡፡ “Laying a foundation for democracy or undermining it? Dominant parties in Africa’s Burgeoning Democracies” በሚል ርዕስ በአፍሪካ የተፈጠሩትን አውራ ፓርቲዎች ያጠኑት ስቴፈን ሊንዳበርግና ጆንታን ጆንስ እንደሚሉት የተረጋጋ የመንግስት እና የፖለቲካ ስርዓት፣ ዝቅተኛ የዋጋ ንረት እና የኢኮኖሚ እድገት በነዚህ ዓይነት ሀገራት ሊፈጠሩ የሚችሉ አዎንታዊ ክስተቶች ናቸው፡፡ እነ ስቴፈን በሌላኛው በኩል ያለውና ከቦትስዋና ውጪ ያሉትን የአፍሪካ ሀገራትን ይገልፃል የሚሉት ሁለተኛው ሙግት በአምባገነናዊ የፖለቲካ ስርዓት ውስጥ የአውራ ፓርቲዎች መከሰት ሀገራቱን ወደ ጥልቅ ሙስና፣ የኢኮኖሚ ድቀት እና በኒህ ሁኔታዎችን ጋር ተከትሎ ወደሚመጣ ሀገራዊ ውድቀት ይመራል የሚለው ነው፡፡ የመሪዎች ተጠያቂ አልባነት፣ አግላይ የፖለቲካ ስርዓትና ስራ-ዓጥነት ዋነኞቹ የአምባገነን አውራ ፓርቲዎች መለዮ እንደሆነ የሚናገሩት ሁለቱ መምህራን ..ስልጣን ያባልጋል ብዙ ስልጣን ደግሞ የበለጠ ያባልጋል.. የሚለው ተለምዷዊ ድረሳን የእነዚህን ሀገራት መንግስታት በሚገባ ይገልፃል ሲሉ በተጠቀሰው ፅሁፋቸው ይከራከራሉ፡፡ አውራ ፓርቲው ኢህአዴግ በሀምሌ-ነሐሴ 2002ዓ.ም በታተመው ..የንድፈ-ሐሳብ.. መጽሔቱ አዲስ ራዕይ ቦትስዋናን እያሞካሹ ኢትዮጵያን የሚያወግዙት በሁለቱ አገሮች ያሉት ስርዓቶች የተለያዩ ስለሆኑ ሳይሆን ፓርቲው የሚከተለው የልማታዊነት ፖሊሲ ያልተዋጠላቸው ኒዮ-ሊበራሎች የሚያሰሙት ክስ እንደሆነ ቢከራከርም በዓለም አቀፍ ደረጃ ሀገራትን ከፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማህበራዊ እድገቶቻቸው አንፃር ደረጃዎችን የሚያወጣው ሊግተም /Legatum/ የተባለው ተቋም በዚሁ ዓመት ባወጣው የሀብት ደረጃ ፍረጃ (Legatum prosperity index) ኢትዮጵያን 108ኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧታል፡፡ ኢትዮጵያ በአለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ የስራ-አጥ ቁጥር ካላቸው ሀገራት በ6ተኛነት ስትመደብ፤ በአኗኗር ዘዴያቸው የሚረኩ ዜጎች ቁጥር እጅግ መመናመናቸውን በሚመሰክር መልኩ ሀገሪቱ ዘጠና አንደኛ ደረጃ ላይ ቆማለች፡፡ የፖለቲካ ስርዓቷንም በተመለከተ የተቋሙ ዘገባ ፀለምተኛ ነው፡፡ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች የተገደቡባት፣ የህግ-የበላይነት ያልተከበረባት፣ ዜጎቿ በሚሊተሪው እና በፍርድ ቤት ስርዓቱ

Page 3: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ላይ ያላቸው እምነት ዝቅተኛ መሆን በተጨማሪም 19ኀ የሚሆኑት ብቻ በሀገሪቱ ላይ በሚደረጉ ምርጫዎች በጎ እይታ ያላቸው መሆናቸው ተቋሙ በመልካም አስተዳደር መኖር ምደባ ኢትዮጵያን በ101ኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧታል፡፡

አንድ ብቸኛ ፓርቲ የፖለቲካ ምህዳሩን በሚቆጣጠርበት ወቅት መሰረታዊ የሆኑትን የዴሞክራሲያዊ ሂደቶችን እየጣሰ እንደሚመጣ እና ፣በምርጫ አልሸነፍም፣ ከሚል ማን አኽሎኝነት የተነሳ የፖለቲካ ስርዓቱ ወደ አምባገነናዊነት እንደሚቀየር የሚከራከሩት ሌላው የጉዳዩ ተንታኝ ሄዱ ብሩክስ፤ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ብዙ እና እጅግ የተለያዩ የፖለቲካ ማህበረሰቦች ባለባቸው ሀገራት አውራ ፓርቲዎቹ ራሳቸውን ሀገራቱን ለማረጋጋት በብቸኝነት እንደሚሰሩ ሀይሎች አድርገው ያቀርባሉ፡፡ ፀሐፊው “The dominant party system: challenges for South Africa’s democracy” በሚለው ፅሁፋቸው የፖለቲካ ፓርቲዎችን የስልጣን መቀያየር ግድ የሚለውን የዴሞክራሲ መርሆ አምባገነን ሲሉ የሰየሟቸው አውራ ፓርቲዎች የማዕከላዊውን መንግስት የትኞቹንም ተቋማት በመጠቀም ተቃዋሚዎችን በመደፍጠጥ ማህበረሰቡ ምንም አይነት አማራጭ ሀሳቦች የማይሰማበትን የፖለቲካ ስርዓት ያበጃሉ፡፡ በመንግስት ተቋማትና በፓርቲው መዋቅር መሀከል ይሄ ነው የሚባል ልዩነት ያለመኖሩ፤ አውራ ፓርቲዎቹ የህግ-አውጪ ውን የመንግስት ክፍል በመናድ፣ የስራ-አስፈፃሚውን የሀይል ማዕከል ያጠናክራሉ፡፡

ይህ የሄዱ ብሩክስ ትንታኔ ኢህአዴግን በሚገባ እንደሚገልፀው የሚሟገቱት የኢትዮጵያ የረዥም ጊዜ ወዳጅና አጥኚ አብፎም ..ተቃዋሚዎችን መታገስ በማይችሉት መሪ የሚመራ.. ብለው ፓርቲውን የሚጠሩት ፕ/ር ጆን አቢቢኒክ በኢትዮጵያ የተካሄዱት ሁሉም ምርጫዎች ..ለገዢው ፓርቲ ያደሉ የነበሩ.. ሲሆን፣ ፓርቲው ይሄን የምርጫ የበላይነት ለማግኘት ሲል ከፖሊስ እስከ ፍርድ ቤት ያሉትን ተቋማት ለመጠቀም እንደመረጠ “Political culture in Ethiopia: a balance sheet of post-1991 ethnic-federalism” በሚለው ፅሁፋቸው ጉዳዩን ለማስረገጥ ይሞክራሉ፡፡

የፖለቲካው ነባራዊ ሁኔታዎች በምሁራኑ እና በአንዳንድ ተቋማት ምልከታ እንዲህ አይነት ትችቶች ቢደርሱበትም ኢህአዴግ ከላይ በተጠቀሰው የንድፈ-ሀሳብ መጽሔቱ አሁን ያለው የፓርቲው የአውራ ፓርቲነት ጉዞ ..ተተካኪ ፓርቲዎችን.. ወደ ሚያስተናግደው እና ፓርቲው ..የላቀ የእድገት ደረጃ ላይ የሚገኝ.. ሲል ወደጠራው ..የተረጋጋ የዴሞክራሲ ስርዓት.. ሀገሪቷን ሊያደርሳት እንደሚችል ተከራክሯል፡፡ ከመለስ-ባርኔጣ ስር

ከነፃ-አውጪነት ወደ ገዢ አውራ ፓርቲነት ስለሚቀየሩት የፖለቲካ ፓርቲዎች ያጠኑ መምህራን አያይዘው የሚያነሱት ቀዳሚ

ጉዳይ ሁኔታው ግለሰብን ማዕከል ወደሚያደርግ የፖለቲካ ስርዓት የመቀየሩን ሁነት ነው፡፡ ጆ-አንሲያ ቫን ዌይክ የተባሉ ፀሐፊ ሁኔታውን ሲያብራሩ የሚጠቀሱት ሁሉም የሀገሪቱ የፖለቲካ ስልጣን በስራ-አስፈፃሚው የሚጠቀልልበትን አመክኖያዊ ትስስር ነው፡፡ እንዲህ አይነት ጡንቸኛ መሪዎች ስልጣናቸውን ራሳቸውን በሀብት ለማደለብ ስለሚጠቀሙበት፤ የሀይል ማዕከላቸውን ለማደላደል የከፋ እርምጃዎችን እንደሚወስዱ የሚተነትኑት ቫንዌይክ የአውራ ፓርቲዎቹ መሪዎች በተለምዷዊው የዴሞክራሲ የሀሳብ ማዕቀፎች ከስልጣናቸው የሚወርዱበት እድል እጅግ የሳሳ እንደሆነ “Political leaders in Africa: presidents, patrons or profiteers?” በሚለው ፅሁፋቸው ያቀረቡት እና በአቶ መለስ እና በኢህአዴግ የአራት ፓርቲዎች ጥምረትነት መሀከል ያለውን ተዛምዶ እንደሚያብራራ በተንታኞች የሚጠቀሰው የፀሐፊው ሀሳብ፣ እንደ ኢህአዴግ ያሉ ዘውግ ተኮር ፓርቲ ስብስቡ ወደ አውራ ፓርቲነት ራሳቸውን ሲያሻግሩ የፓርቲው መሪ ከስብሰባ መሀከል ብዙውን የማህበረሰብ ክፍል ከሚያካትተው ፓርቲ ከሆነ በቀላሉ በሌላ መሪ የመቀየር እድል ይኖረዋል የሚለው መላምት ነው፡፡ ፀሐፊው በዚህ መላምታቸው የሚያቀርቡት ሙግት መሪው ብዙውን ዘውግ (ብሄር) ማዕከል ካደረገው ፓርቲ የሚነሳ ከሆነ ሌሎቹ የፓርቲው አባላት ቁጥሩ የበዛ ብሄርን ማዕከል አድርገው የፖለቲካ ሀይላቸውን ስለሚደለድሉ፤ መሪው ቢቀያየርም የፖለቲካ ፍላጐቶቻቸው ተጠብቆ እንደሚቆይ ማመናቸው ዋነኛ ምክንያት ነው፡፡ ..ነገር ግን.. ይላሉ ፀሐፊው ..የአውራ ፓርቲው መሪ ቁጥሩ ካነሰ ብሄር እና ወታደራዊ ዳራ ያለው ከሆነ ስልጣኑን ለማስጠበቅ ተደጋጋሚ የአፈና እርምጃዎችን ይወስዳል፡፡.. በዚህ ትንታኔ መሰረት ከኢህአዴግ ግንባር ፓርቲዎች መሀከል የፓርቲው መሪ ከኦህዴድ የተነሳ ቢሆን የአቶ መለስን ያህል በብቸኝነት ለአስርት ዓመታት ሊመራ የሚችልበት እድል ላይኖር ይችል ነበር የሚለው ሀሳብ ጉዳዩን ለሚከታተሉ ፀሐፊዎች አንድ የመሟገቻ ሀሳብ የሚሆን ይመስላል፡፡

በ2002ቱ ምርጫ ማግስት አቶ መለስ የምርጫውን ውጤት በተመለከተ ይነሳ ለነበረው ትችት መልስ ይሆን ዘንድ፤በጊዜው ለተለያዩ ሚዲያዎች ከሰጧቸው ቃለ-መጠይቆች በተጨማሪ በእርሳቸው እንደተፃፈ በሚነገርለት ከላይ በተጠቀሰው የፓርቲው መፅሄት ውጤቱ እና እርሱን ተከትሎ የመጣው የኢህአዴግ የአውራ ፓርቲነት ጉዳይ ከአምባገነናዊነት ጋር ምንም ዝምድና እንደሌለው ለማስረዳት የጃፓንን እና የስዊድንን ተሞክሮ በመጥቀስ ትችቶቹን ለመግራት ሞክረዋል፡፡ የእርሳቸው ሙግት ..በጃፓን ሊበራል ዴሞክራቲክ ፓርቲ /ሏሓ/፣ በስዊድን ደግሞ ስዊድሽ ሶሻል ዴሞክራቴክ /SSDP/ ለብዙ አስርታት ብቸኞች ገዢ ፓርቲዎች መሆናቸው ኢ-ዴሞክራሲያዊ የማያደርጋቸው ከሆነ የኢህአዴግም አሸናፊነትና የብዙ ዓመታት መሪ ፓርቲነት እንግዳ አይደለም.. የሚል ነው፡፡ ይሄን የርሳቸውን ክርክር በጥልቀት ለማየት የሞከሩ ፀሐፊዎች የሰውየው ንፅፅር አመክኖያዊ መሆኑን ይጠረጠራሉ፡፡ ለኒህ ተንታኞች በመጀመሪያነት የሚጠቀሰው የንፅፅር መዛባት የሚገኘው ሶስቱ ሀገሮች..ኢትዮጵያ ስዊዲንና ጃፓን) ያሏቸውን ዴሞክራሲያዊ ተቋማት በማስተያየት የሚጠቀሰው ነው፡፡ በጃፓን እና በስዊድን የሚካሄዱት ምርጫዎች እንደ ኢትዮጵያ ምርጫ ስለፍትሓዊነቱና ዴሞክራሲያዊነቱ ከውጭም ሆነ ከውስጥ ክስ ሲቀርብበት አይስተዋልም፡፡ በሁለቱ ሀገራት ያሉ ተቃዋሚዎች ከገዢዎቹ ፓርቲዎች እኩል ሀሳቦቻቸውን የሚያስረዱባቸው ሚዲያዎች አሏቸው፡፡ በተጨማሪም ነፃ የፍትህ ስርዓት፣ በተሻለ ብቃት የሚንቀሳቀሱ ሲቪክ ማህበራት ነፃ የሚሊተሪ እና የፖሊሲ ተቋማት እና በማንኞቹም ተቋዋሚዎች ከማንም እንደማይወግን እምነት የሚጣልበት የምርጫ ቦርድ መኖሩን የሚጠቀሱት ብርቱካን ሀይሌ የተባሉ ፀሐፊ ይሄ የመጀመሪያው የክርክር መዛባት ነው፡፡

ሁለተኛውን የአቶ መለስን የተዛባ አመክንዮ ለማሳየት ፀሐፊዋ “The reformation of one-man dictatorship in Ethiopia” በሚለው ፅሁፋቸው የሚጠቅሱት በሶስቱ ሀገራት ያሉትን አውራ ፓርቲዎች የሚመሩትን መሪዎች መተካካት በማስተያየት ነው፡፡ የጃፓኑ ሊበራል ዴሞክራቲክ ፓርቲ ሀገሪቱን ለሀምሳ ዓመታት ቢመራም እጅግ ብዙ ጊዜ የፓርቲ መሪዎቹን ቀያይሯል፡፡ በጃፓን ያለው የጠቅላይ ሚኒስትሮች መቀያየር ከየትኞቹም ዴሞክራሲያዊ ሀገራት ቀዳሚው ነው፡፡ በፓርቲው የግማሽ ክፍለ-ዘመን ቆይታ ሃያ ዘጠኝ ጠ/ሚኒስተሮች ቦታውን ተቀያይረዋል፡፡ ይህ ማለት አንድ /ሚኒስትር በአማካይ ለሁለት አመታት ግድም ብቻ ፓርቲውን ለመምራት ተመርጧል፡፡ አቶ መለስ ስልጣን ላይ ከወጡ ከ1983ዓ.ም ያለውን ዘመን ብናይ ጃፓን አስራ አራት ጠ/ሚኒስትሮችን አስተናግዳለች፡፡ ሌላኛዋ ሀገር ስዊድን ባለፉት ሃያ ዓመታት አምስት ጠ/ሚኒስትሮችን አይታለች፡፡ የአቶ መለስን ክርክር እርሳቸው

Page 4: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ከጠቀሷቸው ሁለቱ ሀገራት አውጥተን ስርዓታቸው እያዘነበለባት እንደሆት የምትጠቅሰውን ቻይናን እንመልከት የሚሉት ተንታኞች አቶ መለስ ከፓርቲው መሪነት ሳይነቃነቁ፤ ቻይና ሶስት ፕሬዘዳንቶችን እና ሶስት ጠ/ሚኒስትሮችን መቀያየሯን በማንሳት አሁን በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የአንድ ፓርቲ አምባገነንነት ብቻ ሳይሆን የአንድ ሰው ብቸኛ መሪነትም ነው ሲሉ ይሟገታሉ፡፡

ከአውራ ፓርቲ ጋር...

የዴሞክራሲ ተቋማት ባልዳበሩበት እና አምባገነናዊ የፖለቲካ ባህል የተስፋፋበትን የፖለቲካ ስርዓት የሚመሩ አውራ ፓርቲዎች ወደ ምርጫ ሲገቡ አስልተው የሚነሱት ስልጣናቸውን ሊገዳደራቸው የሚችሉ ተቋዋሚ ፓርቲዎች አለመኖርን እና ፓርቲያቸው በርቀት ሊቆጣጠራቸው የሚችሉ ሳተላይት ፓርቲዎችን ከጎናቸው ማሰለፋቸውን እንደሆነ የሚናገሩት ፕ/ር ሜሪድዝ በርግ፤ በአፍሪካ ውስጥ የተከሰቱት ብዙዎቹ አውራ ፓርቲዎች የነፃ-አውጪ ነት ስያሜ ያላቸው መሆናቸው፣ ይህንን የነፃ-አውጪ ነት ተጋድሎ በፖለቲካው ማህበረሰብ ዘንድ ተቀባይነት ሊያስገኝላቸው በሚችልበት መንገድ የተለያዩ ሚዲያዎችን በመጠቀም አበክረው ይሰራሉ፡፡ ፕ/ር በርግ “From liberation movements to Ruling parties” በሚለው ጥናታዊ ስራቸው እንደሚሉት እነዚህ አውራ ፓርቲዎች የፖለቲካውን ምህዳር እጅግ ከማጥበባቸው በዘለለ፣ እነርሱ በፈቀዱት ልክ የሚንቀሳቀሱትን የፖለቲካ ፓርቲዎች እንኳን በመራጮች ሊያገኙ ይችላሉ ብለው የሚያስቧቸውን ድጋፎች ለመሸርሸር ተቋዋሚዎችን የሀገሪቱ ዋነኛ ጠላቶች አድርገው ሊስሏቸው ይሞክራሉ፡፡ በ1997ቱ ምርጫ ከኢህአዴግ በኩል የተሰማው የ..ኢንተርሀሞዌይ.. ክስ እና በአንድ ወቅት በአቶ መለስ ፅሁፍ ሌበራል ዴሞክራሲን እንከተላለን የሚሉትን ተቃዋሚዎችን ..ፊውዳሎችና የደርግ ርዝራዦች..፣ ..የውጭ እርዳታ ለመቀላወጥ ሲሉ.. እና ..የበከተ አድሀሪና የጠነባ አስተሳሰብ ያላቸው.. የሚሉት ትህትና አልባ ስያሜዎች በዚህ የፕ/ሩ ትንታኔ በኩል ሊታይ ይችላል፡፡ አውራ ፓርቲዎች ተቋዋሚዎች ላይ የሚያደርሷቸው ውንጀላዎች በውጤቱ መራጮችን አቅም አልባ (De-legitmate) ያደርጋቸዋል፡፡ ..በውጤቱም.. ይላል ስቴፈን ፍሬድማን የተባለ ፀሐፊ ..የፖለቲካ ማህበራሰቡ ለተቃዋሚዎች የሚኖረው ምልከታ አውራ ፓርቲዎች ተቋዋሚዎችን በተመለከተ እንዲኖር ከሚፈልጉት አተረጓጎም ጋር ይዛመዳል፡፡ ..ፓርቲዎቹ ሀገራቱን የብዙሃን ሚዲያዎች እንዳሻቸው ለመጠቀም የመቻላቸው ሁነት ይህንን ሊያደርጉ የሚችሉበትን ሁኔታ በቀላሉ ይፈጥርላቸዋል፡፡ ራሳቸውን በዚህ ሁኔታ ውስጥ እንዲያገኙ የተገደዱ የስርዓቱ ተቀናቃኞችም በእያንዳንዱ ሀገራዊ ክስተት ላይ የሚኖራቸው አቋም በአውራ ፓርቲው የተመራ ሊሆን የሚችልበትን እድል ይፈጠራል፡፡.. ሬድማን “No easy strom to dominance” በሚለው መጣጥፉ እንደሚሟገተው በዚህ መልክ የሚብራራ የፖለቲካ ስርዓት አውራ ፓርቲዎቹ የሚያራምዱትን ርዕዮተ-ዓለም በመንተራስ ሲቪል ማህበረሰብ፣ ጠንካራ ተቃዋሚዎች እና ነፃ ፕሬስ የማይኖሩባቸውን ስርዓቶች ለመፍጠር ይተጋሉ፡፡ ከዚህ ትንታኔ ጋር በሚዛመድ መልኩ፡፡ አቶ መለስ ..መሰረታዊ ጥያቄዎች በኢትዮጵያ.. በሚለው የ1993ቱ ፅሁፋቸው አብዮታዊ ዴሞክራሲን የሀገሪቱ ብቸኛ ጠቅላይ ርዕዮተ-ዓለም መሆን እንዳለበት በርትተው ተከራክረዋል፡፡ ይህንን የበላይነትም ለማምጣት ፓርቲው ሁለት መንገዶችን እንደሚጠቀም ከፅሁፋቸው ለመረዳት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው የመንግስትን ተቋማት በመጠቀም የፓርቲውን አባላትን እና ዳኞችን ጨምሮ የተለያዩ ሲቪል ሰራተኞችን በርዕዮተ-ዓለሙ ማጥመቅ ነው፡፡ ይህ በተለያዩ ህዝባዊ መሰል ስብሰባዎች አማካኝነት የሚካሄደው የጠመቃ አካሄድ አባላቱን እና ሲቪል ሰራተኞቹን ሌሎች የማህበረ-ኢኮኖሚም ሆነ የፖለቲካ እሴቶችን እና ሀሳቦችን እንዳያውቁ ይጋርዳቸዋል፡፡ መጠየቅንና መፈተንን በሚያወግዘው ጥምቀት የሚያልፉት ተሳታፊዎች የፓርቲው የበላይ ልሂቃን ከሚነግሯቸው ውጪ የሚኖሩ ሙግቶችን የማያደምጡበት አውድ ይፈጠራል፡፡ ሌላው ከፍሬድማን ትንታኔ ጋር የሚስማማው የፓርቲው አካሄድ ስልጣኔን ይሸራርፋሉ ብሎ የሚያስባቸውን የማህበረሰብ ክፍሎች የተለያዩ የመንግስትን ተቋማት በመጠቀም ..መጨፍለቅ.. (በአቶ መለስ አነጋገር) ነው፡፡ ይህንንም ለመከወን ከ90/10ሩ የሲቪል ማህበረሰብ አዋጅ ጀምሮ እስከ ፀረ-ሽብርተኝነት ህጉ ድረስ ለመጠቀም መሞከሩን ማስተዋል ይቻላል፡፡

Page 5: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ዳገት ላይ ሰው ጠፋ ፕ/ር መስፍን ወልደማርያም

የአሜሪካ ብሔራዊ መዝሙር ውስጥ “ነፃ ሰዎች ምድር፣ የጀግኖች አገር” የሚል አለበት፤ በሰማሁት ወይም ባነበብሁት ቁጥር ልቤ ያብጣል፤ በአገሬ መኩራት ናፍቆኝ ነው እንጂ አሜሪካዊ የመሆን ምኞት አድሮብኝ አይደለም፤ ነገር ግን በአሜሪካኖች እቀናለሁ፤በሰማይ ላይ በሚበሩ ወፎችም እቀናለሁ፤ ሁለቱንም ልሆን አልችልም፤ ግራ ገባኝ የሚለውን ግጣሜን የደመደምሁት በሚቀጥሉት መስመሮች ነበር፤

ዓላማው ጠፋብኝ፤ፍጹም ግራ ገባኝ፤ መልአክነት ስሻ ሰው መሆን ከብዶብኝ..

እንኳን በኢትዮጵያዊነትና በሰውነትም ለመኩራት ከባድ እየሆነ ነው፤የቁልቁለት ኃይል የሚለውን ግጥሜን ደግሞ የዘጋሁት

በሚከተሉት መስመሮች ነው፡- ዳገት ላይ ሰው ጠፋ፤ አቀበት ከበደ፤ ሁሉም በሸርተቴ ቁለቁለት ወረደ፤ ሰው ተዋረደ፤ ገንዘብ ተወደደ፤ በምነቱ፣ ፍቅር፣ በክብሩ ነገደ፤ በቁልቁለት ኃይል እየተገደደ፡፡

አባቶቻችንና እናቶቻችን ክብራቸውን ከምንም ነገር በላይ አድርገው ይመለከቱት ነበር፤ ይህንንም ዓለም ሁሉ አውቆላቸው

ክብርንና አድናቆትን አትርፎላቸዋል፤በአንዳድ አገሮች ለኢትዮጵያውያን ቪዛ አያስፈልጋቸውም ነበር፤ዛሬ ኢትዮጵያዊነት ረክሶ ኢትዮጵያውያን ለስደት ሲጓዙ ጀልባ እየተገለበጠ በባሕር ይሰምጣሉ፤ መኪና እየተገለበጠ ይሞታሉ፤ወደ አረብ አገር እየተጓዙ ፍዳቸውን የሚበሉትን በሺህ የሚቆጠሩ ሴቶችን ሳናነሣ፤በዚህ ሁሉ የኢትዮጵያውያን አበሳ የሚነግዱና የሚጠቀሙ ወገኖች አሉ፡፡

ደሀነት እየቆጠቆጣቸው፣ ወይም የልጆቻቸውና የወላጆቻቸው ረሃብና ሰቀቀን እየበላቸው የሚሰደዱ ሴቶች አሉ፤

ጉልበታቸውን፣ አእምሮአቸውን፣ የፈጠራ ችሎታቸውን በሙሉ ኃይላቸው ሊጠቀሙበት ባለመቻላቸው እድላቸውን ለማቃናት ወይም የውስጣቸውን ጩኸት ለማስተጋባት የሚሰደዱ አሉ፤ በጣም የተማሩና የተራቀቁ ሰዎች በነፃነት ለመተንፈስ የማያስችለውን ዓየር እየሸሹ የሚሰደዱ አሉ፤ ነጋ ጠባ የአገዛዙ ሰላይ ሎሌዎች እየተከታተሉ መውጫ መግቢያ እያሳጡዋቸውና እያስፈራርዋቸው ተደናብረው የሚሰደዱ አሉ፤ ብዙ የመሰደጃ ምክንያቶች ይኖራሉ፤ ነገር ግን ደስታን በአገሩ ባያገኝም ደስታን በስደት ለማግኘት የሚሰደድ ኢትዮጵያዊ ያለ አይመስለኝም፡፡

ገና ወያኔ አዲስ አበባ እንደገባ በአገዛዙ ትእዛዝ አርባ ያህል የኃይለ ስላሴ ዩኒቨርስቲ መምህራን ችሎታ የላቸውም ተብለው

ተባርረው ነበር፤ እንዴት ያሉ ሰዎች እንደተኳቸው ተማሪዎቹ ይናገሩ፤ ላነሳው የፈለግሁት ነጥብ ግን ከነዚያ አርባ መምህራን ውስጥ ብዙዎቹ በህይወት አሉ፤ ከቀሩት ውስጥ ከአንድ ሰው በቀር ሁሉም በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጭ ከዱሮው በበለጠ ሁኔታ በተሻለ የኑሮ ደረጃ ላይ ናቸው፤ ችሎታቸውን የሚያውቅላቸው እያገኙ ተጠቅመው ይጠቅማሉ፤ እኔን በጣም የሚደንቀኝ ሌላ እውነት አለ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ በነበሩበት ጊዜ ቢጨምቋቸው ምንም የማይወጣቸው የሚመስሉ ሰዎች አሜሪካ ገብተው በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚያበረክቱት ጽሑፍ አንቱ የሚያሰኛቸው ነው፤ የአፈና አየር ስንቱን አደንዝዞታል.. ዱሮ፣ ዱሮ በምን ላይ እንዳነበብሁት ትዝ የማይለኝ የፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ግጥም በከፊል ትዝ ይለኛል፤

አንድ ነገር ሲያምር ያየሁት እንደሆን፣ ያንን ካላጠፋሁ ከቶ ምንም ቢሆን፣ እንቅልፍ አይወስደኝም... እያለ የሚቀጥል ነበር፤ ይህ ፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት በዘመናቸው ያስተዋሉት አጉል ጠባይ እያቆጠቆጠ ኖሮ እየተኮተኮተ አድጎ ኢትዮጵያውያንን እያቆረቆዘ ለምልሞአል፤

ህዳር 2/2004 አቤ ቶኪቻው አገር ጥሎ ሄደ የሚል ወሬ ሰማሁ፤ “አንድ ነገር ሲያምር ያየሁት እንደሆን”፤ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ጉዞ ወይ ወደማዕከላዊ እስር ቤት ወይ ወደስደት እየሆነ ነው፤ ሰው እንዳይበቅልባት የተረገመች ሀገር ይመስል አንድ ባለሙያ ሲያቆጠቁጥ ማየት ዓይናቸውን የሚፈጀው ሰዎች ያሉ ይመስላል፤ “አንድ ነገር ሲያምር ያየሁት እንደሆን”፤ ቀደም ሲል በማቆጥቆጥ ላይ የነበረችው ጎበዝ ፀሐፊ ርዕዮት ዓለሙም ቃሊቲ ከገባች ቆየች፤ አንድ ነገር ሲያምር ያየሁት እንደሆን..

Page 6: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ህዳር 12 ደግሞ የአውራምባ ጋዜጣ ባለቤት፣ በቅርቡ በዓለም ጋዜጠኞች ማህበር ሽልማት የተሰጠውና በ1998 ታስሮ ሁለት ዓመታት ያህል በእስር ቃሊቲ ቆይቶ በምህረት የተለቀቀው ዳዊት ከበደም የጥቃቱ እሳት ለበለበውና በቃኝ ብሎ ሄደ፤ “አንድ ነገር ሲያምር ያየሁት እንደሆን”፣ እነዚህ ጋዜጠኞች የአገሪቱን ስም ሊያስጠሩ የሚችሉ በኢትዮጵያ ውስጥ የአእምሮም የመንፈስም ችሎታ መኖሩን ሊያስመሰክሩ የሚችሉ ነበሩ፤ በቃሊቲ የተዘጋባት ርዕዮት ዓለሙም ስምዋ የሚጠራ ፀሐፊ ለመሆን እያቆጠቆጠች ነበር፤ “አንድ ነገር ሲያምር ያየሁት እንደሆን” ሆነና ቃሊቲ ተዘጋባት፤ እግዚአብሔር አእምሮዋን እንደከፈተው ያቆይላት እንጂ ችሎታዋ የሚታይበት ጊዜ ይመጣ ይሆናል፡፡

በማናቸውም የእውቀትና የሙያ መስክ አእምሮአቸውና ህሊናቸው የተሳለ ሰዎች ለሎሌነት አይመቹም፤ እነሱም ሎሌነት አይመቻቸውም፤ በዚህ ምክንያት ኢትዮጵያ በአንድ በኩል የሰው ደሀ እየሆነች ልጆችዋ የዓለምን አገሮች በር እያንኳኩ ስደተኞች ሆነው ደሀነትንና ስደትን የሚያጋቡ ይመስል ሁሉም ይጠላቸው ጀምሯል፡፡

አንድ አገር ዜጎቹ በደሀነትና በለማኝነት በችጋርና በስደት ሲታወቅ በነእዚህ ከችጋር በተረፉ ለማኞችና ስደተኞች ላይ የበላይነት እየተሰማው የሚኮራና አገሩን የሚያኮራ ሰው አለ? የአገር ውርደት ለማን የኩራት ምንጭ ይሆናል? የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ወደአሜሪካ ወይም ወደአውሮፓ (የተሙዋላ ነፃነት ባሉባቸው አገሮች) ሲሄድ የሚያጋጥመው ዜጎች ተሰብስበው እንኳን ደህና መጣህ የኛ መሪ የሚል ጭብጨባ አይደለም፤ ይህ አያሳፍርም? አያስቀናም? ሰዎችን አዋርዶ መከበር አይገኝም፤ ጠመንጃና ጉልበት የውስጡ እውነት እንዳይወጣ ያፍናል እንጂ እውነቱን አያጠፋውም፤ ዞሮ ዞሮ ሰዎችን ማዋረድ ራስን ማዋረድ ነው፤ የተዋረዱ ሰዎች በውስጣቸው የሌለውን ክብር ለሌላ ሊሰጡ አይችሉም፤ የተዋረደ ሰውስ አከበረ ወይ አላከበረ ምን ፋይዳ አለው? ፋይዳ ያለው የሚያከብሩት ሰው ሲያከብር ነው፡፡

የአገር ደህንነት ማለት ትርጉሙ ግራ እያጋባ ነው፤ እንደሚገባኝ የአገር ደህንነት ሁላችንንም የሚነካ በመሆኑ ፊታችንን የምናዞርበት ተግባር አይደለም፤ ለግዮን ሆቴል የቆየሁ ደንበኛ ነበርሁ፤ ቦምብ እስከፈነዳበት ድረስ፤ በዚያ ቦምብ ፍንዳታም ህይወታቸውን ያጡትን አውቃቸዋለሁ፤ የምንቀላለድ ነበርን፤ ዛሬም ግዮን ሆቴል ስሄድ የእነዚህ ሰዎች ፊት ይታየኛል፤ እንባዬ ይመጣብኛል፤ ቦምቡን አስቀምጦ የሄደውን ሰው ባወቀው ምን የማላደርገው አለ? ከግዮን ያስቀረኝ ኪሴ ብቻ ሳይሆን የአነዚያን ወዳጆች መልክ በሐዘን በማስታወስ ነው፤ በየሰው ቤትና በየቢሮ እየሄዱ ሰላማዊ ሰዎችን ማስፈራራት ሽብርተኛነት ነው ወይስ ደህንነት?

ከእንደዚህ ያለው በሆቴል ውስጥ ቦምብ የሚያፈነዳ አረመኔ ራሳችንን ለመጠበቅ በየሰው ቤት ወይም ቢሮ እየሄዱ ሰዎችን ማስፈራራት እንዴት ይበጃል? የሚያስፈራሩት ሰው ሽብርተኛ ከሆነ እንዳወቁበት መረጃ ሰጥተው ሊያስጠነቅቁት ነው? ካልሆነ በማስፈራራት ወደሽብርተኞች መንደር ሊገፋፉት ነው? በሃያ አንደኛው ምዕተ-ዓመት እነዚህ ሰዎችን እንዲህ የሚያደርጋቸው ሙስና ነው? አለማወቅ ነው? ግዴለሽነት ነው? መጽሐፍ ማንበብ ቢያቅታቸው ቪዲዮ እያዩ መማር ለምን ያቅታል? ያለማወቅ ምሽግ አንድ ብቻ ነው፤ አውቃለሁ እያሉ ባለማወቅ መታበይና ማበላሸት..

የአሜሪካ መንግስትና ኢትዮጵያ በሽብር ላይ ጦርነት አብረው የተሰለፉ ናቸው፤ ነገር ግን ስለሽብርተኛነት ያላቸው አመለካከት ግልጽ የሆነ ቅራኔ ውስጥ እየገባ ነው፤ ኢትዮጵያ ሽብርተኞች ከምትላቸው ውስጥ በአሜሪካ ተከብረውና ሙሉ ሰብዓዊ መብቶቻቸው ተጠብቀውላቸው የሚኖሩ ሰዎች አሉበት፡፡ የምዕራብ አውሮፓ መንግስታትም ቢሆኑ ኢትዮጵያ ሽብርተኞች የምትላቸውን ከእነ ሙሉ ሰብአዊ መብቶቻቸው ያኖሩአቸዋል፤ ይህ በአንድ በኩል ስናየው ነው፤ በሌላ በኩል ስናየው ደግሞ አሜሪካና አውሮፓ ሽብርተኞች የሚሉአቸው ሰዎች (የመብቱን ጉዳይ እንርሳውና) በኢትዮጵያ ውስጥ መኖር ይችላሉ ወይ? ካልቻሉ ለምን? ኢትዮጵያስ ሽብርተኞችዋን ከአሜሪካ እና ከአውሮፓ አስገደዳ የማታሰመጣበት ምክንያት ምንድን ነው? የኢትዮጵያ ሽብር ከዓለም-አቀፋዊው የሽብር ትርጉምና ከዓለም-አቀፋዊው የሽብር ሕግ የተለየ ነው ማለት ነው? ወይስ አሜሪካና አውሮፓ በአለም-አቀፋዊ የሽብር ህግ አይገዙም ማለት ነው? ወይስ ኢትዮጵያ በዓለም-አቀፋዊው ሕግ አትገዛም ማለት ነው? ስለሽብርተኛነት ዓለም-አቀፋዊ ሕግ የለም? በአንድ የአውሮፓ መንግስት በሽብርተኛነት የተፈረጀ ሰው አሜሪካ ሄዶ የሙጢኝ አይልም፤ ታዲያ በኢትዮጵያ በሽብርተኛነት የተፈረጀ ሰው አሜሪካ ሄዶ የሙጢኝ ሲል በሁለቱ አገሮች መሀከል ያለው ቅራኔ የአስተሳሰብ ነው? ወይስ የተግባር?

በአሜሪካ በሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ የጥናት ግብዣ በሄድሁ ጊዜ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሌላ ስራ ጠፍቶበት፣ የእኔን በዩኒቨርስቲው መጋበዝ ትልቅ የአገር ጉዳይ አድርጎ ለዩኒቨርስቲው የጻፈውን የተቃውሞ ደብዳቤ እየቀለዱበት አሳዩኝ፤ ምንም የኔ ጉዳይ ቢሆንም የአገሪቱ ባለስልጣኖች ሲሰደቡ ያሳፍረኛል፡፡ በስንት ነገር እየተዋረድን ገለባ እንሆናለን? በስንት ነገር እያፈርን አንገታችንን እንደፋለን? ፈርተን፣ አስፈራርተን፣ በወሬ እየተሸበርን ሽብርን እናስተምራለን? የአንዳንድ ባለስልጣኖች ንግግርም ሆነ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ሽብርን የሚያስተምሩ ይመስለኛል፤ አስቡ፤ አንድ ኢትዮጵያዊ ራሱን በእሳት ሲያቃጥል ለመጀመሪያ ጊዜ ይመስለኛል፤ ባለስልጣኖችና የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አስተማሪው ራሱን ማቃጠሉ የሽብር ጥንስስ ሊሆን እንደሚችል የተረዱት አይመስልም፤ እግዚአብሔር ልቡና ይስጣቸው!

Page 7: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

መምህር የኔ ሰው እውነተኛ አርበኛ ወይስ እብድ? ጥላሁን አክሊሉ በዓለም ታሪክ በፍትህ እጦት ራሳቸውን በራሳቸው በእሳት አቃለው ያጠፉ አያሌ ሰዎች ነበሩ፡፡ በደቡብ ኮሪያ የቀድሞ መሪ የአስተዳደር ዘመን በርካታ ኮሪያዊያን ተቃዋሚዎች በየጊዜው ከፖሊሶች ጋር ያደርጉ ከነበረው

ጠንከር ያለ ግጭት በተጨማሪ በተለያዩ ጊዜያት ኮሪያዊያን ወጣቶች አደባባይ በመውጣት ራሳቸውን አቃጥለው ይገድሉ ነበር፡፡ እንዲያውም 1970ዎቹ የደቡብ ኮሪያ ዋነኛ ዜና መንግስትን በመቃወም ራሳቸውን በእሳት ያቃጥሉ የነበሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ እንደ ደቡብ ኮሪያ ተደጋጋሚ ባይሆንም በቺሊ አምባገነን ጨፍጫፊ የነበሩት አውግስቶ ፒኖቼን የሚቃወሙ ወጣቶች በሳንቲያጐ ከተማ ራሳቸውን በራሳቸው አቃጥለዋል፡፡ በኢንዶኔዢያም በፖለቲካና በሃይማኖት ተፅዕኖ ምክንያት ብዙዎች ራሳቸውን አቃጥለዋል፡፡ የሶሻሊስት ስርዓት በዓለም ላይ ከመውደቁ በፊት ስርዓቱን ይከተሉ በነበሩ በአንዳንድ አገራትም ተመሳሳይ እርምጃዎች ተወስደዋል፡፡

የከፍተኛ ተቋም ምሩቅ የነበረው ሙሐመድ ቡአዚዝ፣ ስራ ባለማግኘቱ በመንገድ ላይ ይቸረቸር የነበረው ንብረቱ በፖሊሶች በመቀማቱ የደረሰበትን በደል ለበላይ አካል በተደጋጋሚ ቢያሰማም ምላሽ ባለማግኘቱ፣ በራሱ ላይ ቤንዚን አርከፍክፎ ራሱን አቃጥሎ መግደሉን ተከትሎ፣ በቱኒዚያ የፕሬዝዳንት ዜን ኤልአብዱን ቤን አሊ መንግስት ላይ ታላቅ ቁጣን አስከትሏል፡፡ ፕሬዚዳንት ቤን አሊም እንደሌሎቹ አምባገነን መሪዎች ህዝባዊ አመጹን በሃይል ለመጨፍለቅ ሳያስቡ ወይም እንደ ዴሞክራት መሪዎች ጥያቄያችሁ ምንድን ነው? ለማለት ጊዜ ሳይሰጡ፣ የአመጹ መነሳትና የእርሳቸው ሹልክ ብሎ አገር ጥሎ መጥፋት እኩል ሆነ፡፡ ሁሉም አምባገነን መሪዎች እንደ ቤን አሊ የተሻለ አምባገነን መሪዎች በሆኑ የሚያሰኝ ነው፡፡

በመሆኑም መሐመድ ቡአዚ ራሱን አቃጥሎ በመግደል የዓለምን ታሪክ የቀየረ ከመሆኑ ባሻገር የፖለቲካና የኢኮኖሚ ርዕዮቶችንም አተረማምሷል፡፡ የአረቡን አለም የአምባገነን መሪዎች ከስልጣን መውረድ እና በተለያዩ አገራት ህዝባዊ አመጾችን እየሰማን ባለበት በዚህ ጊዜ ከቱኒዚያዊው ወጣት ጋር በከፊል ሳይሆን ሙሉ በሙሉ የሚመሳሰል ድርጊት በአገራችን ሰማን፡፡

በደቡብ ክልል በዳውሮ ዋካ ዞን በመምህርነት ሙያ ተሰማርቶ ሲያገለግል የነበረው የኔሰው ገብሬ የተባለ ኢትዮጵያዊ በአካባቢው ላይ ..ፍትህ፣ መልካም አስተዳደር እና ልማት የለም.. በሚል ከክልሉ አስተዳደር እስከ ጠ/ሚኒስነር መለስ ዜናዊ ቢሮ ድረስ አቤቱታ ቢያቀርብም መፍትሔ ባለማግኘቱ፣ በህዳር 1/2004ዓ.ም በራሱ ላይ ነዳጅ አርከፍክፎ ካቃጠለ ከሶስት ቀን በኋላ ህይወቱ ማለፉን ተሰምቷል፡፡ የኔሰው ገብሬ ራሱን አቃጥሎ መግደሉን በተመለከተም የተለያዩ አለም አቀፉ ሚዲያዎች ሰፊ ሽፋን ሰጥተው ዘግበውታል፡፡ በአገራችንም ዜናውን በመጀመሪያ ያሰራጨውን ፍትህ ጋዜጣን ተከትሎ ሌሎች የግል ፕሬሶችም ዘግበውታል፡፡

ከልማታዊ ዜና በስተቀር መርዶ ነክ ዜናዎችን ለማስተናገድ በራቸውን የከረቸሙት ኢቲቪ፣ የኢትዮጵያ ሬዲዮና አዲስ ዘመን ግን እንደተለመደው ዜናውን አልፈውታል፡፡ ምናልባት ኢቲቪ ወደፊት ስለዳውሮ ዋካ የልማት እንቅስቃሴና የአካባቢው አርሶ አደሮች ታታሪነትን በሚገልፀው ልማታዊ ዘገባ የኔ ሰውን ያስታውሰው ይሆናል፡፡ ማን ያውቃል? ከህዝብ ቅሬታና ብሶት ይልቅ ለገዢው ፓርቲ ታማኝ በመሆን የቆመው ኢቲቪ የኔ ሰው ፀረ-ልማት እንደነበር ጥቂት የአካባቢው ነዋሪዎችን በማስረጃነት በማቅረብ ጉድ ያሰማን ይሆናል፡፡

መምህር የኔሰው ገብሬ በፍትህ ማጣትና በመልካም አስተዳደር አለመኖር ያሰማው ቅሬታ ምላሽ አለማግኘቱ አስመርሮት ራሱን ማጥፋቱን ከተለያዩ ሚዲያዎች አድምጠን ወይም አንብበን የተረዳን፣ አሊያም ከሌሎች ሰዎች ወሬውን የሰማን አብዛኞቻችን ወጣቱ በከፈለው መስዋዕትነት ከማዘናችን በተጨማሪ በአገራችን የመልካም አስተዳደር እጦት መቆጨታችን አልቀረም፡፡ ምናልባትም አንዳንዶች የፍትህ ጥያቄን ለማንሳት ልባቸው ተነሳስቷለ ብል አልተሳሳትኩም ብዬ አስባለሁ፡፡ ይህንን ጽሑፍ እያነበቡ የሚገኙ አንዳንድ የኢህአዴግ መሪዎችና ደጋፊዎቻቸው የፁህፉን ይዘት በአንድ አቅጣጫ ብቻ በማየት አመጽን እየቀሰቀሰ እንደሆነ ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ ይህ ግን ስህተት ነው፡፡ ምክንያቱም እናንተ በአመራር ላይ የተቀመጣችሁ ቢሆንም ሰብዓዊ ተፈጥሯችን ተመሳሰሳይ በመሆኑ የየኔ ሰው ድርጊት እናንተንም ማሳዘኑ አይቀርም፡፡ በመሆኑም የግለሰቡን ድርጊት ተከትሎ ህዝባዊ አመጽ ሊቀሰቀስ ይችላል የሚለውን ሀሳብ ብቻ ከማሰብ ይልቅ ራሳችሁንም ሆነ በየክልሎች እና ዞኖች የተቀመጡትን ሹመኞች ልትፈትሹ የምትችሉበት አጋጣሚም ጭምር ነው፡፡

የኔ ሰው ራሱን አቃጥሎ መግደሉን የሰሙ ጥቂት ሰዎች መሀመድ ቡአዚን ያስነሳውን አመጽ በአ ትዮጵያም እንዲደገም ነው በማለት ተናግረዋል፡፡ ይህ የየዋሆች አስተሳሰብ መሆኑን ማስረጃ መጥቀስ አያሻውም፡፡ ምክንያቱም አመጽ ለማስነሳት የራስህን ህይወት የሚያክል ነገር መስዋዕት የሚያደርግ ሰው ሊኖር አይችልም፡፡ መሀመድ ቡአዚዝም ቢሆን ከቱኒዚያ ጀምሮ መላውን ዓለም ሊያናውጥ የሚችል አመጽ እንደሚያስነሳ አስቦ አይደለም ራሱን አቃጥሎ ያጠፋው፡፡ የፍትህ እጦት ምን ያህል ስብዕናችንን ሊፈትን እንደሚችል ወደ ዳውሮ ዋካ መሄድ ሳያስፈልገን በአካባቢያችን ያለው ኢ-ፍትሃዊነት መለስ ብለን ማሰቡ ይበቃል፡፡ ለማንኛውም መምህር የኔ ሰው ብዙዎቻችን የፍትህ እጦት ቢደርስብንም እንኳን ልንሞክረው ይቅርና ልናስበው የመማንደፍረውን ገድል ፈጽሟል፡፡

እንደሚታወቀው በብዙ ቦታዎች ሰዎች መብታቸው ሳይከበር ሲቀር ወይም በደል ሲፈጸምባቸው፣ በደል የፈጸመባቸውን አካል ለመበቀል ካልሆነ የራሳቸውን ህይወት እንደማያጠፉ ይታወቃል፡፡ አሸባሪዎች በብሔራቸው፣ በዘራቸው፣ በጎሳቸው እና በሃይማኖታቸው ላይ ኢ-ፍትሃዊ ድርጊት ፈጽመዋል የሚሏቸውን አገሮች ላይ ጥቃት ሲፈጽሙ፤ ፍትህን ተነፍገዋል ላሏቸው ህዝቦች ፍትህን እየሰጡ እንደሆነ ይሰማቸዋል፡፡ መላው ዓለም እነርሱን ሽብር ፈጣሪዎች እንደሆኑ ይፈርጃቸው እንጂ ..ጆሮ የተነፈጋቸውን ሚስኪን ህዝቦች ድምጽ.. እያሰሙ እንደሆነ ነው የሚያስቡት፡፡ ራሳቸውንም አሸባሪ እንደሆኑ ሳይሆን ነፃ አውጪ ኃይሎች አድርገው ነው የሚመለከቱት፡፡ ይህ አስተሳሰባቸውም የራሳቸውን ህይወት እንኳን መስዋዕት በሚያደርግ ጥቃት ውስጥ በድፍረት ይሳተፋሉ፡፡ የኔሰውን ተቃጥሎ መሞት ተከትሎ የኢትዮጵያ መንግስት ምንም ምላሽ አልሰጠም፡፡ እብድ ሆኖ ራሱን ያቃጠለ ሰው በታሪክ የማይታወቅ ቢሆንም፣ የገዥው ፓረቲ የዜና አገልግሎት የሆነው ዋልታ ግለሰቡ የአእምሮ በሽተኛ መሆኑን ገልጿል፡፡ በተመሳሳይ አንድ የግል ጋዜጣም እብድ መሆኑን ዘግቧል፡፡

የኔሰው ገብሬ ራሱን በራሱ በእሳት አቃጥሎ ከሞተ በኋላ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ፣ ታዋቂ ኢትዮጵያዊያን የፖለቲካ ተንታኞች ሃሳባቸውን ሰንዝረዋል፡፡

Page 8: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

የስታንፎርድ ዩኒቨርስቲ ተመራቂ የሆነው ጃዋር መሀመድ Yenesew’s self immolation, an ultimate call for justice በሚል ርዕስ ባቀረበው መጣጥፍ ላይ እንደገለፀው፣ የየኔሰው ድርጊት የተቃውሞ መግለጫ የመጨረሻ ልዩ ምልክት ተደርጎ የሚወስድ ነው፡፡ በተለይ ህዝብ በመንግስት ላይ የተሰማውን ቅሬታ ከአመፅ ውጪ በሆነ መንገድ የሚገለጽበት ነው ብሏል፡፡ ጃዋር መሀመድ አያይዞም የየኔሰው ተግባር ለመንግስት አካላትና የእነርሱ ደጋፊ ለሆኑ የውጭ መንግስታት ግልጽ መልእክት ነው በማለት ከገለፀ በኋላ፣ የኢትዮጵያ መንግስት የግለሰቡን ጥያቄ ካለመመለሱ በላይ በመጨረሻም ራሱን ካቃጠለም በኋላ ምንም ምላሽ አልሰጠም በማለት ገልጿል፡፡ ታዋቂው ፕሮፌሰር አለማየሁ ገ/ማርያም ደግሞ Ethiopian patriot Yenesew Gebrei give me Liberty or give me Death በሚል ያቀረቡትን ጽሑፍ የጀመሩት በርትራንድ ራስል የተባለ የ20ኛው ክ/ዘመን ታላቅ ፈላስፋ ንግግርን በመጥቀስ ነው፡፡ የፈላስፋው ጥቅስ አገር ወዳዶች ወይም አርበኞች ሁሌም ሲናገሩ፣ ለአገራችን እንሞታለን በማለት እንጂ፣ ለአገራችን ብለን በጭራሽ አንገልም የሚለውን ሀሳብ በመጠቀም ነው፡፡

ፕሮፌሰሩ፣ የየኔሰው ራሱን በራሱ አቃጥሎ የመግደል እርምጃን ሲገልፁ ..የኔሰው ለአገሬ እሞትላታለሁ የሚለውን አባባል ብቻ አይደለም የተናገረው፡፡ በትክክል ለአገሩ ሲል ሞቷል.. በማለት ነው፡፡

የኔሰው የሞተው ለወገኑ፣ ለዴሞክራሲ፣ ለነፃነት፣ ለሰብዓዊ መብት፣ ለፍትሕ፣ ለህግ የበላይነት ነው፡፡ በዚ ድርጊቱ የኔሰው ወደፊትም ቢሆን በዚህ ትውልድና በመላው የኢትዮጵያ ህዝብ የአርበኝነት ምልክት ተደርጐ ይወሰዳል፡፡ እውነተኛ አርበኛ ደግሞ ስለ ራሱ መብት ብቻ ሳይሆን ስለህብረተሰቡ መብት የሚሟገት ነው፡፡ እውነተኛ አርበኛ ድምጻቸው ለማይሰማ ህዝቦች ድመጻቸው እንዲሰማ አጥብቆ የሚታገል ነው፡፡ እውነተኛ አርበኛ ህዝቡ መንግስትን መፍራት እንዳለበት ሳይሆን መንግስት ህዝቡን መፍራት እንዳለበት ያምናል፡፡ እውነተኛ አርበኛ አምባገነንነትን፣ ጨካኝነት፣ ጨፍጫፊነትን፣ ኋላ ቀር አገዛዝን፣ ወንጀልን፣ ህገወጥነትን፣ ኢ-ፍትሃዊነትን፣ ኢ-ሰብዓዊነትን፣ ጠላትነትን እና ዘረኝነትን አጥብቆ የሚያወግዝ ነው፡፡ በዚህ መሰረት መምህር የኔሰው እውነተኛ አርበኛ ነው፡፡ በእርግጥም መምህር የኔሰው ገብሬ የዴሞክራሲና የፍትህ መብታቸው ለሚጣስ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ከራስ ወዳድነት አስተሳሰብ ፍፁም በፀዳና በተለየ መንገድ ራሱን መስዋት በማድረግ ያቀረበ ጀግና ነው፡፡ እስከ ዘላለምም በኢትዮጵያዊያን ዘንድ ሲታወስ ይኖራል፡፡

Page 9: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ርእሰ አንቀጽ

“አኬልዳማ” ፊልም ወይስ የፍርድ ውሳኔ?

በዚህ ሳምንት እንደተለመደው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ድርጅት አፍዝዝ አደንግዝ የሆነውን ዘጋቢ ፊልም አቀርቧል፡፡ ርዕሱንም አኬልዳማ ብለውታል፡፡ “አኬልዳማ” የሚለው ርዕስን የተጠቀሙት የርዕሰ ጉዳዩን አሳሳቢነት ለማስመር በመፈለግ ይመስላል፡፡

የዚህ ፊልም ጭብጥ ዋነኛ ማጠንጠኛ በዚህ ወቅት ለእስር የተዳረጉትን ጋዜጠኞችና የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ መሪና አባላት የሆኑ ግለሰቦች በሽብር ስራ ተሳታፊ መሆናቸውን ለማረጋገጥ አስረጅ መረጃ ይዘው ለመቅረብ ቢሆንም ፊልሙ ከብዙ አተያይ አንፃር በብዙ ጉድልት ከመሞላቱም በላይ ህገ-ወጥ ነው፡፡

ከዚህ በፊት ይቀርቡ እንደነበሩት ዘጋቢ ፊልሞች ይኼኛውም ፊልም ላይ የእውቀትና እውነት ጉድልቶች ይስተዋሉበታል፡፡ እንደዚህ አይነት ዘጋቢ ፊልም ለማቅርብ በተረጋገጠ መረጃና በተለየ አኳኋን ርዕሰ ጉዳዩን ማየት ተገቢ ነው፡፡

ገና ለገና ሰዎቹ ተከሰዋልና ህብረተሰቡ በጥርጣሬ እንዲያይ ለማድርግ የግለሰቦቹን ወንጀለኝነት ለማረጋገጥ፣ ግብረ-መልስ በሌለበት፣ ለብቻቸው በያዙት የቴሌቪዥን ጣቢያ ፊልም እየቆራረጡ፣ ንግግር እያሳመሩ ማቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በፓርላማ ቀርበው ንግግር ባደረጉበት ወቅት ትልቅ አፅንኦት ሰጥተው የተናገሩት ዋነኛው ርዕሰ ጉዳያቸው የነበረው የነፃ ጋዜጣ ዘጋቢዎች ተከሳሾችን ከፍርድ ቤት አስቀድመው ነፃ ማለታቸውን በማውገዝና ለዚህም “ጋጠ-ወጥ... የጋዜጠኝነት ሀሁ ያልገባቸው” የሚሉ በዘለፋ የተሞሉ ንግግሮችን ማድርጋቸውን እናስታውሳለን፡፡

የርሳቸው መንግስት በበላይነት በሚቆጣጠረው የሚዲያ ተቋም ግን በማን አለብኝነት ያቀረቡትን ዘጋቢ ፊልም ከፍርድ ቤት በፊት ፍርድ ሰጥተው መጨረሳቸውን ስንመለከት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዘለፋ ለማን ይሆን? እንድንል እንገደዳለን፡፡

ኢቲቪ ፍርድ ቤት ነገሩን አጣርቶ ውሳኔ እስኪሰጥ ትዕግስቱን አሳጥቶታል፡፡ ሰዎቹ ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ፍርዱን ጨርሶ መዝገቡን ዘግቷል፡፡ ከዚህ በኋላ ፍርድ ቤቱ በምን አይነት ጫና ውስጥ ሊገባ እንደሚችል መገንዘብ እንችላለን፡፡ምክንያቱም ዳኞቹም እንደማንኛወም ዜጋ ኢቲቪን መመልከታቸው ስለማይቀር ነው፡፡

ፍትህ እንዲህ አይነቱን በፍርድ ቤት ስራ ላይ የሚደረግ ጣልቃ ገብነትን አጥብቃ ትቃወማለች፡፡ ኢቲቪም ሆነ ፕሮግራሙ እንዲቀርበ መመሪያ የሰጡ ባለስልጣናት ለፍርድ ይቀርቡ ዘንድ ፍትህ ትጠይቃለች፡፡

ነፃ ጋዜጠኞች ላይ የሚሰነዝሩት ቁጣዎች እና ማስፈራሪያዎች ለምንድን ነው የመንግስት ተጠሪዎችን የማይመለከተው? ፍርድ ቤቱ በራሱ አጣርቶ እንዲወስን ጊዜ የሚሰጠው መቼ ነው? ዜጐች ባልሰሩት ስራ የሀሰት ትረካዎችን በቃላት እያሳመሩ የሚከሱትና ፍርድ የሚሰጣቸው ማቆሚያው መቼ ነው? ፍትህን ለሚፈልጉ ዜጐች አሁንም ፍትህ ከደጃፋቸው ትሆን ዘንድ አቋማችንን እንገልፃለን፡፡ በመጨረሻም ከፊልሙ በኋላ አንዳንድ “ግለሰቦች” በቴሌቪዥን በሰጡት አስተያየት መሰረት “እነዚህን ግለሰቦች መፍታት በራሱ እኛን ለማስጨረስ ነው” ብለዋል ተብለው ህዝቡን በራሱ ዜጐች ላይ እንዲረባረብ አድርጎ ፍርድ ቤቱ ላይ ጫና ለማሳደር የተደረገውን ድርጊት ፍትህ አጥብቃ ትቃወማለች፡፡

Page 10: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

አስተያየት

ህገ መንግስቱ ይከበር ሞራላችንም ይጠበቅ አንተነህ ደረሰ ከተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን ለመረዳት እንደቻልነው ኢትዮጵያ በሃህሞ....መ ላይ የሚካሄደውን 16ኛው አለም አቀፍ ኮንፈረንስ

ለማስተናገድ ዝግጅቷን አጠናቃለች፡፡ ከዚህ ኮንፍረንንስ ቀደም ብሎ ግን ወንድ ግብረሰዶማውያን በአፍሪካ ህጋዊ እውቅናና ከለላ እንዲያገኝ የሚሰሩ ግለሰቦችና አለም አቀፍ ተቋማት በመጪ ው ቅዳሜ (23/03/04) በመዲናችን አዲስ አበባ ጉባኤቸውን ለማካሄድ ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል፡፡

እዚህ ላይ ጉባኤው ከሀገሪቱ ህግ አንፃር እንዴት ይታያል? ግብረሰዶማዊነት ለኛ ለኢትዮጵያዊያን ምን ማለት ነው? ጉባኤው በሀገራችን መካሄዱ ምን አንድምታ አለው? የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳታችን አይቀርም፡፡ የመጨረሻውን ጥያቄ ለአንባቢያን ልተውና የቀሩት ላይ ጥቂት ልበል፡፡

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 27 ንዑስ አንቀጽ 5 ላይ በግልጽ እንደተመለከተው ምንም እንኳ ማንኛውም ሰው የአመለካከት ነፃነት ቢኖረውም ነገር ግን የያዘው አመለካከት ለህዝብ የሞራል ሁኔታ ተፃራሪ ከሆነ ይህንን አመለካከቱን ከመግለፅ በህግ ሊገደብ እንደሚችል ደንግጓል፡፡ በህገ መንግስቱ መሰረት የወጣው የወንጀል ህግም በአንቀፅ 643 በግልፅ እንዳስቀመጠው ከግብረገብ (ሞራል) ውጭ የሆኑ ነገሮችን፣ ምርቶችን እና ስራዎችን ህዝብ በተሰበሰበበት ቦታ (In public) ማቅረብ ወይም መግለፅ ወንጀል መሆኑን ይደነግጋል፡፡ መቼም ጉባኤው በግል የሚካሄድ አለመሆኑ ግልፅ ነው፡፡ በጉባኤው ላይም ወንድ ግብረሰዶማዊነትን የሚመለከቱ ንግግሮች፣ ጥናታዊ ፅሁፎች፣ በራሪ ወረቀቶችና የመሳሰሉት ስራዎች መቅረባቸው አይቀርም፡፡ የወንጀል ህጉ ግብረ ሰዶማዊነትን ከግብረ (ሞራል) ውጭ መሆኑን በግልፅ ከአንቀፅ 629-631 ባሉ ድንጋጌዎች የህዝብን ሞራል በመፃረር የሚፈፀሙ ወንጀሎች በተዘረዘሩበት ምዕራፍ ስር አስፍሮትና ቅጣትም ጥሎበት እናገኘዋለን፡፡ እነዚህን ሁለት ህጐች (ህገ-መንግስቱንና የወንጀል ህጉን) በጋራ ስንመለከታቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ግብረ ሰዶምን መፈፀም አይደለም ግብረ ሰዶምን የሚያበረታቱ (Pro homosexual) አመለካከቶችን ህዝብ በተሰበሰበበት መግለፅ በህግ የተከለከለ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ህጉ ይህን የሚል ቢሆንም ህግ አስፈፃሚው ወዶና ፈቅዶ የወንድ ግብረ ሰዶማዊነት የህግ ከለላ ያገኝ ዘንድ የሚታገሉ አካላት ጉባኤያቸውን አመላካከታቸውን መግለፅ ኢ-ህገ መንግስታዊ በሆነበት ሀገራችን ሊየካሄዱ ነው፡፡

ግብረ ሰዶማዊነት በሃይማኖታችንም በባህላችንም የተወገዘ ተግባር ነው፡፡ የትኛውም የኢትዮጵያ ባህል ወይም ሃይማኖት ግብረ ሰዶማዊነትን ይጠየፋል፡፡ ይህንን የማይጠየፍ ሃይማኖት ወይም ባህል አለን የሚል አካል ቢኖር እንኳን ከላይ የጠቀስኩትን የህግ ድንጋጌ ስለሚፃረር ከተጠያቂነት የሚድን አይሆንም፡፡

በጉዳዩ ላይ በመጀመሪያ ደረጃ ድምጻቸውን ማሰማት ካባቸው አካላት መካከል የሃይማኖት አባቶች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የሃይማኖት አባቶች ማክሰኞ እለት (19/03/04) በአዲስ አበባ የስብሰባ ማዕከል መግለጫ ለመስጠት በቦታው የተገኙ ቢሆንም የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴውድሮስ አድሃኖም በቦታው በመገኘት የሃይማኖት አባቶችን በማነጋገር መግለጫው ለሌላ ጊዜ እንዲተላለፍ በማድረጋቸው የሃይማኖት አባቶች በጉዳዩ ላይ አንድም ቃል ሳይናገሩ ወደ መጡበት ተመልሰዋል፡፡

ይህ ብዙ ጥያቄዎችን የሚያጭር ተግባር ነው፡፡ የሃይማኖት አባቶች ምን ነካቸው? ለነፍሳቸው ለሃይማኖታዊ አስተምሮ ያደሩ አይደሉም እንዴ? መንግስት ሌላ ሃይማኖት ሌላ፡፡ ሃይማኖታችን ግብረ ሰዶማዊነትን አይፈቅድም ብለው ጉባኤውን ቢያወግዙ ምን አለበት? ዶ/ሩስ ምን ነክቷቸዋል? ማድረግ ያለባቸው ህገ መንግስቱን ማክበርና ማስከበር፣ የህዝብን ሞራል መጠበቅ እና ጉባኤው እንዳይካሄድ ማድረግ ነው ወይስ የሃይማኖት አባቶች ጉባኤውን እንዳያወግዙ ማድረግ? መንግስት ጉባኤውን ከፈቀደ የሃይማኖት አባቶች ጉባኤውን እንደያወግዙ ማድረግ? መንግስት ጉባኤውን ከፈቀደ የሃይማኖት አባቶችም መንግስትን ፈርተው ዝም ካሉ የህዝቡን መብት ማን ያስከብር? ድምጹንስ ማን ያሰማለት? ሞራሉንስ ማን ይጠብቅለት?

በመጨረሻም ይህን እላለሁ ይህን ጉባኤ በሃገራችን እንዲካሄድ የፈቀደ አካል አንድ ቀን በህግ ተጠያቂ በታሪክም ተወቃሽ መሆኑ አይቀርም፡፡ መንግስት ደጋግሞ እንደሚለው እኔም መንግስትን እላለሁ ..ህገ መንግስቱ ይከበር.. ሞራላችንም ይጠበቅ፡፡ ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ

Page 11: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ጓደኞቹን መልሱለት! መምህር ወንድሙ ኢብሳ LLB AAU

የኢትዮጵያ ህዝብ በአፄ ኃ/ስላሴ ዘመን መጨረሻ ድረስ 30ሚሊዮን ይገመት ነበር፡፡ በደርግ ደግሞ 45 ሚሊዮን ገደማ፤ ዛሬ

በኢህአዴግ ዘመን ከ80 ሚሊዮን በላይ ሆነዋል፡፡ ከህዝቡ ቁጥር አንፃር ተፈላጊ እድገት እና አመራር፣ የህግ የበላይነት፣ የህዝብ አሸናፊነት፣ የነፃ ሀሳብ መስጠት እና መቀበል አላደገም፡፡ ከ99 % በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬ በአስፈሪና አሸማቃቂ የኑሮ ውድነት በስደት እና በፍራቻ እየኖረ ይገኛል ተብሎ ይታሰባል፡፡ 1ኀ የገዢው ፓርቲ ታማኞች እና ተባባሪዎች ዛሬ ኢትዮጵያን ተቆጣጥረው ምድራዊ ገነታቸውን ፈጥረው ለራሳቸው ብቻ እየፈነጩባት ይገኛሉ፡፡

የደርግ አብዮታዊ ዴሞክራሲ እና የኢህአዴግ ልማታዊ ዴሞክራሲ ሁለቱም ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ለታማኞቻቸው ለመደብ ጥቅማቸው ብቻ የቆሙ ናቸው፡፡

ይህንን ያህል ለመግቢያ ከጠቀስኩኝ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ጓደኞቼን መልሱልኝ ሲል የፃፈውን ሀሳብ መነሻ በማድረግ ነፍሴ የነገረችኝን አንድ ነገር ልበል፡፡ ይኼውም እኔም እንደተመስገን ሁሉ ገዢዎቻችንን በህግ አምላክ ጓደኞቹን መልሱለት ብዬ ተማፅኖዬንም አቀርባለሁ፡፡

በኢትዮጵያ አገራችን ምግብ ተወዷል፣ ልብስ ተወዷል፣ ትራንስፖርት ተወዷል፣ ውሃ ተወዷል፣ መብራት ተወዷል፣ የቤት ኪራይ ተወዷል፣ የትምህርት ቤት ክፍያ ተወዷል፣ የደብተር ዋጋ ተወዷል፣ የመጽሐፍ ዋጋ ተወዷል፣ የመድሀኒት መግዣ ዋጋ ተወዷል፣ መጠጥ የተባለው ሁሉ ከትኩስ እስከ ቀዝቃዛ ቡናና ሻይን ጨምሮ ተወዷል፡፡ ምን ያልተወደደ ነገር አለ? ብፈልግ አጣሁ፡፡

ሽሮ፣ በርበሬ፣ አተር፣ ምስር፣ ቲማቲም፣ አትክልት እና ጥራጥሬ ሁሉ ዋጋቸው ተወዷል፡፡ በአንፃሩ በኢትዮጵያችን ለሙ የጋምቤላ መሬት አንድ ሄክታር ለውጪ ባለሀብት ከሆነ ከአንድ የብርቱካና ሙዝ ዋጋ በኪሎ ወርዶ ዘጭ ብሏል፡፡ ለኢትዮጵያውያን ሲሆን ግን በግልባጩ መሬትን ለቤት መስሪያም ሆነ ለሌላ ልማታዊ ግብዓት ከፈለጉ እጅግ በጣም ተወዷል፡፡ ሌላ ምን ያልተወደደ ነገር አለ? ብዬ ፈለኩ፡፡

ጤፍ፣ ስንዴ፣ ገብስ፣ በቆሎና ማሽላም ተወደዋል፡፡ ስኳር ቡና ተወዷል፣ ዘይት ተወዷል፣ ስራ ማግኘት ተወዷል ከማለት ይልቅ አለተቻለም ማለት ይቀላል፡፡ የስራ ዋስትና ተወዷል፡፡ ከህግ መአቀፍ ወጥቶ በገምጋሚ አለቃ እጅ ተከርችሟል፡፡ በእውነት ምን ያልተወደደ ነገር አለ? እውነት የሆነ ዜና በኢትዮጵያ ከላይ እስከ ታች መስማት ከቶ እየቀረ ነው፡፡

በአንፃሩ ደግሞ የማይታይ ልማት እና እድገት፤ዳቦ የማይገዛ ገቢ በሽበሽ ነው ይሉናል፡፡ በመግቢያዬ ላይ እንደጠቀስኩት ለ1ኀ ቅምጥልና ሽቅርቅር ባለጊዜዎች የሆነ እንደሆነ አዎን እንደ አፄና ደርግ ዘመን ሁሉ ኢትዮጵያ ለእነሱ በልፅጋለች ማለት ይቻላል፡፡ ለ99ኀ ኢትዮጵያውያን ግን ኑሮ ከድጡ ወደ ማጡ፤ ከፍሙ ወደ ነበልባል ረመጥ እሳት እየሆነ ነው፡፡ የኔሰው ገብሬ ፍትሕ እና መልካም አስተዳደር ከኢትዮጵያ ጠፋ ብሎ በራሱ ላይ ቤንዚን አርከፍክፎ ራሱን ማጥፋቱ ለዚህ ማረጋገጫ ነው፡፡

ዛሬ ሽብልቅ እውቀት እንጂ ትክክለኛ እውቀት እጅግ ተወዷል፤ አልያም ተሰዷል፡፡ ባለሽብልቅ እውቀቶች ግን በበርም በመስኮትም እየገቡ ለብዙሃን ሰቀቀን እየፈጠሩ ነው፡፡ ዛሬ ሰላምና መረጋጋትን፣ እንደልብ ወጥቶ መግባትን ፀረ ሽብር በተባለው አስፈሪ ህግ ከባለጊዜዎች ውጪ ሌሎቹ ኢትዮጵያውያን ዋስትናው እየቀጠነ እየጠፋ ነው፡፡ እጅግ አስገራሚው ነገር ከላይ የጠቀስኩት ሁሉ ጠፍቶ አብሮ አደግ ጓደኛ፣ የሙያ ጓደኛ፣ የስራ ጓደኛ በኢትዮጵያ ምድር ዛሬ እጅግ ተወዷል ወይም ተሰዷል፡፡

ይሄንን የምለው የትንታጉ ብዕረኛ ብላቴና ተመስገን ደሳለኝ ጥያቄ የሚሊዮኖች ጥያቄ ስለሆነ ነው፡፡ የጓደኞቹ በየጊዜው በስደት እና በእስር እየሳሱና እየመነመኑ መሰደድ አሰቃቂነትና አሳሳቢነት ተመስገንን እና ጓደኞቹን እንደለያያቸው እንዳይቀር ወደ ውጭ ሳይሆን ወደ አገር ውስጥ መልሱልኝ ባለው መሰረት ጓደኞቹ ይመለሱለት ስል ለገዢዎቻችን የተማፅኖ ብሶትና አቤቱታ በኢትዮጵያዊ ትህትና አቀርባለሁ፡፡

ኢህአ ዴግ ከደርግ ትንሽም ቢሆን የተሻለ ነው ስለምል የተመስገን ጓደኞች ይመለሱለታል ብዬም ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ጱረ ጎበዝ ኑሮ ተወዶ፣ ጓደኛ ተወዶ ተሰዶ፣ ምግብ ተወዶ፣ ነፃ ጋዜጦች እና የተለየ አስተያየትና አስተሳሰብ ተወዶ

ኢትዮጵያችን ምን እየሆነች ነው? አብሮ አደግ ጓደኛን፣ ሚስትን፣ ባልን፣ ልጅን፣ አባት እና እናትን፣ ጐረቤትን፣ ጠያቂ ሰላምተኛን፣ መንደር እና የሰፈር

ሽማግሌን፣ እየናፈቅን እና እየተሳቀቅን እንደምን ሰላሳና አርባ ዓመታት መሪ አሰባሳቢ አጥተን እንዘልቃለን? ክፋት በዝቶ መሰረታዊ ለውጥ ማምጣት ጠፍቶን እስከመቼስ በሰዶ ማሳደድ እንኖራለን? ስለዚህ ተመስገን እንደተማፀነው

ትንታጐቹ ብላቴናዎቹ ተንታኞች እውቀትን በነፃ ሰጪዎች የአዲስ ነገሮቹ፣ የአውራምባው ዳዊት ከበደ እና ዝነኛው የወግ ፃሀፊ አቤ ቶኪቻው ከተሰደዱበት ሀገር ይመለሱ፡፡ ይሰባሰቡ፡፡ ቃሊቲ የተላኩትም ይፈቱልን፡፡ ቀጣዩ ማነው የሚለውንም ስጋት ማቆሚያ ያብጁለት ስል በድጋሚ እማፀናለሁ፡፡ እንደ ክቡር ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እኔም ሳስበው ሳስበው ሳስበው እንደ ተመስገን ሁሉ አሳዳጆቹ በቃን ካላሉ እንደደርጐቹ በመጨረሻ መሰደዳቸው አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህ ገዢዎቻችን ቁጣችሁን አብርዱ ካልሆነ፤ ወይ በሪቮሊውሽን አሊያም በኢቮሊውሽን በቅጽበታዊና በዝንፈታዊ ለወጥ እንደነሙባረክ እና ጋዳፊ ኋላ የቃሬዛና ቱቦ ቲያትር ዳግም በኢትዮጵያም እንዳይታይ ንቁዎቹ ኢትዮጵያውያን ከገዢ እስከ ተቃዋሚ እንተባበር፡፡ በተለይም ገዢዎቻችን ስለተሰዉት ጓዶቻችሁ ብላችሁ የተመስገንን ጓደኞች መልሱአቸው (ከስደትም ከቃሊቲም..፤ እስከመቼስ አለም ተሳልቆብን እየተሳቀቅን አንገት ደፍተን በውስጥም በውጭም እንደ ውሻ ልጆች ሰዶ በማሳደድ እንኖራለን፡፡ ስደት ይብቃን፡፡ ጓደኞቼን መልሱልኝ የተመስገን ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ነውና ልትመልሱለት ይገባል፡፡ እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ ፡፡

Page 12: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

“አኬልዳማ”ው የአይሁድ ወይስ የኢህአዴግ? ተመስገን ደሳለኝ

አኬልዳማ-የደም መሬት፡፡ አኬልዳማ የእብራይስጥ ቃል ነው፡፡ የአማርኛ ትርጓሜው የደም መሬት የሚል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የመለስ መንግስት ምን እንደነካው እንጃ ብቻ መሬት መሬት ብሏአል፡፡ የኢንቨስተር መሬት፣ የሪል እስቴት መሬት፣ የአባበ

እርሻ መሬት፣ የሩዝ መሬት፣ ለህንድ የተሰጠ መሬት፣ ለሳውዳአረቢያ የተሰጠ መሬት፣የሊዝ መሬት፣ የደም መሬት (አኬልዳማ)...፡፡ በእርግጥ መንግስት እስከዛሬ ድረስ ..መሬት..ን የሚያየው ሸንሽኖ ከመሸጥ አንፃር ብቻ ነበር፡፡ ሰሞኑን ደግሞ የፊልም ርዕስ አድርጎታል፡ ፡ ... አኬልዳማ-የደም መሬት፡፡

ጥቂት ስል አኬልዳማ፡- በክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተተረከው አለምን ለማዳን የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ ወጌልን በሚሰብክበት ወቅት 12 ደቀመዛሙርት (ተከታይ ጓደኞችን) መርጦ እንደነበረ እናነባለን፡፡ በመጨረሻም ከእነዚህ ተመራጮች አንዱ የሆነው የአስቆሮቱ ይሁዳ የመረጠውን፤ ያከበረውን ኢየሱስ ክርስቶስን በ30 ዲናር ለጥላቶቹ ሸጠው፡፡ ሆኖም ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ይሁዳ ንፁህ ወዳጁን አሳልፎ እንደሰጠ ገባውና ተፀፀተ፡፡ ተፀፅቶም አልቀረ የተቀበላትን 30 ዲናር ለገዢዎቹ መለሰላቸው፡፡ ገዢዎቹም ..ካልፈለክ ተወው.. የራስህ ጉዳይ ነው.. ብለው ገንዘቡን ከተቀበሉ በኋላ መሬት ገዙበት፡፡ እነሆ ያ መሬት በወዳጁ በተሸጠ ንፁህ ሰው ደም የተገኘ መሬት በመሆኑ ዛሬም ድረስ “አኬልዳማ” (የደም መሬት) እየተባለ ይጠራል፡፡

ይሄ ከሆነ ከሁለት ሺ አመት በኋላ የኢትዮጵያ ገዥ ፓርቲ “አፍ” የሆነው ኢቲቪ፤ የገዢው ፓርቲ “ጠላቶች”ን ወንጀል የሚተርክ ፊልም አዘጋጅቶ ወይም ጣጣ ፈንጣጣው ያለቀለትን ፊልም ተቀብሎ “አኬልዳማ” በሚል ስም ለሶስት ቀን ያህል አሳይቶናል፡፡ በእርግጥ ያ በክርስቶስ ደም የተገኘው የ”አኬልዳማ” ትርጓሜ እና የኢቲቪ የፊልም ጭብጥ ሀራምባና ቆቦ ነው፡፡ ምክንያቱም የአይሁድ ካህናቶች “አኬልዳማ” ያሉት መሬት የተገዛው ይሁዳ የተባለ ሰው፤ ክርስቶስ የተባለውን ወዳጁን ሸጦ ባገኘው ገንዘብ ነው፡፡ የኢህአዴግ “አኬልዳማ” ጭብጥ ደግሞ ከሀገር በቀሎቹ እስከ አልቃይዳ፣ አሊ-ታሀድ፣ ሻዕቢያ፣ አልሼባብ... ድረስ ያካተተ ነው፡፡ እናም የፊልሙ እርስ የፊልሙን ጭብጥ ሊወክል ይችል የነበረው በፊልሙ ላይ አንዳርጋቸው ፅጌ፣ ብርሃኑ ነጋን አሳልፎ ሲሰጠው የሚታይ ቢሆን ኖሮ ነበር፡፡ ወይም አልቃይዳ ተተኪ ሊቀመንበሩን አይማን አልዛሃዋሪን ሲሸጥ የሚያሳይ መሆን ነበረበት፡፡

የሆነ ሆኖ በአኬልዳማ ፊልም ላይ የሚጣረሱ ነገሮች በመኖራቸው “ሂስ” መስጠቱ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ሌላው ቢቀር ዳሬክተሩ እና ደራሲው በሚቀጥለው ለሚያዘጋጁት ዶክመንተሪ ፊልም ገንቢ አስተያየት ሊያገኙ ይችላሉና፡፡ መማር ከፈለጉ ማለቴ ነው፡፡ አሊያ እንዲህ እንዳየነው አይነት ቀሽም ፊልም እየሰሩ መሳቂያ መሳለቂያ መሆን ነው፡፡ መቼም የዚህ ፊልም ደራሲ እና ዳሬክተር እንደእነ ሠራዊት ፍቅሬ እና ጓደኞቹ ሰማያዊ ፈረስ፣ ሄሮሺማ፣ አባይ ምናምን ቬጋስ... እንደሚሉን “አርቲ-ካድሬ”ዎች አይደሉም፡፡ እነዚህኞቹ (የአኬልዳማ ባለቤቶች.. ፊልም የሚሰሩት ገንዘብ ለማግኘት አይደለም፡፡ ገንዘብ ሞልቶ የተረፋቸው ናቸው፡፡ ገንዘብ ከፈልጉም እንኳ ከፊልም ይልቅ በጥቂቱ የታክስ ጭማሪ ቢያደርጉ ገቢው የትየለሌ እንደሆነ ከልምድ ያውቁታል፡፡ እናም እነሱ ፊልም የሚሰሩት ሲያሻቸው ታክስ እንዲጨምሩ፣ ሲያሻቸው መሬት እንዲሸጡ፣ ሲያሻቸው ከትዳር ጓደኛቸው ጋር በሚሊኒየም አዳራሽ እንዲደንሱ፣ሲያሻቸው... ብቻ የፈቀዱትን ለማድረግ የሚያስችላቸውን እና የሚንደላቀቁበትን “ስልጣነ መንግስት” ለማስጠበቅ ነው፡፡ ...ማንነታቸው ላይ መነጋገሩ እዚህ ይገታና ስለፊልሙ እናውራ

ከጭብጡ እንጀምር፡፡ እንግዲህ የወቅቱ ፖለቲካ “አሸባሪ” እና “ሽብርን መከላከል” እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ እናም አሸባሪ በሚል ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞች፣ መንገደኞች... በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ ይህንን ተከትሎም መንግስት ሰዎቹን ያሰራቸው ስለተቹት እና ስለተቃወሙት እንጂ አሸባሪ ሆነው አይደለም የሚል ተቃውሞ ከውስጥም ከውጭም መነሳት ሲጀመር፤ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ሰዎቹ የተያዙት በበቂ ማስረጃ መሆኑን ገልፀው በሁለት ሳምንት ውስጥ ማስረጃውን ለህዝብ ይፋ አደርጋለሁ አሉና ተቃውሞውን አስተባበሉ፡፡ ሆኖም ከአምስት ሳምንት በኋላ ማሰረጃ የተባለው “አኬልዳማ” በሚል ስም የቀረበ ፊልም ሆነ፡፡ (ምናልባትም የፊልሙ ደራሲ ራሳቸው አቶ መለስ ሊሆኑ ይችላሉ)

ብዙሃኑም ፊልሙን በንቃት ተከታተለ፡፡ የቴሌቪዥን ኤቲክስ (ስነ-ምግባር) እንደተጠበቀ ሆኖ ማለቴ ነው፡፡ ምክንያቱም ሆሊውድ የሚሰሩ አስፈሪ ፊልሞች እንኳ ቢያንስ ከ16 አመት በታች እንዳያዩት የሚከለከል ሆኖ እያለ፤ ኢቲቪ ደግሞ የተቆረጠ አንገት፣ የተገነጠለ እጅ፣ የተፈረከሰ ጭንቅላት... እያሳየ 13 ዓመት የሞላው በሙሉ ሊያየው ይችላል ይላል፡፡ ያውም ሲኒማ ቤት ሳንሄድ እቤታችን ድረስ መጥቶ ማለቴ ነው፡፡

...ወደ ጭብጡ እንመለስ፡፡ የመለስ መንግስት “አሸባሪ” ብሎ ለአሰራቸው ጋዜጠኞች እና ፖለቲከኞችም ሆነ እየተፈለጉ ባሉት ያልተያዙ “አሸባሪዎች” ላይ በአኬልዳማ ፊልም ከቀረበው አንዱ ማስረጃ መላ ቤተሰባቸውን ያጡ አንድ ግለሰብ በሚሰጡት ምስክርነት የሚጀምር ነው፡፡ ግለሰቡ ባለቤታቸው እና ልጆቻቸው በኦነግ እንደተገደሉ የሰጡትን ቃል ነው በአኬልዳማ ፊልም ያየነው፡፡ ሆኖም በፊልሙ የቀረበውን አልደግመውና፤ ኢቲቪ ከሰውየው ቃል የቆረጠውን ቀጥዬ፤ ሰውየው የተናገሩትን ሙሉውን እንደወረደ ላውርድላችሁ፡-

“...ዘጠኝ ቤተሰቤን ወሰዱብኝ፡፡ ቀጥቅጠው ባለቤቴንም ገደሏት፡፡ የእኔ ወንድሞች ልንገራችሁ ባለቤቴን ገደሉብኝ፤ 34 አመት አብረን የነበረን፤ ለንብረቴ አላለቀስኩም፡፡ ስሜንም አልገልፅም፡፡ እናንተ ሄዳችሁ እዩት ሽባ ልጅ፣ አይኑ የፈሰሰ፣ እጁ የተሰበረ ልጅ መልሰውልኛል አሉ፣ አላየኋቸውም እኔ፡፡ የእኔ ወንድሞች ብትተውኝ ጥሩ ነው፡፡ ትንሽ አንጎሌ ልክ አይሰራም፡፡ እና ይሄ ነው ድርጊቱ፤ የሚደረገው ድራጎት የከተማ ወሮበላን አስታጥቀው ህዝቡን ፈጁት፡፡ አምስቱን ጓደኞቼን ገደል ከተቷቸው፡፡ የጓደኛዬን ሚስት

Page 13: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

እና የእኔን ሚስት ገደሉ፣ እንዲህ ያለ ግፍ ይሰራል፡፡ ይሄን ሁሉ የሚያደርገው መለስ ዜናዊ ነው” የሚል ነው፡፡ (ኢቲቪ የቀረፀው ይሄ ፊልም እኔም ጋር አለ ምናልባትም ኢቲቪ ጠፍቶበት ከሆነ ቆራርጦ ያቀረበው ላውሰው እችላለሁ፡፡)

ስለቃል ሰጪው ሰውየ ደግሞ ትንሽ ልንገራችሁ፡- አቶ ይርጋ ይመር ይባላሉ፡፡ ነዋሪዎነታቸው በኦሮሚያ አቡ ሴራ በተባለ

የቀበሌ ገበሬ ማህበር ውስጥ ነው፡፡ አደጋው የደረሰባቸው በጥቅምት ወር 1984ዓ.ም ነው፡፡ በአደጋውም ባለቤታቸውን አልጋነሽ ጃራን፣ የ18ዓመት ልጃቸውን ሲሳይ ይመርን እና የ9 አመቱን አሸናፊ ይመርን አጥተዋል፡፡ እሳቸውን ጨምሮ ደግሞ በላይነሽ እና ወሰኔ የተባሉ ልጃቸው በጥይት ቆስለዋል፡፡ ሆኖም አደጋውን ያደረሱት ሰዎች ለጥቂት ጊዜ ተይዘው በዋስ ተለቀዋል፡፡ አቶ ይርጋ እስከ 2000 መጨረሻ ድረስ ፍትህ አለማግኘታቸውን እና መዝገቡ ተሰረቀ መባላቸውን በሰኔ ወር 2000ዓ.ም በወጣችው ፍትህ ጋዜጣ ላይ ተናግረዋል፡፡

አኬልዳማ ፊልም ሆዬ ደግሞ ለዚህ ሁሉ ተጠያቂው “መለስ ዜናዊ ነው” የሚለውን የተበዳይ አቤቱታ ቆርጦ፤ አደጋውን እና እነእስክንድር ነጋን እያፈራረቀ ያሳየናል፡፡ ምን ለማለት ፈልጎ እንደሆነ ግን ግልፅ አይደለም፡፡ መቼም ጠቅላይ ሚኒስትሩ “ከበቂ በላይ ማስረጃ አለን” ያሉን ይሄንን ነው ብዬ አላስብም፡፡ ከሆነ ግን ደባ ራሱን፣ ስለት ... አይነት ነገር መሆኑ ነው፡፡

ሌላው ፊልሙ ሲፋቅ የምናገኘው ሀቅ አቶ ይርጋ እና ቤተሰቦቻቸው ላይ ይሄ አደጋ የደረሰው በ1984ዓ.ም በወርሃ ጥቅምት መሆኑን ነው፡፡ በዛን ጊዜ ኢትዮጵያን የሚያሰተዳድረው ወይም የሚገዛው ማን ነው? ደርግ ይሆን እንዴ? በጭራሽ፡፡ ደርግ ደግሞ በ1983 ነው የወደቀው፡፡ ...አሃ.. ትዝ አለኝ ለካስ “ጊዜያዊ መንግስት” የሚባል ተመስርቶ ነበር፡፡ እሺ! ይሄ ጊዜያዊ መንግስት በእነማን ነበር የተመሰረተው? ጥሩ ጥያቄ ነው፡፡ በኢህአዴግ እና በኦነግ በጋራ ነበር የተመሰረተው፡፡ ይሄም ጥሩ መልስ ነው፡፡ እንዲያውም በወቅቱ የኦነግ ሊቀመንበር ሌንጮ ለታ የመከላከያ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነበሩ፡፡ (የመከላከያ ሚኒስትር እንደማለት ነው)

ያን ጊዜ እነ አንዷአለም አራጌስ የት ነበሩ? የአንዱአለም ሲቪ እንደሚነግረን ከሆነ፤አንዱአለም በወቅቱ የኮከብ ፅብሃ የ10ኛ ክፍል ተማሪ ነበር፡፡

እንግዲህ እግዜር ያሳያችሁ! ይሄ የኢቲቪ ፊልም አሁን በማን ላይ የሚቀርብ ማስረጃ ሆኖ ነው እንድናየው የተደረገው? ...ደህና! አኬልዳማን መመልከታችንን እንቀጥል፡፡

የአኬልዳማ ፊልምን ስናይ ከተወናያኖቹ አንዱ ጋሽ ደቤ በማዕከላዊ እስር ቤት ዘና ብሎ፤ የዶሮ አይን የመሰለ ቡናውን እየተጎነጨ ስለሽብር ተግባሩ ሲዘረዝር የሚታይበት ፓርት አለ፡፡ ከዚሁ በተቃራኒ ደግሞ ከሶስት ሳምንት በፊት (ምን አልባትም ፊልሙ እየተቀረፀ ባለበት ጊዜ ሊሆን ይችላል) ናትናኤል መኮንን የተባለው ተከሳሽ በማዕከላዊ እስር ቤት የደረሰበትን ለፍርድ ቤቱ ሲናገር ግን ስለቡና ግብዣ አላነሳም፡፡ ይልቁንም እንዲህ ነው ያለው፡-

“በተከታታይ ለሃያ ሶስት ቀናት የፌደራል ፖሊስ መርማሪዎች ኃላፊ እና በስራቸው የሚገኙ መርማሪዎች በአካሌ፣ በሞራሌ ላይ ጉዳት አድርሰውብኛል፤ ምግብ ተከልክዬ እርቃኔን እጄ ወደ ኋላ ታስሮ ለሃያ ሶስት ቀን ውሃ እላዬ ላይ እየተደፋብኝ እነርሱ የሚፈልጉትን እንድናገር ሲያስገድዱኝ ነበር፡፡ ለአራዳ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በደሌን አቅርቤ ዛሬ መልስ እንዲሰጡ ታዞ ነበር፡፡”

የተከበረው ፍርድ ቤትም የናትናኤልን ሰቆቃ ካዳመጠ በኋላ በመሀል ዳኛው በኩል መልስ ሰጠ፡- “ዛሬ የክሱን ቻርጅ ዐቃቤ ህግ ለፍርድ ቤቱ የሚያቀርብበት ወቅት ስለሆነ ክርክሩ ሲሰማ በደልህን ታቀርባለ፤ አሁን

የምናደምጥህ መናገር ስለጀመርክ ብቻ ነው፡፡” እሺ! ክቡር ፍርድ ቤቱ፤ ለሀቅ መፍርዱ ቀርቶ ማዳመጡ ከሆነ ሀላፊነታቸው፤ መቼስ ምን ይደረጋል፡፡ እኛ ግን ስራችንን

እንቀጥል፡፡ ናትናኤል “እነሱ የፈለጉትን እንድናገር አሰቃዩኝ” ያላትን ስንመነዝራት የአኬልዳማ መስካሪዎች በዚህ በኩል የተገኙ ሊሆኑ ይችላሉ የሚል ብርቱ ጥርጣሬ ያድርብናል፡፡ መቼም ማዕከላዊ አንድ ነው፡፡ ቦታውም ያው ከአራዳ ጊዮርጊስ ትንሽ ከፍ ብሎ የሚገኘው ነው፡፡ ሆኖም አንዱን ቡና እየጋበዘ፤ ሌላውን እርቃኑን አቁሞ ውሃ እየደፉበት የሚውል ከሆነ ከዚህ በላይ የሰበአዊ መብት አክባሪነት የትም የለ፡፡ ይሄ ተባራሪ ወሬ አይደለም፡፡ ራሳቸው የጉዳዩ ባለቤቶች ናቸው በአንደበታቸው የተናገሩት፡፡ ስለቡናውም ስለ እርቃኑም፡፡

“...ቶርቸር” ስልሚባል ነገር ብዙ ሰምተናል፡፡ ያውም ከደርግ ጊዜ ጀምሮ፤ ያውም በማዕከላዊ እስር ቤት፡፡ ኢትዮጵያ የሰው ዘር መጀመሪያ እንደመሆኗ ሁሉ የ..ቶርቸር..ም መጀመሪያ ትሆን እንዴ? ፕ/ር መስፍን ወልደማርያም ለደቂቀ እስጢፋኖስ መፃሀፍ “ቀዳሚ ቃል” ይሆን ዘንድ አዘጋጅተውት፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬስ ውድቅ በተደረገባቸው መጣጥፍ ላይ “ቶርቸርን” እንዲህ ይገልፁታል፡-

“ይህን መፃሀፍ ሳነብብ ምዕራባውያን (በእንግሊዝኛ) ፣ቶርቸር፣ (የግዕዝ ፀሐፊዎች ፣ኩነኔ፣ የሚሉትን ሰውን የማሰቃየትን ዘዴ) እኛ የፈጠርነው መሰለኝ፡፡ ቻይናውያን በዚህ ክፉ ዘዴ እንደሚታሙ አውቃለሁ፡፡ እኛም ሆንን ቻይናውያን የታሪካችንን ርዝመትና ያለንበትን የደኽነትን አዘቅት ለመገንዘብ ይህ የክፋት ዘዴአችን ማስረጃ ሆኖ ሊያገለግል የሚችል ይመስለኛል፡፡”

ልክ ኖት ፕሮፌሰር፡፡ እንደሚታወቀው የእኛ እና የቻይናውያን ፍቅር ከፍቅር እስከ መቃብርም በላይ ነው፡፡ በህግ

ባለሙያዎች ዘንድ ብቻ ሳይሆን በሀገራችን ህግም “በቶርቸር” የተገኘ መረጃ፤ እንኳንም በፓርላማ ሊያስፎክር ቀርቶ፤ በአጥቢያ ዳኛም ቢሆን ተቀባይነት የለውም፡፡ ያውም በህግ አውጪው ፊት... “ከምር ማስረጃ አለን” ሊያስብል ቀርቶ...

ይሄ አይነቱ አሰራር መንግስትን ከ “መንግስትነት” ደረጃው አውርዶ የጎበዝ አለቃ ያስመስለዋል፡፡ ወይም ምዕራባውያኖቹ እንደሚሉት “Police state” ማለቴ ነው፡፡

የሆነ ሆኖ ቶርቸር በዋናነት በሁለት መንገድ ይገለፃል፡፡ አካላዊ እና ስነ ልቦናዊ ተብሎ፡፡ ለምሳሌ ናትናኤል ደረሰብኝ ያለው የቶርቸር አይነት አካላዊ በሚለው ሊመደብ ይችላል፡፡ ከቤተሰብ እንዳንገናኝ ተደረግን ያሉት ደግሞ የደረሰባቸው የቶርቸር አይነት ስነ ልቦናዊ ሊባል ይችላል፡፡

እዚህ ጋር አስቂኟ ነገር ሁሉም የአኬልዳማ መስካሪዎች በራሳቸው ላይ ከመሰከሩ በኋላ ከእስር ቤት መለቀቃቸው ነው፡፡ በእርግጥ የታሳሪዎቹ መለቀቅ መልካም ነገር ነው፡፡ እኔ ሲጀመርም የታሰሩበት መንግድ አልተዋጠልኝም፡፡ ተደጋጋሚ ጊዜ ሰዎቹ ይፈቱ ዘንድ ፅፌአለሁ፡፡ ሆኖም ታሳሪዎቹ የተለቀቁት በፊልሙ ላይ የታየውን ተናግረው፤ እንዲለቀቁ ተደራድረዋቸው ከሆነ ግን ከቶርቸር ጥቃቶች አንዱ እንደደረሰባቸው ነው የሚያስቆጥረው፡፡

ሌላው የአኬልዳማ ድራማ በማዕከላዊ እስር ቤት ሆነው ስለሽብር እቅዱ እና አፈፃፀሙ ታሳሪዎቹ ከነገሩን ውጪ መንግስት ከማሰሩ በፊት አለኝ ሲል ስለነበረው ማስረጃ አንዳች ማየት አለመቻላችን ነው፡፡ እውነት ለመናገር ኢቲቪ ፊልሙን እንደሚያሳይ ከአንድ ቀን በፊት ሲያስተዋውቅ፤ ስለእነ እስክንድር ነጋ ንፁህነት ስንመሰክር የነበረውን ምስክርነት፤ ገደል የሚከት ማስረጃ አቅርቦ

Page 14: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ሊያሳፍረን ይሆን እንዴ ብዬ ራሴን ተጠራጥሬው ነበር፡፡ እናም የመጀመሪያው ክፍል ታየ ምንም አዲስ ነገር የለም፡፡ ሁለተኛው፤ ሶስተኛው እያልኩ ጠበኩ፡፡ ሆኖም የቀረበው ማስረጃ አንዳንዶቹ ኦነግ ከኢህአዴግ ጋር በጋራ መንግስት ሆኖ የፈፀማቸው፤ ሌሎቹም እስረኞቹ ራሳቸው ከታሰሩ በኋላ ማዕከላዊ ሆነው እንዲህ ልናደርግ ነበር እንዲህ አስበን ነበር ጂኒ ቁልቋል... የሚል ሆነና አረፈው፡፡ የእኛ ጥያቄ መንግስት ሰዎቹን ከማሰሩ በፊት ሰበሰብኩ (አገኘሁባቸው) ያለው ማስረጃ የት አለ? የሚል ነው፡፡ ...ወይም እንደ መሬት ወረራው መረጃው ተሰርቆ ተወስዶ ከሆነም ይንገሩን? ኢህአዴግ እኮ ሞኝ ነው፡፡ የማይሰረቀው ነገር የለም? የምርጫ ድምፅ ይሰረቃል፣ ኮሮጆ ይሰረቃል፣ማስረጃ ይሰረቃል፤ አሁን ደግሞ የሰበሰበው ማስረጃ...፡፡ ከዚህ ውጭ ኢህአዴግ እንኳንም ጋሽ ደቤን የራሱን ታላቁ ተጋዳላይ ታምራት ላይኔንም በፓርላማ “ተመክሬ ተመክሬ አልሰማ ብያለሁ” የሚል ዘፈን አዘፍኗል፡፡ አቶ መለስ “ስንይዛቸው ይዘፍናሉ” ያሉት ይሄን ችሎታቸውን ይሆን እንዴ? ብቻ ኢህአዴግ በማናዘዝ (በማዘፈን) የተካነ ይመስለኛል፡፡

እዚህች ጋር አንዲት ቀልድ ትዝ አለችኝ ፡- ከእለታት አንድ ቀን የፌደራል ፖሊስ አባላት በከተማው ያሉትን ዝሆኖች በሙሉ ይዛችሁ ኑ ተባሉ አሉ፡፡ ከተፎ ፖሊሶቹም ያለ የሌለ የዝሆን መንጋን እየነዱ አመጡ፡፡ አዛዡም ግድያቸውን ሊጐበኙ ከቢሮ ሲወጡ ከዝሆኖቹ መሀል በድብደባ ብዛት ሁለት ጥርሱ የወለቀ እና አናቱ የተፈነከተ ፍየል ያያሉ፡፡ በሁኔታው ተደንቀው እንዲህ ሲሉ ጠየቁ “ዝሆን ብቻ አይደል እንዴ አምጡ የተባላችሁት?”፤ ከተፎ ፖሊሶቹም መለሱ “ጌታዬ! ዝሆን ነኝ ብሎ አምኗል፡፡”

የሆነ ሆኖ መለስ በቂ መረጃ አለኝ ከአሉ በኋላ እና ፊልሙ እንደሚታየ ሲነገር ከፊልሙ የጠበኩት እስክንድር ነጋ እንደ ኦሰማ ቢላደን ክላሽ ከጎኑ አድርጐ፤ ፊልድ ጃኬት ለብሶ ከሀገራችን ተራራ ስር በአንዱ መሽጐ የሽብር ትእዛዝ ሲሰጥ ነበር፡፡ ሆኖም በፊልሙ ላይ የቀረበው ግን በጋዜጣ ማስታወቂያው ተነግሮ፤ በይፋ በተጠራ የውይይት መድርክ ላይ ጥናታዊ ጽሑፍ ሲያቀርብ ነው፡፡ ይሄ ነው እንግዴ አኬልዳማ- የደም መሬት፡፡

ለአንዱአለም አራጌ ደግሞ እንደ ማጠናከሪያ ሆኖ ቀርቦ ያየነው ውንጀላ ወንድሙ በኤርትራ ለሽብር ተግባር እየሰለጠነ መሆኑ ነው፡፡ ይሄ ፌር አይመስለኝም፡፡ በምንም ሊገናኝ አይችልምም፡፡ እንዲህ ከሆነማ ዛዬም በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ያሉት የኢሳያስ አፈወርቂ ዘመዶች ምን ሊባሉ ነው፡፡ ...ይገናኝ ከተባለ ደግሞ እኛም የግድ ደርግ “ስዬ አብርሃ የወንበዴ መሪ ነው” በሚል ምክንያት ብቻ የስዬን ታናሽ ወንድም አሰፋ አብርሃን ለ7 አመት በእስር ቤት ማሰቃየቱን እንደ ህጋዊ እርምጃ ልንወስደው ነው ማለት ነው፡፡ አያችሁ የአኬልዳማ ፕሮዲሰሮች፡- ጉድጉድ ሲቆፈር ብዙ መጥለቅ የለበትም፡፡ ማን እንደሚወድቅብት አይታወቅምና፡፡

በተቀረ ሽብርተኝነትን መከላከል አስፍላጊ ነገር ነው፡፡ የሽብር ድርጊትም አረመኔያዊ ተግባር መሆኖን ለማወቅ ምንም አይነት

ትንተና አያሰፈልግም፡፡ ምክንያቱም ዋነኛ የጥቃቱ ኢላማ ሰላማዊ ዜጋ ነውና፡፡ ይሄንን ማንኛውም ዜጋ አይደግፈውም፡፡ ሻዕቢያም ፀረ ኢትዮጵያ አቋም እንዳለው ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ በዚህ በኩል ልዩነት ያለ አይመስለኝም፡፡ ልዩነቱ የሚመጣው ጋዜጠኞችን እና ሰላማዊ ፖለቲከኞችን እያሰሩ ከእነ ቢላደን እና ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር ሲደመሩ ነው፡፡አሁንም የአኬልዳማ ፊልም ላይ አንድ ግልፅ ያልሆነ ነገር አለ፡፡ እርስ በእርሱ የሚጣረስ ማለቴ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ “ሽብርተኝነትን በተመለከተ ከአሜሪካ ጋር እንደጋገፋለን፤ መረጃ እንለዋወጣለን” ብለውን ነበር፡፡ ሆኖም በአኬልዳማ ፊልም ላይ ያየናቸው የአሸባሪዎቹ አለቆች ነዋሪነታቸው በአሜሪካ ነው፡፡ ይሄ ባለበት ሁኔታ እንዴት ሆነ ነው እንደጋገፋለን የተባለው? መረጃ መለዋወጥስ ማለት ምን ማለት ነው? መቼም እነ ኦሳማ ቢላደን አዲስ አበባ በሰላም የሚኖሩ ቢሆን ኖሮ፤ አሜሪካ እንኳንም ልትደግፈን፣ እንኳንም ብድር ልትሰጠን፣ እንኳንም... ገና ድሮ አፈር ድሜ አብልታን ነበር፡፡ እናም ይሄ ፊልማችሁን ተልካሻ ከአደረጉባችሁ ምክንያቶች አንዱ ስላልሆነ በሚቀጥለው ፊልም ላይ ብትጠነቀቁበት ይጠቅማችኋል በሚል ቅንነት ነው ያነሳሁት፡፡

የሆነ ሆኖ አቶ መለስ የፎከሩበት ማስርጃ ሄዶ ሄዶ መንግስትን መቃወም... ከሚል ሊዘል አልቻለም፡፡ ወይም ውሃ የሚቋጥር አይደለም፡፡ ይሄ ደግሞ ህገ-መንግስታዊ መብትን መግፈፍ ነው፡፡ ህገ-መንግስታዊ መብት ደግሞ ለአንዱ የሚነሳ፤ ለአንዱ የሚሰጥ አይደለም፤ ለሁሉም እኩል ነው፡፡ እነ አንዱአለም አራጌ በሰላማዊ መንገድ የመንግስት ለውጥ ያስፈልጋል ማለታቸው እና ያለፈው እሁድ በተደረገው ታላቁ ሩጫ ላይ የተሳተፉ 36ሺ ሯጮች፡- “ሳንፈልጋቸሁ ሃያ አመታቸሁ” እያሉ መቃወማቸው ልዩነት የለውም፡፡ የሯጮቹም መብት ነው፡፡ የእነ እስክንድርም መብት ነው፡፡ በተቀረ አኬልዳማ ላይም ሆነ አዲስ አበባን እንደ ባግዳድ ወይም ከዚህ ቀደም ተሰርተው ያየናቸው ፊልሞችን ስም እና ተዋናይ እየለዋወጡ ማሳየቱ ከደረሲው እና ከአዘጋጁ በቀር ማንንም አያሳምንም፡፡

እናም የሚሻለው፤ ለሀገራችን የሚበጀው በእሳት የጋየ ቤት እና መኪና፤ ወይም በፈንጅ የተበጣጠሰን የሰው አካል እያሳዩ ማስፈራራቱ ሳይሆን የፖለቲካ መፍትሄ መስጠቱ ነው፡፡ ብሔራዊ እርቅ እንጂ የደህንነት አባላትን ቁጥር ማብዛት መፍትሄ አይሆንም፡፡ የዶክመንተሪ ፊልምም ብዛት እንዲሁ መፍትሄ አይሆንም፡፡ ለዚህም ጥሩ አስረጅ እንዲሆን ከፕ/ር መስፍን ቀዳሚ ቃል ልጥቀስ፡፡

“ቁም ነገሩ ደቂቀ እስጢፋኖስ መሸነፋቸው አይደለም፡፡ ቁም ነገሩ እየተሰቃዩ መታገላቸው ላይ ነው፡፡ ለህገ አራዊት

አንበረከክም ማለታቸው ነው፡፡ በጣም የሚያስደንቀው ነገር አንድም የደቂቀ እስጢፋኖስ አባል ሲሞት ሞተ አለመባሉ ነው፡፡ ሰማዕትነቱን፣ ወይም ፣ገድሉን፣ ፈጸመ ይላሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ጥልቅ መልእክት ያለው ሆኖ ይሰማኛል፡፡ የሰው ልጅ ህይወት እንደ እንሰሳ ህይወት አይደለም፤ አላማ አለው፡፡ መልእክት አለው፡፡ ቁም ነገሩ ዓላማውን ወይም መልእክቱን መፈፀሙ ነው እንጂ መኖር ብቻ አይደለም፡፡ ሐሳብንና እምነትን እንደያዙ በነፃነት ማለፍ ሐሳብንና እምነትን አስረግጦ ከመኖር የተሻለ ነው ብለው የሚያምኑ ይመስለኛል፡፡ ለዛሬው ትውልድ ይህ ኃይለኛ መልዕክት ነው፡፡”

አ ዎ!ፕሮፌሰር ይሄ ለእኛ ትውልድ ሀይለኛ መልእክት ነው፡፡ “ታጋይ ይሞታል እንጂ፤ ትግል አይሞትም”ን የት ነበር የሰማሁት?

Page 15: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ደስታ ለማግኘት ስኬት አስፈላጊ ነው? (በኤፌሶን) ውድ ዶ/ር አድለር

ደስታ ለማግኘት ዓለማዊው ስኬት ግድ ይለናል? በኛ ማህበረሰብ ዘንድ ሰዎችን ስለስኬታቸው መመዘን የተለመደ ነገር እየሆነ

መጥቷል፡፡ ያንን ስኬት የምንመዝነው ደግሞ ሰዎቹ ሊያጠራቅሙ በቻሉት ቁሳቁሳዊ ሀብት ልክ ነው፡፡ ለራሳችን ስህተተኛ ጣኦት አቁመን ካልሆነ የሚገርመኝ ነገር ይሆናል፡፡ ለመሆኑ የሰው ልጅ ደስተኝነት ከቁሳቁሳዊ ስኬት አንፃር መታየት ያለበት ነገር ነው? ኢ.ዲ

ውድ ኢ.ዲ

ታስታውስ እንደሆነ ስለደስታ በተነጋገርንበት ምዕራፍ ላይ ደስተኝነት በቁንፅል የህይወት ገፅታ አይለካም ብለን ነበር፡፡ የሰው

ልጅ አርኪ ህይወት ለመምራት የሚያስፈልጉት መልካም ነገሮች ሁሉ የተካተቱበት ኑሮ ደስተኝነትን እንደሚገልፅ ተነጋግረናል፡፡ እንደ ስነ-ምግባራዊና አእምሯዊ ሀብቶች ሁሉ ዓለማዊው ሀብትም እነዚህ መልካም ነገሮች ውስጥ እንደሚካተት ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ሁሉም ሰው እንደሚረዳው መልካም የተባሉትን ነገሮች ሁሉ በገፍ ማግኘት ይቻላል፡፡ ይሁንና በተለይ ቁሳቁሳዊ ሀብት እየተብዛዛ በሄደ ቁጥር ከፍተኛ የስነ-ምግባር ችግር መሆኑ አይቀርም፡፡

የስኬት ጠቅላላ ትርጓሜ የሚያመለክተው ማንኛውም ግብ፣ ዓላማ ወይም ምኞት ከዳር እማድረስ ላይ ነው፡፡ ደስታ ይሰጠናል ብለን ጥረት ያደረግንለትን ነገር ካሳካን እኛ ውጤታማዎች ነን ማለት ነው፡፡ ነገር ግን አንተም ጠቆም እንዳደረከው አብዛኞቻችን ስኬትን የምንመለከተው ከቁሳቁሳዊ ሀብት አ ንፃር ብቻ እየሆነ መጥቷል፡፡ የስኬታማነት ፅንሰ ሀሳብ በእንዲህ ያለ ድምዳሜ በተገደበ ጊዜ ስኬት እንደ ደስታ ሊሆን አይችልም፡፡ ቁሳቁሳዊ ሀብት በራሱ አንድን ሰው ደስተኛ አያደርገውም፡፡ እንደውም ደስታ መሻቱን እንዳያሳካ እንቅፋት ሊሆንበት እንደሚችል ማወቅ ይገባል፡፡

ከጥንት አንስቶ እስከሰለጠነው ዓለም ድረስ ቁሳዊ ሐብት የነገሮች ሁሉ መጀመሪያና መጨረሻ እንደሆነ የተደመደመበትን አመለካከት ለማስፋፋት ተግተው ሰርተዋል፡፡ ነገር ግን እንደ አርስቶትል ያሉ ፈላስፎች እንዲህ ያለው ድምዳሜ እጅግ ጠባብና የተሳሳተ ገፅታ ያለው እንደሆነ ለማሳየት ጥረዋል፡፡ አርስቶትል በቅደም ተከተል ለመልካም ነገሮች ዋጋ ሲያወጣ ከአእምሯዊና ከባህሪያዊ ሀብቶች ስር የመጨረሻ ደረጃ ላይ ያስቀመጠው የአካል ፍላጐትን ከማሳካት ውጭ ፋይዳ የሌለውን ቁሳቁሳዊ ሀብት ነው፡፡

የአርስቶትል የሀብት ምዘና ገንዘብ፣ ፣እስካላጣኸው ድረስ አላስፈላጊ ነገር ነው፣ ከሚለው ነባር ብሂል ጋር የተጣጣመ ነው፡፡ ለመኖር ግድ የሚሉን ጥቂት አስፈላጊ ነገሮች አሉ፡፡ ግሩም የሆነ ኑሮ ለመምራት ደግሞ በህይወት መገኘት ግድ መሆኑን የሚያጣው የለም፡፡ ነገር ግን ግሩም አኗኗርን መምራት ደግሞ በህይወት ከመገኘት አልፎ የተጓዘ ነገር ነው፡፡ ቁሳቁስ ብቻውን በአግባቡ የተመራ ህይወትን ሊያስገኝ የሚችል አለመሆኑ መታወቅ አለበት፡፡

አርስቶትል ሁለት ዓይነት ሐብት ክምችት እንዳለ አስረድቶ በመካከላቸው ግልፅ ድንበር ያቆማል፡፡ የመጀመሪያው የሐብት ክምችት ለማንኛውም የቤት እመቤት በተለምዶ የሚታወቅ ነው፡፡ አንድን ቤተሰብ ባልተጋነነ ፍላጐት ለማኖር የሚያስችል በቂ ቁሳቁሳዊ ሀብት አለ፡፡ የተደላደለ ህይወት ለመምራት፣ ላልተጋነነ ምቾትና ድሎት መሰረት የሆነ አቅርቦት የመጀመሪያው አይነት የሀብት ክምችት ነው፡፡

ሌላኛው የሀብት ክምችት ደግሞ ገንዘብን ስለገንዘብነቱ ብቻ በማጠራቀም የተጠመደው ነው፡፡ አርስቶትል በትዝብት የቃኛቸው አንዳንድ ሰዎች የህይወት ነጠላ ግብ ብለው የሚያስቡት ..ያለ ገደብ በገንዘብ ላይ ገንዘብ ማከማቸትን ነው... በሰዎች ውስጥ ያለ የዚህ ዓይነቱ ዝንባሌ በአግባቡ ከመኖር ይልቅ ለመኖር ብቻ ጉጉት ከማሳየት ይመነጫል.. ይላል አርስቶትል፡፡ እነዚህ ሰዎች እንደሮማዊው ባለፀጋ ክሮሱስ ተሳክቶላቸው ሀብታም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን አሁንም ልክ እንደ ክሮሱስ ሁሉ ህይወታቸው ፍፃሜ ላይ የሚደርሰው እንደ ሶሎን ያሉ ጠቢቦች ያገኙትን ደስታ ስለምን ሀብታሞቹ እንዳላገኙት እያምሰለሰሉ በመገረም ይሆናል፡፡

እንደ አርስቶትል ሁሉ ፕሌቶም የራሱ ሀብትን የተመለከተ አቋም አለው፡፡ ..ሀብትን ስለሀብትነቱ የሚያጠራቅም ስስታም ሰው መጨረሻው በችግር የተሞላ ይሆናል፡፡.. ይላል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ..በተመሳሳይ ሁኔታ በከፍተኛ ደረጃ ጥሩ መሆንና በከፍትኛ ደረጃ ሀብታም መሆን አይቻልም፡፡.. የሚል አቋምም አለው፡፡ ይህ የፕሌቶ ድምዳሜ ..ሀብታም ወደ መንግስተ ሰማያት ከሚገባ ይልቅ ግመል በመርፌ ቀዳዳ መሹለክ ይቀላታል.. ከሚለው ከሀዲስ-ኪዳኑ ጥቅስ ጋር ተስማምቶ እናገኘዋለን፡፡

ነገር ግን እንዲህ ያሉ አስተያየቶች የሀብት ፍላጐቶች በሙሉ በራሳቸው የስህተት መንገዶች ናቸው ወደሚል እንዳይተረጐም መጠንቀቅ ያሻል፡፡ ስህተት ተደርጐ የሚወሰደው ሀብትን እንደ መጀመሪያም እንደ መጨረሻም ግብ አይቶ ተለግባራዊነቱ በሙሉ ትኩረት መንቀሳቀስ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የሚስተዋሉ ተግሳፆች የሰው ሐብት መመኘትና ስስት ላይ የሚሰነዘሩ እንጂ አጠቃላይ ሀብትን የሚመለከቱ አይደሉም፡፡ ብዙውን ጊዜ የስነ-ምግባር መዝቀጥን የሚያስከትለው ከፍተኛ የሀብት ማካበት ፍላጐት እንደሆነ ነብያትና ሃይማኖታዊ መዝሙራት በግልፅ አሳይተዋል፡፡ እንዲህ ያሉ ጉዳዮችን በግልፅ ከጠቀሱት ውስጥ ቅዱስ ጳውሎስን እዚህ ላይ ማንሳት ይቻላል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በቀጥታ የሀጢያት ሁሉ ስር ገንዘብ ነው አላለም፡፡ ያለው ..የገንዘብ ፍቅር የሰውን ልጅ ወደ ስነ ምግባር ጥፋት ያደርሰዋል.. ነው፡፡ ለቁስ ስኬት መናወዝ ለመንፈስ ውድቀት ይዳርጋል፡፡

Page 16: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ወንድም-ኢትዮጵያውያን እባካችሁ አትግደሉኝ! አትሰሩኝ! አታሳዱኝ! አናኒያ ሶሪ (የአውራምባ ታይምስ አዘጋጅ)

እኔም እናንተም የአንድ አገር ልጆች አይደለንምን? ታዲያ ስለምን ታሳድዱኛላችሁ? ስለምንስ ምክንያት ልትገድሉኝ ትሻላችሁ? መታሰሬስ ከቶ ምን ይረባችኋል? በእውኑ እኔን ለዚያውም ስጋዬን ገድላችሁስ ነብሳችሁ ሀሴት ታደርግ ዘንድ ይቻላታልን? ሰላማችሁስ ከናንተ ጋር አብራ የምትኖር ይመስላችኋል?

የፈጠረን አባታችንስ ደሜን ከናንተ እጅ ሳይሻ ይቀራልን? የንፁህ ሰው ደም በከንቱ ማፍሰስ ለልጅና ልጆቻችሁ እርግማንን

ከማውረስ በቀር አንዳች አይበጃቸውም፡፡ የግፍና የተንኮል መንገድም የኋላ ኋላ እናንተኑ ሳይጠልፍ አይቀርም፡፡ መልካም ህልሜንስ ስለምን ትፈሩታላችሁ? የኔ ህልም እኮ እናንተም፣ እኔም፣ ሁላችን ኢትዮጵያውያንም በፍቅር እና

በህብረት፣ በፀጋ እና በክብረት ተዋደን አንድ ሆነን እንድንኖር ብቻ ነው፡፡ ኢትዮጵያችን ለሁላችን ስትበቃ ሳለ ስለምን እንገፋፋለን? በዚች በተባረከች ምድር የተረገመና የተዋረደ ህይወት የምንኖረውስ መለኮታዊ-ትእዛዝ ሆኖብን ነው? ወይስ ካለማስተዋል? አሊያስ አውቆ-ከማጥፋት? እናንተ ፣፣መሪዎቻችን፣፣ እረኛ ሆናችሁ በምትጠብቋት አገር ይህ ሁሉ መከራ፣ ሙስና፣ የኑሮ ግብግብ፣ አድር-ባይነት፣ ማስመሰል ሀሰት እንዴት ሊነግስ ቻለ? በመንጋዎቻችሁ መካከልስ የጠላትነት ዘርን ከቶ ማን ዘራው? መተማመንና ፍቅራችንስ ወዴት ገባ? በህይወታችን ውስጥ የነበረውን ሰላምና በረከትስ የትኛው ሌባ ሰረቀው? ኑሮዋችንስ ስለምን በእንዲህ ያለ ውጥረት ተሞላ? የዜጐቻችን በመላው ዓለም መበተንስ የሚያበቃው መች ይሆን?

ይህን ሁሉ ተመልክቼ ባያስችለኝ፤ የህዝቡ እና የእኔ ጐደሎ-ህይወት መጨረሻው ቢያሳስበኝ ጊዜ ለመናገር ወደድሁ፡፡ ይሄ

ሀሳብ ከቀና ልቡና የፈለቀ እንጂ አንዳች እኩይ-ሀሳብ እንደሌለው በማምነው አምላክ እና በምወዳት አገሬ ስም በህይወቴም ጭምር እምላለሁ፡፡ አብረን መላ እንፈልግለት ዘንድ እንጂ አንድን ወገን ብቻ ተጠያቂ ለማድረግ ያለመ ሀሳብ አይደለምና ከቶም በዚህ ሀሳብ አትሸበሩ፡፡ የአንድ እናት ልጆች ስለሚኖሩበት ጐጆዋቸው መልካም ለማሰብ እና ለመወያየት፣ የኑሮዋቸውን ሰንኮፍ ለመንቀል፣ የወደፊታቸውን ዕጣ ፈንታ ለማቃናት ባንድ አብረው ቢመክሩ ሀጢያት እና ነውር የሌለበት የብልህ ተግባር ነው፡፡

በመሆኑም ህልሜን አትፍሩት፡፡ ይልቁንስ የናንተንም እውነተኛ አዲስ ራዕይ ንገሩኝና የፊቱን የማግለል፣ የአመፃ፣ የተንኮል፣

የጭቆና፣ የግፍ፣ የእብሪት መንገድ እርግፍ አርጋችሁ ትታችሁ ወደቀናው ጐዳና ተመለሱ፡፡ የፍቅር መቅደስ በሩ ሳይዘጋ በንስሃ ታጥበን በሙሉ-ዓይን እንተያይ፡፡ ከጥፋት መንገዳችሁ ዘወር በሉ፡፡ የፍረጃና የማሸማቀቅ፣ የመግፋትና ጥግ የማስያዝ፣ የማፈንና ልሳን የመዝጋት እኩይ ስትራቴጂ-ተብዬዎችን ትታችሁ ከልብ በሆነ መታደስ ተለወጡ፡፡ አማራጭ ህልሞችን አትጥሉ፡፡ ባለራዕዮችን አታሳዱ፡፡ ምሁራንና ልሂቆቻችንን ጥላሸት በመቀባትም ሆነ አለግብራቸው ስምን በመለጠፍ እርም አታርጉብን፡፡ ሁሉም ላገሩ ድርሻ እና መልካም ህልም አለው፡፡ ፣ከእኛ በላይ ለዚች ሀገር..፣ አትበሉ፡፡ ከናንተ በላይ ምልዐተ-ህዝቡ አለ፡፡ ከህዝቡም በላይ አምላኩ ሁሌም አለ፡፡ ፈሪሃ-ህዝብ እና ፈሪሃ-እግዚአብሔር በልቡናችሁ ይደር፡፡ የታናናሾችን ምክር አትናቁ፡፡ በብረታችሁ ብዛት አትታበዩ፡፡ "እግዚአብሔር ከተማን ካልጠበቀ ጠባቂ በከንቱ ይተጋል” እንደተባለ አልሰማችሁም?..

አሁን እናንተ የልጆች አባት፣ የቤተሰብ አስተዳዳሪ፣ የአገር መሪ ሆናችኋልና ከጠባብ የቡድን፣ የጐሳ፣ የብሔር፣ የቁስ ፍላጐት

ውጡ፡፡ ስላለፈው ታሪክ ብቻ ሳይሆን ስለወደፊቱ የልጆቻችሁ መፃኢ-ህይወት አብዝታችሁ ተጨነቁ፡፡ ትታችሁት ስለምታልፉት መልካም ስራ አስቡ፡፡ የእርቅን መንገድ እሹ እንጂ ለጠብ አትጋበዙ፡፡ ባለራዕይን አታሳዱ፡፡ አታሰድዱ፡፡

እመኑ እንጂ አትፍሩ! ውደዱ እንጂ አትጥሉ! ይቅር በሉ እንጂ አታቂሙ! ከቶም አትጠራጠሩ! እስካሁን ፈርተን፣ ጠልተን፣

ተበቅለን፣ ጠርጥረን ምን አተረፍን? አመፃን እና እልቂትን አይደለንምን? ታዲያ የጐጆዋችን ምሰሶ ስለምን ፈረሰ እያልን እንባችንን መዝራት ምን ይጠቅመናል?

ራዕይ ላይሞት ነገርስ ባለራዕይን ማሳደድ፣ ማጥመድ፣ መግደል ከቶ ምን ይረባናል? በቅናት ተነሳስተው ራዕዩን አጣጥለው

ወንድሞቹ የሸጡት ብላቴና የህይወታቸው መቆያ ሲሆን ላስተዋለ ሰውስ ባለራዕይ ወንድሙን ማሰደድ አገሩን ማስራብ እና ጠቢብ ማሳጣት አይሆንበትምን?

የክፋትን መንገድ ትተን ወደቀናው ጐዳና የምናዘነብለውስ መች ይሆን? ወንድሞቼ ሆይ፡- ወደእኔ ተኩሳችሁ ራሳችሁን ስለምን ትገድላላችሁ? እኔ እናንተ አይደለሁምን? ስለእኔና እናንተ እውነት

የምቃትት የምሟገት፤ በእኔ ውስጥ የሚጮህ በእናንተ ውስጥ ያረመመ ህሊናችሁስ አይደለሁምን? በምትተኩሱት ጥይት አካሌ ሲወድቅ ህሊናችሁ እንደሚንኮታኮት እውነት ሳታውቁት ቀርታችሁ ነው?

Page 17: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

መግደል ስራ አይደለም፡፡ በተለይ ደግሞ ወንድምን፤ በተለይ ደግሞ እህትን፤ በተለይ ደግሞ ዘመድን፤ በተለይ ደግሞ ጐረቤትን፤ በተለይ ደግሞ ወገንን፤ በተለይ ደግሞ ኢትዮጵያዊን፡፡ ይህ የዘላለም ፀፀት የሚያወርስ የሀጢአቶች ሁሉ የበላይ ሀጢአት ነው፡፡ ልክ እንደቃየል ሀጢአት..

ምንድነው ይህ የምሰማው ጩኸት? የወንድምህ ደም ከሩቅ ወደኔ ትጣራለች..፣ የሚል የአምላከ-ህሊና መለኮታዊ ድምፅ

ሲያስበረግጋችሁ ይኖራል፡፡ ይብላኝ እንጂ ለእናታችን እኔስ ለመሞት ዝግጁ ነኝ፡፡ እናንተም ግን በመግደሉ ከፀናችሁ የእናት-የአባታችን አምላክ ምህረት ያድርግላችሁ.. በሰው አገር በረሃ ከምሞት ግን በአገር ልጅ-እጅ መገደል ለኔ ክብሬ ነው፡፡ እጆቻችሁ ይባረኩ.. ህልም እና ህሊና ሁለቱም አይሞቱም እስከጊዜው ድረስ የጠፉ ቢመስሉም ህልም እና ህሊና ከቶ አይታሰሩም ሾልከው ይወጡ እንጂ በመስኮት በበሩም ህልም እና ህሊና ሩቅ አይሰደዱም ካገራቸው ከሰው ወዴትም አይሄዱም

በፍቅር እና በእውነት እፅፋለሁ! ምክንያቱም፡- ፍቅር ያለእውነት-ሽንገላ እውነት ያለፍቅር-ዱላ ናቸውና!

አንዲት ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

Page 18: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

የሞራል የበላይነቱ ሁሌም ከእኛ ጋር ነው! አቤል ዓለማየሁ /የአውራምባ ታይምስ ም/ዋና አዘጋጅ/

በኢትዮጵያ ሚሊኒየም የካቲት ወር የተመሰረተችው አውራምባ ታይምስ ጋዜጣ በየካቲት 2002 ዓ.ም ሁለተኛ ዓመቷን ስትደፍን የጋዜጣዋ ኤዲቶሪያል ቡድን አባላት ከጋዜጣዋ እና ከፕሬስ ነፃነት አንፃር የሚሰማንን ስሜት ስናሰፍር በኢትዮጵያ ፕሬስ ውስጥ ..ለከርሞ እንገናኝ ብሎ መመኘት እንጂ እርግጠኛ መሆን አይቻልምና ተመኘሁ፤ የከርሞ ሰው ይበለን.... ብዬ ነበር፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ያለፈበትን እና እያለፈበት ያለውን አሜኬላ የሚያውቅ ..ለምን እንደዚህ አልክ?.. ብሎ የዋህ ጥያቄ አያስቀምጥም፡፡ አምና ሶስት ዓመት ሲደፍነን ዘንድሮ መኖራችን ለከርሞ ለመገናኘታችን ማረጋገጫ እንደማይሆን በውስጥ ስንነጋገር እውን አራተኛ ዓመታችን እናከብር ይሆን? ሳንባባል አልቀረንም፡፡

አራት ዓመት ከደፈነው የጋዜጠኝነት ጉዞዬ ሦስቱን ዓመት ያሳለፍኩት አውራምባ ታይምስ ውስጥ ነው፡፡ እነዚህ ዓመታት በአገራዊ ስሜት አንድ ነገር ለማድረግ የዋተትንባቸው ናቸው፡፡ ጋዜጣዋንም ሆነ ጋዜጠኞቿን ለማየት የሚጠየፉ፣ ድርጅታቸውን እና ስማቸውን ስላነሳን ከኩርፊያ በላይ ጥላቻቸውን በተለያየ መንገድ የሚነግሩን ቢኖሩም አካሄዳቸው ሳያስበረግገን እድሜ ከመቁጠር ባለፈ ጉዞ አድርገናል፡፡

ደረሰብን ባሉት ጫና ሳቢያ በአዘጋጆቹ ከአገር መሰደድ ሳቢያ ከ110 ሳምንታት በላይ መዝለቅ ያልቻለው አዲስ ነገር ጋዜጣ መዘጋትን አስመልክቶ የዛሬ ሁለት አመት ገደማ ..አዲስ ነገር ማጣት.. በሚል ርዕስ ባሰፈርኩት ሰፊ ሀተታዊ ፅሁፍ ላይ ለግብዓትነትም ሆነ ኢ-መደበኛ በሆነ መልኩ አግኝቼ ያናገርኳቸው አውራምባ ታይምስ ቀጣይዋ ተሰናባች መሆኗ እንደማይቀር በመገመት ይህ እንዳይሆን እንደሚመኙ ይነግሩን ነበር፡፡ ምኞታቸው ግን ሳይሰምር ቀረ፡፡ ለአዲስ ነገር የፈሰሰው እንባ አውራምባ ታይምስንም አጥቧት ሄደ እንጂ አላስቀራትም፡፡ መንግስትን ተቺ የነፃ ፕሬስ እድሜ መርዘም የሁሉም ወገን ጥርጣሬ በመሆኑ የአውራምባ ታይምስ አንባቢያንም ሆኑ የጋዜጣዋ ባልደረቦች አንድ ቀን ሊያጧት እንደሚችሉ ቢያውቁም ድንገተኛ የግድ ስንብቷ ግን ሁላችንንም ከልብ ማስደንገጡ አልቀረም፡፡ ጉዟችንን በመጠኑ ልፈትሽ፡፡

ቲም አውራምባ ከቤተሰብ በላይ..

የአውራምባ ታይምስ የጋዜጠኞች ቡድን (Team Awramba) የቤተሰብ ያህል የተዋሃደ ነው፡፡ ብዙዎቻችን ከስራ በኋላ እና

በእረፍት ቀናት እንኳን የምናሳልፈው በጋራ ነው፡፡ አርብ ማተሚያ ቤት መግቢያ ቀን በመሆኑ ስራዎችን ለማጠናቀቅ በሚደረገው ሩጫ (ውጥረት) አዕምሯችን ስለሚዝል ቅዳሜ እና እሁድ ከስራ ወሬ (አስተሳሰብ) በፀዳ መልኩ ..ዘና.. ብለን ሰኞ ወደ ስራ እንደምንመለስ ..ፎክረን.. የተለያየንባቸው ጊዜያት በርካታ ቢሆኑም ተሳክቶልን አያውቅም፡፡ ቅዳሜ በማለዳ ስልክ ተደዋውለን ገበያ ላይ ስለዋለችው አውራምቢት (እንደ ዋና አዘጋጃችን ፍፁም ማሞ አጠራር) የይዘት ሁኔታ የጀመርነው ወሬ ወደ ቀጣይ ወሬ ይከተንና ተገናኝተን መደምደሚያ እንድናበጅላት ያደርገናል፡፡

አብረን በምንቆይባቸው ሰዓታት ሁሌም ከአውራምባ ታይምስ ኤዲቶሪያል ፖሊሲ እና የአምድ ሁኔታዎች አንፃር የምናያቸውን (የሰማናቸውን) አገራዊ፣ ተቋማዊና ግለሰባዊ ህፀፆች እንዲታረሙ መፍትሄ አመላካች ፅሁፍ ስለማሰናዳት፣ መልካም፣ ወቅታዊ እና ትኩረት የሳቡ ጉዳዮች ላይ ሽፋን ሰጥተን ለቅዳሜ ለመዳር እናወራለን፤ መጠነኛ ኤዲቶሪያል ስብሰባ ልትሉት ትችላላችሁ፡፡

ግላዊ ወጋችን እንኳን ማዋዣው አውራምባዊ (ጋዜጠኛዊ) ይዘቱን ስለማይለቅ አብሮን የተቀመጠ አዲስ ሰው ..ሌላ ርዕስ አያውቁምን?.. እስከሚል ድረስ ወሬያችን ምንችክ ሊለው ይችላል፡፡

በተለያየ ወቅት አውራምባ ታይምስን የተቀላቀሉ ዘመደ ብዙ ባልደረቦቻችን እንኳን ከጋዜጣ ስራ እና ከባልደረቦቿ ጋር የሚፈጥሩት ቁርኝት ጠንካራ መሆን ..እዚህ ጋዜጣ ላይ ስራ ከጀመርክ ጀምሮ ምነው ዘጋኸን?.. ባዮችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማፍራት ይገደዳሉ፡፡ አድሮ፣ ሌሊቱን አጋምሶና አምሽቶ ጋዜጣዋን በሁለገብነት ለማገልገል ጉልበቱን የሚሰስት ስብስብ አልነበረም፡፡ ከጓደኛ፣ ቤተሰብና ወዳጅ (በጥቅሉ ከማህበራዊ ግንኙነት ማለት ይቻላል) ርቀን ትንሿን ዓለም ጋዜጣዋ ዝግጅት ክፍል ውስጥ መስርተን ስለ አውራምባ ታይምስ ኖረናል፡፡

ለጋዜጣዋ ያለንን የባለቤትነት አስተሳሰብ (Ownership Mentality) ተመልክተው ተቀጣሪ ሳይሆን የድርጅቱ ባለትልቅ አክሲዮን ባለቤት አድርገው የሚያስቡን ቁጥራቸው ቀላል አይደለም፡፡ ..አበዛችሁት.... ብለው የታዘቡን እስኪፈጠሩ ድረስ ሀሳባችንን ሰብስበን ለአውራምቢት በመስራት የጋዜጣዋን እድሜ ለማርዘም ታግለናል፤ያሰብነውን ያህል ሳይሳካልን ቀረ እንጂ፡፡

..ህይወቴ ፕሬስ ነው.... ብለን መንገዳችንን ስንጠርግ አውራምባ ታይምስም በነፃነት የምንሰራበት ቤት መሆኑ በሂደት ከቤተሰብም በላይ የሆነ አንድነት ለመመስረት ምክንያት ሆኖናል፡፡ ትልቅ ኢትዮጵያዊ ራዕይ አንግበን የአገር እና የህዝብ ድምፅ ለመሆን መታገላችንን ከእናንተ ከአንባቢያን የበለጠ ማንም ሊናገር አይችልም፡፡ ይህ ቡድን በጋራ መለያችን አውራምባ ታይምስ ስም አለመቀጠሉ ከምንም በላይ የሚያስቆጨን ለህዝብ የቆመ ..አራተኛው መንግስት.. የሚባለው ሚዲያ አንድ አካል ሩጫ በመሰናከሉ ነው፡፡ ይህን ሀዘን ለአገሩ የሚቆረቆር ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚጋራው ነው፡፡

የጋዜጣው ባልደረቦች በአውራምባ ታይምስ ላይ የነበረን ቆይታ ለእንቅፋቶች ሳንበረከክ የህይወታችን መልካሙን ጊዜ የከወንንበት ወቅት በመሆኑ ..እንኳንም የአውራምባ ታይምስ አባል ነበርኩ.... ስንል የምናስታውሰው ይሆናል፡፡ ቪቫ ቲም አውራምባ...... ማን ሊነጥቀን..?

መንግስትን የሚተች ጋዜጣ መጨረሻ ምን ሊሆን እንደሚችል ከታሪክ የምናውቀው ቢሆንም በባልደረባችን እና የጋዜጣው

አሳታሚ ብሉ ጱርዝ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ አንዱ ባለአክሲዮን ዳዊት ከበደ መሰደድ ሳቢያ የአውራምባ ታይምስ መቆም ብዙዎችን አስደንግጧል፡፡ ..ሞት አይለመድም.. አይደል የሚባለው?

Page 19: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

(Team Awramba) በጋዜጣዋ ላይ የነበረን ቆይታ እሾኽ የበዛበት ቢሆንም የአቅማችንን ያህል ባይሆንም በተወሰነ ደረጃ አበርክቷችን በዘርፉ ሊታወስ የሚችል መሆኑን እናስታውሳለን፡፡ አውራምባ ታይምስ ለፕሬስ ነፃነት ያበረከተው አስታዋፆ በዘርፉ ታሪክ ሊታወስ የሚችል መሆኑን እናስባለን፡፡ አውራምባ ታይምስ እና ፍትሕን መረጃ እንደሚነፍገው የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስቴር ሁሉ ማህበራዊ፣ ኪነ-ጥበባዊና ስፖርታዊ መረጃዎችን የሚያቀብሉ ተቋማትም ሳይቀር ለአውራምባ ታይምስ መረጃ ለመከልከል አያመነቱም ነበር፡፡

ይህም አገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ለመፃፍ የምናደርገው ጥረት ሙሉ እንዳይሆን አድርጓል፡፡ በፍርሃት ቆፈን የተቆለፉ ..የግል.. ድርጅቶችም ከእኛ ጋር ተቋዋሚ አሰራር ለማድረግ የነበራቸው ፍራቻ ያለንበትን ነባራዊ ሁኔታ የሚያሳይ ነው፡፡ በጥቅሉ ብዙዎች ለመኖር ሲሉ የሚያተርፉ እየመሰላቸው በአገራችን ያገሉን ነበርና ..እውነት ግን ይህ አገር የማነው?.. የሚል ጥያቄ በዳዊት ብቻ ሳይሆን በሌሎቻችንም ውስጥ ማቃጨሉ አልቀረም፡፡

ይህ ሁሉ ሆኖ ግን የብዙ ድምፅ አልባዎች ድምፅ ስለሆንን ደስ ይለናል፡፡ ብዙዎች የፍትሕ እና የሕግ አካል ይመስል ወደ እኛ መጥተው እንባቸውን እንድንጠርግ ያለቅሱ ነበር፡፡ ብሶታቸውን እንድንሰማ እኛን አምነው በመምጣታቸው ደስ ቢለንም የስራ ጊዜያችንን መሻማቱ ግን አይቀሬ ቢሆንም የቻልነውን ያህል ለማስተናገድ ሞክረናል በማስረጃ የታገዙትን ተቀብለን የሚመለከተውን አካል በማነጋገር በጋዜጣችን ላይ እናስተናግድ የነበረ ሲሆን ..ተጠየቅ?.. ብለን ለመሞገት በ..መረጃ..ነት ማለፍ ያልቻሉትን ግን ወዴት መሄድ እንዳለባቸው ስንጠቁም ኖረናል፡፡

አንዳንዶች ጋዜጣዋ የተቋቋመችው ገዢው ፓርቲ እና መንግስትን ለመተቸት ብቻ ስለሚመስላቸው በማስረጃ ያልደረጀ መረጃ ብቻ ይዘው በመምጣት መንግስትን ያብጠለጠሉበት ፅሁፍ አውራምባ ታይምስ ላይ ካልተስተናገደ አዝነው ለህዝብ እንዳልቆምን አድርገው ቢያስቡንም የጋዜጠኝነትን መርህ ባለመረዳት መሆኑ ሰለሚገባን ቅር ብሎን አያውቅም፡፡

የጋዜጣዋ ቡድን አባላት የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት (ደጋፊዎች) አድርገው የሚያስቡ ብዙ ስህተተኞችም አሉ፡፡ በሳምንታዊው ኤዲቶሪያል ስብሰባችን ላይ አንድም ቀን ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ስለማጠናከር ያወራንበት ጊዜ የለም፡፡ ኢህአዴግ ገዢ ፓርቲ በመሆኑ ከሌሎች ፓርቲዎች በላቀ የአገሪቷን የጉዞ አቅጣጫ ስለሚወስን ትኩረት ስለሚያገኝ በዙሪያው ያሉ ችግሮች ደግሞ እንዲታረሙ መተቸት ፀረ-መንግስት ሳይሆን ..አገር አቅኚ.. የሚል ስም የሚሰጥበት ቀን እስኪመጣ ለሚረዱን ..የማንም ደጋፊ አይደለንም.. ማለትን ብቻ እንሻለን፡፡ የአንድ ታዋቂ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር በፓርቲያቸው ዙሪያ በአውራምባ ታይምስ ላይ ሲቀርቡ የነበሩ የሀሳብ ፍትጊያዎች ስላላስደሰታቸው ..እኛኮ ጋዜጣችሁን የምንጠራው አውራምባ ሳይሆን አውሬ አምባ ብለን ነው.. ሲሉ የነገሩንን አስታውሳለሁ፡፡ ይህም ትችት መሰንዘር በአገራችን አሉታዊ ታርጋን እንደሚያስለጥፍ አመላካች ነው፡፡

ይህ ቢሆንም ቅሉ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ፣ ኪነ-ጥበባዊ፣ ስፖርታዊና ሌሎች ጉዳዮች ላይ የሞራል የበላይነታችንን ስናስደፍር ያሉ እውነታዎችን ስንጠቁም የተጓዝንበት እድሜ አጭር ቢሆንም አንባቢዎች ይሰጡን የነበረው የማበረታቻ አስተያየት ረዥም እድሜ የቆጠሩትን የሚያስከነዳ በመሆኑ ስራችንን በፍላጐት እንድንሰራ አግዞናል፡፡

እድሜ ለመቁጠር፣ ባለሀብትን አጉልቶ ፍርፋሪ ለመልቀም፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ለማፈራረስ እና ለመፈረካከስ፣ ሰውን ወንጅሎ ለማሳሰር ያዋልነው ገፅ እና የጨረስነው ቀለም ሳይኖር ከጨዋታው የግድ ስለወጣን ኩራት ይሰማናል፡፡ በእፍረት ከመኖር 194ኛ ሳምንት መቀጨት የተሻለ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ አንገት የሚያስደፋ ስራ ለአንድም ቀን ሰርተናል ብለን ስለማናምን አጐንብሰን ከመሄድ ነፃ ነን፡፡ አውራምባ ታይምስ ብትቆምም የሞራል የበላይነታችን ሁሌም ከእኛ ጋር ነው፡፡

ክብር-ክብር ለሚገባቸው! ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!

Page 20: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

“የኢትዮጵያ ጦር ዳግም ወደ ሶማሊያ ምድር” መግባትና ፖለቲካዊ አንድምታዎቹ “የኢትዮጵያ ጦር ዳግም ወደ ሶማሊያ ዘልቆ ገባ” BBR, New York Times...ሌሎችም

“አንድም የኢትዮጵያ ወታደር ወደ ሶማሊያ ዘልቆ አልገባም” የውጭ ጉዳይ ሚኒስነር ቃል አቀባይ ዲና ሙፍቲ በሙሉነህ አያሌው [email protected]

ባሳለፍነው ሳምንት ብዙም ትኩረት ካልሰጠንባቸው ጉዳዮች አንዱ የኢትዮጵያ ወታደሮች ዳግም ወደ ሶማሊያ ዘልቀው የመግባታቸው ጉዳይ ነው፡፡ ለምን ዳግም መግባት አስፈለጋቸው? በውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ትርፍና ኪሳራው ምን ሊሆን ይችላል? በርግጥ ወታደራዊው ዘመቻ የታለመለትን ውጤት እያስመዘገበ ነው? ወይንስ? ካለፈው ውጤት ምን ተምረናል? እነዚህ ሁሉ የፖለቲካ አንድምታ ያላቸው ጥያቄዎች የወታደሮቹን በርግጠኝነት ዘልቀው ገብተው ከሆነ እና ዘመቻውን የሚቀጥሉበት መሆኑ ከተረጋገጠ ሊታዩና ሊጤንባቸው የሚገቡ ወቅታዊ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በርግጥም ከኢትዮጵያ መንግስት ውጭ የአሜሪካ መንግስትም የጉዳዩን እውነትነት አረጋግጠው የተሰማቸውን አስተያየት ሲሰጡ ተስተውለዋል፡፡

ለምን ሶማሊያ?

Abdul Mohammed “Ethiopian’s strategic dilemma in the horn of Africa” በሚለው ፅሁፋቸው ላይ በተለይ

የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ በሶማሊያ ላይ ያላቸው አቋም ከሌሎቹ የተለየ ነው ይላል፡፡ ለዚህም በዋነኝነት ሶስት ምክንያቶችን ያስቀምጣል፡፡

የመጀመሪያው ምክንያት በሁለቱ ሀገራት መካከል ለረጅም ጊዜ የቆየ የግዛት ይገባኛል ጥያቄ ሲሆን በተለይ ኦጋዴን እየተባለ የሚጠራው አካባቢ ሶማሌዎቹ በጉልበት እንደተነጠቁ አድርገው በማሰባቸው ምክንያት ለረጅም ጊዜ በሁለት ሀገራት መካከል ጠላትነቱና ጦርነቱ እንዲዘልቅ አድርጐታል፡፡

ሁለተኛው የኢትዮጵያ ፍራቻ ዳግም የታሊባን አይነት አስተዳደር በሶማሊያ ሊመሰረት ይችላል ከሚል የሚመነጭ ነው፡፡ ይህ አይነት አስተዳደር እንደ አልቃይዳ ላሉ አሸባሪ ቡድኖች ጥላ ከለላ በመሆን ለሀገር ደህንነት አስጊ መሆኑ ነው፡፡

በሶስተኝነት የሚያስቀምጠው ደግሞ የኤርትራ መንግስት በሶማሊያ በኩል ኢትዮጵያ ላይ እያከናወነ ያለውን የውክልና (Proxy) ጦርነት በተዘዋዋሪ ለማዳከም ሲባል ኢትዮጵያ በሶማሊያ ጉዳይ ወጥ የሆነና በተጠንቀቅ የሚያስቆም ፖሊሲ አላት ይላል፡፡

ሰላም አስከባሪ ሲባል?

የሰላም አስከባሪ ጦር በታሪክ ሁለት ምዕራፎችን አሳልፏል፡፡ በቀዝቃዛው ጦርነት (Cold war) እየተባለ በሚጠራው ጊዜ

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሰላም አስከባሪ ጦር ዋነኛው ተልዕኮ የነበረው በሁለቱ ኃያላን ሀገራት ርዕዮተ-አለም (Ideology) ፍጥጫ ምክንያት ይከሰቱ የነበሩትን ጦርነቶች መሀል ገብቶ የመገላገል ሚና የነበረው ጊዜ ሲሆን በተለይ ከአሜሪካ ንግድ መአከል ንቃት በኋላ ግን ..ሽብርተኝነትን ለመዋጋት.. በሚል መርህ ሰላም አስከባሪ ጦር አንዱን ወገን በማጥቃት ላይ እየተመሰረተ እንደመጣ john Burton “The contribution of critical theory to new thinking on peacekeeping” በሚለው ከሌሎች ፀሐፍት ጋር በጋራ ባሳተሙት መፅሐፍ ላይ ይገልፁታል፡፡ በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ጦር በላይቤሪያ ወይም በዳርፉር የሚያካሂደው ተግባርና በሶማሊያ የሚያደርገው የተለያዩ ናቸው፡፡ በሌሎቹ የአፍሪካ ሀገራት ላይ የማረጋጋት ስራን ሲሰራ በሶማሊያ ግን አንዱን ቡድን ለመከላከል ሌላውን ማጥቃት የሚለውን መርህ ይከተላል፡፡

ካለፈው ጦርነት ምን አተረፍን?

የሐስብ York Times ዘጋቢ የሆነው Jeffrey Gehlemen ባሳለፍነው ሳምንት ከ800 በላይ የሚሆኑ የኢትዮጵያ ወታደሮች

የሶማሊያን ድንበር ዘልቀው መግባታቸውን ዘግቧል፡፡ ይህንን ተከትሎ በአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት የአፍሪካ ጉዳዮች ፖሊሲ አውጪ የሆኑት ጆኒ ካርስን የኢትዮጵያን ዳግም ወደ ሶማሊያ መዝለቅ አጥብቀው እንደሚቃወሙ የገለፁ ሲሆን ..ኢትዮጵያ ከአራት አመታት በፊት ለሁለት አመት ተኩል ያህል በሶማሊያ ያደረገችው ያልተሳካ ጦርነት ይበልጥ ጅሃዲስቶቹን ያጠናከረ ነበር.. ሲሉ የአሁኑን ቀጥተኛ ተሳታፊነት ይቃወማሉ፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በአሜሪካ የመንግስት አስተዳደርና ዴሞክራሲ ላይ ኤክስፐርት ናት የምትባለው E.Burton ኢትዮጵያ ወታደሮች በሶማሊያ ያደረጉት ቆይታ ..ሁለት ቆሻሻ አመታት.. ትላቸዋለች፡፡

ከመስከረም 2001 (እ.ኤ.አ) ጥቃት በኋላ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአልቃይዳ መሸሸጊያ ናቸው ባላቸው የደቡብ ሶማሊያ ግዛት ያደረገው የተጠናከረ አሰሳ አንዳችም ፍንጭ እንዳላገኘ ዘግቧል፡፡ በዚህ ወቅት የወጣው ሪፖርትም የሚያመላክተው ከተለያዩ የተከፋፈሉ አንጃዎች በስተቀር ሶማሊያ ውስጥ ይህንን ያህል ስጋት ሊሆኑ ይችላሉ የሚባሉ ቡድኖች አለመኖራቸውን ይፋ አድርጐ ነበር፡፡ በዚህ ወቅት እስላማዊ ቡድኖች ከራሳቸው ጐን በስተቀር በህዝቡ ዘንድ የነበራቸው ቅቡልነት ዝቅተኛ እንደነበር ይታወቃል፡፡

Page 21: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

እ.ኤ.አ 2005 የኢትዮጵያ መንግስት በአሜሪካ አጋዥነት የወሰደው እርምጃ በሶማሊያ የነበሩትን የጁሃዲስቶን እንቅስቃሴ በእጅጉ የቀየረ እንደነበር Markus virgil “Counter terrorism in Somalia” በሚለው ፅሁፋቸው ይገልፁታል፡፡ እንደ እርሳቸው አገላለፅ ከሆነ የፀረ-ሽብርተኝነት /Counter terrorism/ ዘመቻው ለጂሀዲስቶች ሰፊ ህዝባዊ ድጋፍ እንዲያገኙ በእጅጉ ከመረዳቱም በተጨማሪ ከህዝቡ ጋር በመቀላቀል በኢትዮጵያ ጦር ላይ በሚከፍቱት ደፈጣ ውጊያ ውጤት እንዲያስመዘግቡ ረድቷቸዋል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት በጊዜው ህዝባዊ መሰረት ነበረን ቢልም እውነታው ግን ከዚህ የራቀ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ እጣ ፈንታ አሜሪካ በአፍጋኒታንና በኢራቅ ከደረሰበት ሽንፈት ጋር ያያይዙታል፡፡ በተለይ በአሁኑ ጊዜ የኬንያ ጦር ሶማሊያ መግባቱን ተከትሎ የተለያዩ የኬንያ ሚዲያ ተቋማት ለመንግስታቸው ኢትዮጵያን እንደምሳሌ በማሳየት ከድርጊቱ እንዲቆጠብ እያስጠነቀቁ ይገኛሉ፡፡ ጠ/ሚ መለስ ዜናዊም በፓርላማ ቀርበው በጊዜው ስለደረሰብን ጉዳትና ስለሞቱ ወታደሮች ሲጠየቁ ..ይህንን ለፓርላማው የማሳወቅ ግዴታ የለብኝም.. ያሉበት አንዱ ምክንያት ከጦርነቱ ያለማትረፋችን እንደሆነ ይታወቃል፡፡ አሁን ምን አዲስ ነገር ተገኘ?

የቢቢሲው (BBC) ዘጋቢ Mohammed Adow “Why Ethiopia is on war footing” በሚለው ፅሁፍ ላይ ..ሶማሊያ

ለኢትዮጵያ ምን ያህል ለደህንነት አስጊ ልትሆን እንደምትችል በአሁኑ ጊዜ በሚገባ ሊያውቁ የሚችሉት ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ብቻ ናቸው.. ብሏል፡፡

ጠ/ሚኒስትሩ ደርግን ለመጣል በታገሉበት ጊዜ ለረጅም አመታት ሞቃዲሾ መቆየታቸውን ያስታወሰው መሐመድ ስልጣን ከያዙ በኋላ ከሶማሊያ ጋር መልካም የሚባል ጉርብትና ይመሰርቱ ዘንድ ምን አይነት አስተዳደር እንደሚያስፈልጋት ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ ይህንንም ለማድርግ የተቻላቸውን ከማድረግግ ወደኋላ እንደማይሉ ጨምሮ ገልጿል፡፡

በአሁን ወቅት የኢትዮጵያ መንግስት እንደ አዲስ ለመንቀሳቀስ የተነሳባቸውን ምክንያቶች የፖለቲካ ተንታኞቹ በሁለት ይከፍሉታል ፡፡

ሶማሊዎቹ ላለፉት 60 አመታት ታይቶ በማይታወቅ ድርቅ በተመቱ ጊዜ የእርዳታ እህል እንዳያገኙ መንገዱን ሁሉ የዘጋባቸው የአልሸባብ ተዋጊ ቡድን ላይ ቂም መያዛቸውና ህዝባዊ መሰረቱ የመናጋቱ አንዱ ሲሆን ሁለተኛው ከ9000 የአፍሪካ ሰላም አስከባሪ ጦር በተጨማሪም የኬንያ ጦር ወደ ግዛቱ መዝለቅ ነገሮችን ቀላል ስለሚያደርግ፤ በተለይ በወደብ ዙሪያ ከምታገኛቸው ሀገራዊ ጥቅሞች አንፃር ከኬንያ ቀድማ ለመገኘት ይሄ የማይታለፍ አጋጣሚ መሆኑን ይገልፃሉ፡፡ የኢትዮጵያ ዳግም ወደ ሶማሊያ መዝለቅ ሁሌም ቢሆን በአብዛኛው ሱማሌያዊ ዘንድ በመልካም የሚታይ ካለመሆኑ አንፃር ለወታደሮቻችን ጥንቃቄ ልናደርግ ይገባናል፡፡ ለማይረባ ነገር በደም እየገበርን የምንመለስበት ፖለቲካዊ ኪሳራ ሊኖር አይገባም፡፡ እኛም በግልፅ እየተካሄደ ያለውን የሀገራችንን ጉዳይ ከሌላ ሶስተኛ ወገን መስማት ያለብን አይመስለኝም፡፡ የሶማሊያ ያዕይን እማኞች አይተናል፣ ኮማንደሩ መጥቶ አነጋግሮናል፣ ከ24 የማይበልጡ ተሽከርካሪዎች ገብተዋል እያሉ ሲናገሩ የመንግስት ቃል አቀባይ የሚክዱበት ምክንያት እና ከዚህ የሚገኘው ፖለቲካዊ ትርፍ ግልፅ ቢሆን መልካም ነው፡፡

Page 22: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

አቶ መለስ “አዲሲቷ ኢትዮጵያ” እና የታሪክ ሽሚያው ዳንኤል ተፈራ የታሪክ ልሂቃን “ታሪክ ሽሚያ” የሚለው ሀረግ ዘርፈ ብዙ ትርጓሜ እንዳለው ይገልፃሉ፡፡ በትክክል የታሪኩ ባለቤት መሆን

የሚገባው ህዝብ፣ ግለሰብ ወይም ተቋም በተንሻፈፈ መንገድ የታሪኩ ባለቤት ሳይሆን ሲቀር ነው፡፡ የተከወነን መልካም ድርጊት በተለይም ህዝብ የተቀበለውን ጉዳይ ቦታው ላይ የተቀመጠውና የማይገባው አካል የራሱ መልካም ታሪክ አድርጐ በመጠቅለል ሲወሰድ የታሪክ ሽሚያ ይባላል፡፡

ይሄው የተንጋደደ አካሄድም ታሪክ እየተዛባና መስመሩን እየሳተ፣ ሌላ ታሪክ እየተፈጠረ የታሪክ ሽሚያው ይቀላጠፋል፡፡ ይሄ ብቸኛ ባለታሪክ ሆኖ የመውጣት ክፉ ልክፍት ነው ልንለው እንችላለን፡፡ ኢትዮጵያ ሀገራችን የስንት ዓመት እድሜ ባለፀጋ ናት? የሚል ጥያቄ ብናነሳ እንኳ በርካታ አስደናቂ የሆኑ መልሶችን እናገኛለን፡፡ ከአቶ መለስ አዲሲቷ ኢትዮጵያ እስከ ንቡረ ዕድ ኤርሚያስ የ7 ሺ ዓመት ባለቤቷ ኢትዮጵያ ድረስ እንሰማለን፡፡

በደፈናው የሶስት ሺ ዓመት እመቤት የምንላት ኢትዮጵያ እድሜዋን የአዜብ ንግስት ከሆነችው ንግስተ ሳባ ትጀምራለች፡፡ እድሜ ጠገብዋን ኢትዮጵያ የለም ኮረዳ ናት የሚሉና የአንድ አዛውንት እድሜ የሚቆጥሩም አሉ፡፡ የሄን መስማት የጀመርነው ግን ኢህአዴግ ይችን ሀገር ማስተዳደር ከጀመረ በኋላ ነው፡፡ ከወደ ህወሓት መንደር ብቅ የሚሉ አንዳንድ መጽሐፍት አስደንጋጭ ትንታኔ ይዘው ተመልክተናል፡፡ ይሄንን ወደ ህወሓት የሚያዘነብል ታሪካቸውንና ወዲያኛውን ታሪክ ለመቀበል የሚያንገራግር ፅሁፋቸውን ያለምንም መሳቀቅ ወደ ህዝብ ያቀርባሉ፡፡ እንግዲህ የታሪክ ተሻሚዎችን አፈ-ቀላጤያዊ ብዕር ተወት አድርገን እውነተኛውን መንገድ ከእውነተኛ ታሪክ ታዛቢዎች መጠበቅ ነው፡፡

ንቡረዕድ ኤርሚያስ ..ኢትዮጵያ የዓለሙ መፋረጃ.. በሚለው መጽሐፋቸው እንደውም ይች ሀገር ያላት እድሜ ሶስት ሺ ነው የሚለውን ባለመቀበል ወደ ሰባት ሺ ዓመት ያስጠጉታል፡፡ ለማስረዳትም የኦሪቱን ካህን መልከፃዲቅን ኢትዮጵያዊ እንደሆነ አስረጅ ነገሮችን ይዘረዝራሉ፡፡ ከንቡረዕድ ኤርሚያስ በመቀጠልም የ3ሺ ዓመት ታሪክ የሚለውን እናገኛለን፡፡ ከሶት ሺ ወደ መቶ ዓመት ታሪክ እንሸራተታለን፡፡ ከዚያ አልፎ ደግሞ እነሆ በኢህአዴግ ..አዲሲቷ ኢትዮጵያ.. የሚል እናደምጣለን፡፡ የታሪክ ፀሐፊዎችና ተመራማሪዎች ከተንጋደደ አስተሳሰብ እንድንወጣ ቢያንስ በጋዜጣ እንኳ አንድ ቢሉን ምኞቴ ነው፡፡ ቢያንስ ከመሬት ተነስተው የትናንት ነገስታትን ለምሳሌም አፄ ሚኒሊክን የሚዘልፍ የትናንት ልጆች፤ የዛሬ አባባዎች እንዳደታረሙ ይረዳል፡፡

የዛሬው ፅሁፌ ትኩረት ግን ..አዲሲቷ ኢትዮጵያ.. የሚለው ኢህአዴግ ሰራሽ ሀረግ ላይና አንዳንድ የታሪክ ሽሚያዎችን በጥቂቱ የሚዳስስ ይሆናል፡፡ አዲሲቷ ኢትዮጵያ የሚለውን ጉዳይ ሳስብ ግን በእውነት ኢትዮጵያ አዲስ ናትን? ኢህአዴግስ አዲስ ኢትዮጵያን ፈጥሯልን? እውነትስ አፋቸውን ሞልተው አዲሲቷ ኢትዮጵያ ይላሉን? የሚሉ ጥያቄዎችን ማሰላሰል የግድ ነበር፡፡ ባለቤትም መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ አዲሲቷ ኢትዮጵያ የሚለውን ከኢህአዴግ መንደር ብንሰማም ይፋዊ ማስረጃ ወይም ማረጋገጫ ለማግኘት እንቸገር ነበር፡፡ ሰሞኑን ግን አገኘሁ፡፡ ያውም ከራሳቸው ከአቶ መለስ፡፡

የብሔር ብሔረሰቦችን ቀን አስመልክቶ በኢቲቪ በተለቀቀው ማስታወቂያ በተደጋጋሚ እየታዩ ያሉት አቶ መለስ ..ሕገ-መንግስቱ የአዲሲቷ ኢትዮጵያ ምሰሶ ነው፡፡..... አሉ፡፡ ስለዚህ እነ አቶ መለስ አዲሲቷን ኢትዮጵያ እየፈጠሩ እንደሆነ እየነገሩን ነው፡፡ እውነት ኢትዮጵያ አዲስ ናትን?

ምናልባትም ከታሪክ ጋር ልናያይዘው አንችል ይሆናል፡፡ መንፈሱ ግን ኢትዮጵያን እንደ አዲስ እየፈጠሯት እንደሆነ እየነገሩን

ነው፡፡ አዲስ ነገር ሳናይ አዲስ ኢትዮጵያ እንዴት? ገዢው ፓርቲ በተደጋጋሚና አሰልቺ በሆነ ቋንቋ የሚነግረን የብሄር ብሄረሰቦች መብት መከበርን አዲስ ግኝት አድርጐ ነው፡፡

የብሔር ብሔረሰቦችን መብት ማክበርና በብሔር መከፋፈል የተለያዩ ናቸው፡፡ የብሔር ብሔረሰቦችን መብት ማክበር ተገቢና ትክክለኛ ሲሆን በብሔር /በዘውግ/ መከፋፈል አጥፊ ነው፡፡ ኢህአዴግ በተቃዋሚዎቹ ዘንዳ ከሚታማባቸው ጉዳዮች አንዱ ብሔራዊነትን በማደብዘዝ ብሔርተኝነት እንዲያድግ አድርጓል የሚል ነው፡፡ ይህም ስልጣን ከማቆየት ጋር የሚቆራኝ እንደሆነ የሚናገሩ በርካቶች ናቸው፡፡

ኢህአዴግ የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች ብቸኛ ፈጣሪና አክባሪ በመሆን ወደ ታሪክ ሽሚያ ቁልቁል ሲወርድ እናየዋለን፡፡ ለማነፃፀር ያመቸን ዘንድ በደርግ ጊዜ የነበረውን ሁኔታ መጥቀስ ተገቢ ነው፡፡ እነ አቶ መለስ ደርግን የብሔር ብሔረሰቦችን መብት እንደሚረግጥ ደጋግመው ይናገራሉ፡፡ በዚህ ዙርያ አንዳንድ ነጥቦችን አንስቼ እንዲነግሩኝ የጠየቅኋቸው ዶ/ር ኃይሉ አርዓያ ..በደርግ ጊዜ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ይባል ነበር አሁን የቀየሩት ስሙን ነው የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች በማለት.. ይላሉ፡፡

ዶ/ር ኃይሉ አያይዘው እንደነገሩኝ በኢሰፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽ/ቤት ውስጥ የተለያዩ መምሪያዎች ነበሩ፡፡ የድርጅት ጉዳይ፣ የፋይናንስ ጉዳይ፣ የታሪክና የባህል ጉዳይ፣ የብሔረሰቦች ጉዳይ መምሪያ የመሳሰሉት፡፡ በኋላ የኢትዮጵያ ህዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊካን ኢህድሪ) ይመሰረታል ስለተባለ ለዚህም ሕገ-መንግስት እንደሚያስፈልግ ታመነበት፡፡..

ዶክተሩ ቀጥለዋል ..ደርግ ህገ-መንግስት አፅድቆ ኢህድሪን ለመመስረት እናት እንደሚያስፈልግ አምኖበታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦችም በህገ-መንግስቱ መብታቸው እንዲረጋገጥ የብሔረሰቦች ጥናት የሚያስፈልግ ሆነ፡፡ በመቀጠልም በደርግ ጊዜ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ጥናት ኢንስቲትዩት ተቋቋመ፡፡.. ይላሉ፡፡ እኔን በጣም ያስደነቀኝ ግን ተቋሙ የተቋቋመው በሚኒስቴር ደረጃ መሆኑ ነው፡፡ ደርግ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦችን መብት ለማክበር በሚንስቴር ደረጃ የተቋቋመ መስሪያ ቤት ነበረው፡፡ ታዲያ ኢህአዴግ በኢትዮጵያ የብሔሮች ጥያቄ የተመለሰው በእሱ ብቻ እንደሆነ መናገሩ የታሪክ ሽሚያ እንጅ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል?

እባክዎ ዶ/ር ኃይሉ ይቀጥሉ... ..የኢትዮጵያ የብሔረሰቦች ጥናት ኢንስቲትዩት ተጠሪነቱ ለብሔረሰቦች መምሪያ ነው፡፡ ለዚህ ትልቅ ተቋም የተማሩ ሰዎች ያስፈልጉ ነበርና አብዛኛዎቹ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና ከተለያዩ መስሪያ ቤቶች ተሰበሰቡ፡፡ በዝርዝርም የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ታጠኑ፡፡ ያውም ለአምስት አመት ለአብነትም የብሔረሰቦችን ታሪክ ዶ/ር ላጰሶ ጌታሁን ዴሌቦ (በነገራችን ላይ ዶ/ር ላጰሶ የአባታቸውን ስም ጌታሁን ብለው ፅፈው አያውቁም ጌ. ብቻ ብለው ይተውታል፡፡ ምናልባት ጌታሁን አማርኛ ስለሆነ ይሆን እንዴ?) የህጉን ጉዳይ ዶክተር ፋሲል ናሆም፣ የኢኮኖሚውን ዶ/ር እሸቱ ጮሌና ሌሎችም ሆነው የብሔረሰቦች ጉዳይ በዝርዝር ተጠና፡፡

Page 23: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

በእያንዳንዱ ዘርፍም ዳጐስ ያለ ጥራዝ (Document) ተዘጋጀ፡፡ በዚህ ጥናት ላይ ተመስርቶም የኢህዲሪ ሕገ-መንግስት ፀደቀ፡፡.. አመሰግናለሁ ዶ/ር ኃይሉ፡፡

ኢትዮጵያ ሕገ-መንግስት ፀድቆላት መተዳደር የጀመረችው ዛሬ አይደለም፡፡ ቀዳማዊ ኃለስላሴ ሁሉ ነገሩ የሳቸውን ፍፁም ስልጣንና አይነኬነት የሚያረጋግጥም ቢሆንም ህገ-መንግስትን ይፋ አድርጓል፡፡ እነሆ ህገ-መንግስቱም አዲሲቷን ኢትዮጵያ ፈጠረ ይለናል፡፡ ህገ-መንግስቱም ኢህአዴግ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰጠን በሚያስመስል መልኩ ይሰብከናል፡፡ ህገ-መንግስቱ የህጐች ሁሉ የበላይ መሆኑን ባናጣውም ማስፈራሪያ፣ የሚናድ፣ የሚደረመስና ልዩ ነገር አድርጐ ይሰልብናል፡፡ አቶ መለስ ደግሞ ..ሕገ-መንግስቱ የአዲሲቷ ኢትዮጵያ ምሰሶ ነው፡፡.. ይሉናል፡፡

እንዴ.. አዲሲቷ ኢተዮጵያ እድሜዋ ስንት ነው? በአቶ መለስ የስልጣን ዘመን ልክ ከሆነ 20 ዓመት መሆኑ ነው፡፡ ጉድ ፈላ.. ይሉሃል እንደዚህ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በሁለት ትከፈላለች አዲሲቷ ኢትዮጵያና አሮጊቷ ኢትዮጵያ፡፡ ገዥው ፓርቲ እንደሚለው ደግሞ አዲሲቷ ኢትዮጵያ ውስጥ ሁሉን ነገር አዲስ አድርጐ የመሳል ሁኔታ አለ፡፡ ዛሬ ላይ የደረሰችሁ ኢትዮጵያ አማረም ከፋም የብዙ ዓመትና የብዙ አባቶች ውጤት ናት፡፡ ለእነዚያ አባቶች ደግሞ ክብር መስጠት ተገቢ ነው፡፡ ልማት ዛሬ አልተጀመረም፣ መንገድ መስራት ዛሬ አልተጀመረም፣ ኢትዮጵያ የብዙ ብሔረሰቦች ሀገር መሆኗ ዛሬ የተጀመረ አይደለም፣ ህገ-መንግስትም ዛሬ አልተጀመረም... በጠቅላላው የተጀመረውን የማስቀጠል እንጅ አዲስ ነገር መጀመሩን እኔ አላውቅም፡፡ ሁሉን ነገር ጀማሪና ፈር ቀዳጅ ለመሆን የሚደረገው ሩጫም የታሪክ ሽሚያ አካል ሆኖ ይቀጥላል ማለት ነው፡፡ አንድ ነገር ግን እንደ እባብ ቆዳ አውልቀን መጣል የሚኖርብን ይመስለኛል፡፡ ለመገንባት ማፍረስ ሁሌም ላያስፈልግ ይችላል፡፡ የኛን ጥንካሬና መልካም ስራ ለማሳየት የግድ ሌሎችን ማንቋሸሽ አይጠበቅብንም፡፡ እኛ የሰራነው ስራ ብቻ መገምገም ይገባዋል፡፡ ኢህአዴግ ያለበት ችግር አንዱ ይሄ ነው፡፡ ስለልማት ለማውራት ከደርግ ውድቀት መጀመር አይጠበቅበትም፡፡ ከማንቋሸሽ የሚጀመር ስራ ሁሉ ፍሬ የማፍራት አቅሙ አነስተኛ ነውና፡፡ ምናልባትም ታሪክ የራሱን ፍርድም ይሰጣልና ጠንቀቅ ማለቱ ተገቢ ነው፡፡

Page 24: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

“የብሔር-ብሔረሰቦች ቀን” ያንቀላፋውን የማንት ቅስቀሳ ፍሬዘር ብርሀኑ የብሔር-ብሔረሰቦችን ቀን በምናከብርበት ዋዜማ የደበዘዘውን ኢትዮጵያዊ ብሔራዊ ስሜት መሰረት አድርገን አንዳንድ

እውነታዎችን እናያለን፡፡ ምንም እንኳን ፣ብሔራዊ ስሜት፣ ዓበይት ከሚባሉት የፖለቲካ ርዕሰ ጉዳዮች ጐራ የሚመደብ ፅንሰ ሐሳብ ቢሆንም ስለዚህ ፅንሰ ሀሳብ ዛሬ ላይ ቆመን ማውራት ፣የአልዓዛር፣ን ሙት አካል መለኮታዊ ባህርይ ባልተላበሰ ማንነት ከመቀስቀስ አይተናነስም፡፡ እስቲ ለራሳችን አንዳንድ መጠይቆችን በማንሳት ውይይታችንን እንክፈት፡፡ በእርግጥ ስንቶቻችን ፣ምንድነህ?፣ አሊያም ፣ከወዴት ነህ?፣ ለተሰኙት የማንነት ጥያቄዎች ፣ኢትዮጵያዊ፣ ወይም ደግሞ ፣ከኢትዮጵያ፣ በሚሉ ምላሾች አሰርን፡፡ ብዙዎቻችን ዛሬ ለእነዚህ የማንነት ጥያቄዎች ምላሾችን ፣በአባቴ/አባቴ፣ ከዚህ ወገን ፣እናቴ/በእናቴ፣ ደግሞ... እያልን ማጣቀሳችን የማይታበል ሐቅ ነው፡፡ የ፣ኢትዮጵያዊነት፣ ብሔራዊ ስሜት አሁን... አሁን በስፖርታዊ ክንውኖችና በኪነ-ጥበባዊ (ኢትዮጵያ ተኮር) ስራዎች ላይ ብቻ የሚንፀባረቅ እንደሆነ ጉልህ እውነታ ነው፡፡ ዘመናትን ተሻግረን ይህ ብሔራዊ ስሜት የተስተዋለበትን ክስተት ማጣቀሻ ካሻን ደግሞ አስራ አራት አመታት ወደ ኋላ ተመልሰን የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ይገባኛል ነፍጥ ያማዘዘ የውጊያ ታሪክ ሁነኛ ማሳያችን ነው፡፡ እናም ብዙዎቻችን በዘመነ ኢህአዴግ የ..አልፎ አልፎ.. ክስተቶች ላይ መሰረቱን የጣለውን ይህንን ብሔራዊ ስሜት ፣ለምን፣ ብለን ሳንጠይቅ አንቀርም፡፡ ለአንዳንዶች ብሔራዊ ስሜት ከሥርዓት ግንባታ፤ ለሌሎች ደግሞ ሥርዓቱ ከሚከተለው ርዕዮት ዓለም ጋር ጥብቅ ቁርኝት አለው ብለው ያምናሉ፡፡ ርዕዮት ዓለም /Ideology/ ጋር ያለው ቁርኝት ግን ያን ያህል ለሙግት የሚበቃ እሳቤ ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ ለዚህ ደግሞ ብሔራዊ ስሜታቸውን ከማንነታቸው ጋር በፅንሰ ሐሳብ ያስተሳሰሩ ምዕራባዊያንም ሆኑ የሌላ ክፍላተ ዓለም ህዝቦችን እንደማስረጃ መጠቀም ይቻላል፡፡ የአንድን መንግስትና የሥርዓት ግንባታ (እንደ የፌደራሊዝም መርሖች) እና ብሔራዊ ስሜት ያላቸው ቁርኝት ግን ፣የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታዎች፣ ሊያስብላቸው የሚበቃ ነው፡፡ ብዙ ሲባልለት የነበረውን ይህን የፖለቲካ መርሖችን ውጤትን ዙሪያ ማጠንጠን ምናልባትም ጠቅላይ ሚኒስትራችን አዘውትረው የሚጠቀሙባትን ፣የሞኝ ዘፋኑ...' የምትለዋን ተረት ሊያሰነዝርብኝ ይችላልና የፅሑፌን ጭብጥ የመንግስታችን ፣የሙት ማንነትን፣ን ቅስቀሳ መርሖችን ፍተሻ ላይ እንዲያውጠነጥን አድርጌአለሁ፡፡

..ብሔራዊ ስሜትን.. ያደበዘዘ ..ብሔርተኝነት..

ምንም እንኳን ፣ብሔራዊ ስሜት፣ የሚለው ሐረግ መሰረት ፣ከአመክንዮአዊነቱ፣ (Rational) ፣ስሜታዊነቱ፣ (Emotional)

ያጋደለ ይዘት እንዳለው ስያሜውም ጭምር ምስክር ቢሆንም ፣አመክንዮ ሊበጅለት ግን ፈፅሞ አይችልም፣ ማለት ግን አይደለም፡፡ እንደውም አመክንዮው የበለጠ ሚዛን የሚደፋ እስኪመስል ፣ስሜቱን፣ ምክንያት ማላበስ ይቻላል፡፡ ፣ብሔራዊ ስሜት፣ን (Nationalism) የሚለውን ሐረግ ኆየብሔራዊ ስሜት ፍልስፍና/ማሻስ philosophy of nationalism’ በተሰኘው መጽሐፋቸው የፍልስፍና ምሁር የሆኑት ፓል ጊልበርት ኆብሔራዊ ማንነትንና ብሔራዊ ተዓማኒነትን ቀዳሚ ትኩረቱ አድርጐ የተመሰረተ የፖለቲካ ዕሳቤነ ሲሉ ይፈቱታል፡፡ ሌላኛው የፍልስፍና እና ፖለቲካ ምሑር አርነስት ጌልነር ደግሞ ‘Nations and Nationalism’ በተባለው መጽሐፋቸው ብሔራዊ ስሜትን ኆየራስን ባህልና ትውፊት ከሌሎች የተለየና የበላይ (Superior) እንደሆነ አድርጐ ከማሰብ የሚመጣ የማህበራዊ ህይወት እውነታ፡፡ነ ሲሉ ይገልፁታል፡፡ ጌልነር አክለውም ለዚህ የማህበረሰብ ክፍል ዕሳቤ ማህበረሰቡን ያስተሳሰሩ እንደ ቋንቋ፣ ዘርና፣ የሚጋሩዋቸው ታሪኮች መፈጠር ዋነኛ ምክንያቶች እንደሆኑ ያስረዳሉ፡፡ በእርግጥ ብሔራዊ ስሜትን ተከትለው የተስተዋሉ አንዳንድ ታላላቅ ግድፈቶች ቢኖሩም የብሔራዊ ስሜት ጠቀሜታ አሁን ካለንበት እውነታ ጋር (የብሔራዊ ስሜት መቀዝቀዝ) ግን ለሚዛን የሚቀርብ አይደለም፡፡ ያም ሆነ ይህ ብቻ ኢትዮጵያውያንን የሚያስተሳስር ባህል፣ ትውፊትና የጋራ የሆነ ሺ ዘመናትን የተሻገረ ታሪክ አላቸው፡፡ በተቃራኒው ግን ፣ኢትዮጵያዊነት፣ የሚባለው እሳቤ ጨርሶ ጠፍቷል የሚያስብል ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ እንዲህ አይነቱ የብሔራዊ ስሜት መደብዘዝ ከቅኝ አገዛዝ በተላቀቁ የአፍሪካ ሀገራት ላይ እንኳን ከሚስተዋለው በላይ እጅጉን የባሰ እንደሆነ ለማንም ኢትዮጵያዊ ግልፅ ነው፡፡ቀዝቃዛ ብሔራዊ ስሜት አብዛኛውን የሚስተዋለው በቅኝ አገዛዝ ቀምበር ተጭኖባቸው በነበሩ ሀገራት ላይ እንጂ ቅኝ አገዛዝን አቃሎ በመሸኘት ከታሪክ ማህደር ራሳቸውን ባሰፈሩ ህዝቦች ዘንድ አልነበረም፡፡ ያለመታደል ሆኖ ሥርዓቱ ከብሔራዊ ስሜት ይልቅ ነጭ አምላኪነትን እና ምዕራባዊ ዓለም ናፋቂነትን አወረሰን፡፡ በብሔራዊ ስሜት ከመፋቀር ይልቅ የተጋራነውን ታሪክ፣ ባህልና ትውፊት ዘንግተን አንደኛችን ለሌላችን ባይተዋር እንሆን ዘንድ ..ብሔርተኝነት..ን አላበሰን፡፡ በእርግጥ ..ብሔርተኝነት.. ከማናችንም ጋር የሚገኝ የእኔነት ስሜት ቢሆንም አንድነትን ከሚያላብሰን ብሔራዊ ስሜት ገዝፎ ሲቀርብ ግን ብሔራዊ ስሜትን ሊፈጥሩብን የሚችሉ የባህልና የታሪክ አሻራዎችን ማደብዘዙ አይቀሬ ነው፡፡

ያንቀላፋ ማንነትን ቅስቀሳና ተቃርኖው

አስቀድሜ እንደገለፅኩት አንቀላፉ ያልኩት ማንነት ኢትዮጵያዊ ብሔራዊ ስሜትን ነው፡፡ ዛሬ የሚስተዋለውንም ፣ብሔራዊ

ስሜት፣ በመጽሐፍ ቅዱሱ ፣አልዓዛር፣ ሙት አካል ገልጨዋለሁ፡፡ ምክንያት አለኝ፡፡ ኢየሱስ የዓላዛርን መሞት በሰማ ጊዜ እንዳነባ የሚነግረን የሐዲስ ኪዳን ክፍል ኢየሱስ ለዓላዛር እህቶች ዓልዓዛር እንዳንቀላፋ እንጂ እንዳልሞተ ሆኖ ይነግራቸዋል፡፡ እናም ..አልዓዛር ተነስ.... በሚለው ቃል አልዓዛርን ዳግም ወደ ህይወት እንዳመጣው ይነግረናል፡፡ ይህንን የዓልዓዛርን እንቅልፍ ያንቀላፉ ብሔራዊ ማንነትን ነው አልዓዛር ስር የገለፅኩት፡፡ ታዲያ ይህንንም ማንነት እንደ አልዓዛር ማንቃት ይቻላል፡፡ በእርግጥም ኢህአዴግ ከዚህ እንቅልፍ ብሔራዊ ስሜታችንን ለመቀስቀስ የወሰዳቸው እርምጃዎች እንዳሉ ቢስተዋሉም በውስጣቸው ያዘሉት ተቃርኖ በበደነው ማንነት ላይ ህይወትን ይዘሩበት ዘንድ አልተቻላቸውም፡፡

ዋነኛ ተብለው ከሚጠቀሱ የኢህአዴግ ያንቀላፋ ማንነት ቅስቀሳዎች መካከል ፣የባንዲራ ቀን፣ እና ፣የብሔር ብሔረሰቦች፣ ቀን ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ትናንት ፣ጨርቅ፣ ተብሎ የተፈረጀን፤ ነገር ግን ቀን ተቆጥሮለት፣ ቀጠሮ ተይዞለት፣ አዋጅ ተነግሮለት ዛሬ ይከበራል፡፡ አንዱና ትልቁ ቁም ነገር ሊሆን የሚገባው የባንዲራ (የሰንደቅ ዓላማ) ቀን ስለታወጀና በአመት አንድ ጊዜ ተሰባስበን ሰንደቅ አላማችንን ስላሰቀልን የሰንደቅ ዓላማ ክብር በልባችን መልሶ ያቆጠቁጣል ማለት አይደለም፡፡ አሁንም ቢሆን ለባንዲራ ክብር ክስተት ተኮር ከመሆን (በባንዲራ ቀን ብቻ የሚታወስ) በዘለለ የባንዲራ ቀን ሊፈይድ የሚችለው ነገር አይኖርም፡፡

Page 25: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

የ..ነው-አይደለም.. ተቃርኖ ፣በብሔር ብሔረሰቦች፣ ማንነት

ይህኛው ፣ያንቀላፋ ማንነትን ቅስቀሳ፣ እንቅሰቃሴ በጉልህ ተቃርኖውን ያመላክተናል፡፡ በምክንያታዊ ዕሳቤ (Rational

thinking) መርህ አንድ ነገር ፣እውነት፣ አሊያም ፣ሐሰት፣ እንጂ እውነትም ሐሰትም ሊሆን አይችልም፡፡ ይህንን ተቃርኖ ለተነሳንበት ጭብጥ ማሳያ የሚሆነን የተለመደውና በልዩነት ውስጥ አንድነትን የሚያንፀባርቀው የብሔር ብሔረሰቦች መሪ ቃል (Motto) ነው፡፡

ይህን ስንሰበክ የኖርነውን መሪ ቃል ብንፈትሽ ከአንድነታችን ይልቅ ልዩነታችንን በጉልህ የፃፈና ከታለመለት ዓላማ አንፃር የተቃረነ ይዘት አለው፡፡ በልዩነታችን ውስጥ የሚያመሳስሉን ነገሮች ቢኖሩ እንጂ አንድ ሊያደርጉን የሚችሉ ነገሮችን መፈለግ ከተነሳንበት ልዩነት ከሚለው ጭብጥ ጋር ይጣረሳል፡፡ ፣ልዩነት፣ ብለን የፈረጅነውን ነገር ፣አንድነት፣ ብለን ማወጅን ነው እንግዲህ ተቃርኖ ስል የገለፅኩት፡፡ በተቃራኒው ደግሞ የዚህ ተገላቢጦሽ ይህንን የተቃርኖ ችግር ሲፈታው እናያለን፡፡ በሌላ ቋንቋ በአንድነት ውስጥ ያለ ልዩነት በእርግጥም ህብረ-ብሔራዊነትን ያመላክታል፡፡ አንድን ነገር ምሉዕ ሊያደርጉ የሚችሉ የተለያዩ አስተዋፅኦ ያላቸው አካላት ሊኖሩ እንደሚችሉ ሁሉ ፣ኢትዮጵያዊነትም፣ በብሔር ብሔረሰቦች ተዋፅኦ የሚፈጠር የማንነት መገለጫ ነው፡፡ የአድዋን ድል ስናወሳ ስለኢትዮጵያዊነት እያወራን ነው፡፡ ይህ ታላቅ የታሪክ አሻራ ደግሞ የብሔር ብሔረሰቦች ገድላት ተዋፅኦ እንጂ የአንድ ብሔር ገድል አይደለም፡፡ ስለአድዋ ድል ስናወጋ መነሻችንን ከተዋፅኦ ገድላት ካደረግን ማረፊያችን ሊሆን የሚችለው እነዚህን ገድላት ከሚያስተሳስር የታሪክ ፍፃሜ ይልቅ ገድላቱን በአንፃራዊ መልኩ የሚያሰፍር ባይተዋርነትን ሊፈጥር ከሚችል ፣ማንነት፣ ላይ ነው፡፡

ማጠቃለያ

በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ውስጥ የጥንቱ ብሔራዊ ስሜት በእርግጥም አንቀላፍቷል፡፡ ክስተቶችን ተከትሎ ብልጭ የሚልብንን ብሔራዊ ስሜት ወደ ጥንቱ ለመመለስ ኢህአዴግ እንደ እልባት የሚከተላቸው መንገዶች ፣ከእጅ አይሻል ዶማ፣ ቢጤዎች ናቸው፡፡ ፣የሰንደቅ ዓላማ ቀን፣፣ ፣የብሔር ብሔረሰቦች ቀን፣... ክብረ በዓላት ይልቁንም ፣ብሔራዊና ህብረ ብሔራዊ፣ ማንነታችን በታወጁ ቀናት ላይ ብቻ ከመወሰን በዘለለ የደበዘዘውን የአንድነት ስሜት በጉልህ ሲፅፍ አይስተዋልም፡፡ ተቃርኖን በሚፈጥር የብሔር-ብሔረሰቦች ልዩነትና አንድነት ላይ መሰረቱን የጣለ አመለካከት ይዘን በልዩነት ውስጥ አንድነትን ማስፈን አይቻልም፡፡ የማይካደው ሐቅ ትግሬው ከአማራው፣ አማራው ከኦሮሞው፣ እንዲሁም ደግሞ ኦሮሞው ከደቡቡ... ብቻ ብሔር ብሔረሰቦቻችን የተሳሰሩበት ባህልና ትውፊት፣ የሚጋሩት ታሪክ፣ የተወራረሱት ቋንቋ አለ፡፡ ይህ መጣመር ግን በልዩነታችን ላይ የሚቀኝ መሆን የለበትም፡፡ ይልቅስ ልዩነታችን ሊቀኝ የሚገባው አንድነታችንን መሰረት አድርጐ ነው፡፡ ቀለል ባለ አገላለፅ እርሱ ትግሬ፣ እኔ አማራ፣ እሷ ደቡብ... ብለን ከተፈራረጅን በኋላ መልሰን ደግሞ ፣አንድ ነን፣ ማለት ፣ከብሔርተኝነት፣ ባለፈ ፣ብሔራዊ፣ ፋይዳ የለውም፡፡ አንድነታችንን ቀድመን ያሰፈርንበት ህብረ-ብሔራዊነት ግን ልዩነታችን ያልተለየው ብሔራዊ ስሜትን በመፍጠር ረገድ ትልቁን ሚና ይጫወታል፡፡ ይህም ማለት ፣ኢትዮጵያዊነት፣ ለሚለው ቃል ከማንነት መገለጫነት በላይ ትርጉም ያለው የብሔር ብሔረሰቦች ተዋፅኦ መሆን ይጠይቃል፡፡ ለአንድ ሰው ህይወት የተለያዩ ብልቶቹ ምሉዕ ተግባራትና አሰታዋፅኦ እንደሚያደርጉት ሁሉ ከብልቶቹም የአንዱ መጓደል ሰውየውን ያበድነዋል፡፡ ፣ኢትዮጵያዊነትም፣ እንዲያ ነው፡፡ በልዩነት ውስጥ አንድነትን ሳይሆን በአንድነት ውስጥ ልዩነታችንን እንፈትሽ፡፡ እንዲህ ሲሆን ነው የጥንቱን ብሔራዊ ስሜት መመለስ የሚቻለው፡፡ በእርግጥ ብሔራዊ ስሜት ኢህአዴግ ቁብ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ላይሆን ይችላል፡፡ ግን ቁብ ሰጠነውም አልሰጠነውም ያለ ብሔራዊ ስሜት የሚታሰብ ልማት የሚታለም ግብ አይኖርም፡፡ የተወከሉ የብሔር ተወካዮችን የባህል ልብስ አልብሶ ቀነ ቀጠሮ በተያዘለት ቦታ ተሰብስበው ባህላዊ ጭፈራቸውን እንዲያሳዩ ማድረግ የብሔር ብሔረሰቦቻችንን የባህል ትስስርም ሆነ የጋርዮሽ ታሪክ ያስገነነዝባል ማለት አይደለም፡፡ ቸር እንሰንብት..

Page 26: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

የ “ልማታዊ መንግስት” እና የነፃ ገበያ ፍጥጫ ዘላለም ኪሮስ በቅርቡ የከተማ መሬት ባለቤትነት መብትን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ አንድ አዋጅ በመንግስት ታውጇል፡፡ በአዋጁ መሰረትም

የከተማ ቦታ ያላቸው የግል ባለንብረቶች (ባለመሬቶች) በሂደት ይዞታቸው ወደሊዝ የሚሸጋገርበት ሁኔታ እንዳለ ታውቋል፡፡ ይህ አዋጅ በኢህአዴግ ፓርላማ አባላት (ከአንድ ተቃዋሚ ፓርቲ አባል ተቃውሞ በስተቀር) እንዲፀድቅ ተደርጓል፡፡ አዋጁ እንዲፀድቅ ለፓርላማ በቀረበበት ጊዜ ሌሎች አዋጆች ለምክር ቤት ሲመሩ የጉዳዩ ባለቤቶች ሀሳባቸውን እንዲሰጡ እንደሚጋበዙበት መድረክ ዓይነት አልተፈጠረም፡፡ ኢህአዴግ በፓርቲው አጠናቆ የጨረሰው ጉዳይ በመሆኑና በህዝብ ዘንድ በተለይም በከተማ ቤት ባለንብረቶች በኩል ከፍተኛ ተቃውሞ ሊገጥመው እንደሚችል ግልፅ ስለነበር በተጣደፈ መልኩ በፓርላማው አባላት እንዲጸድቅ ተደርጐ አዋጅ ሆኖ ወጥቷል፡፡ በመሰረቱ ፓርላማው ከአንድ የፓርላማ አባል በስተቀር በአንድ ፓርቲ አባላት የተሞላ ስለሆነ የቀረበለትን በሙሉ ሊያፀድቅ የሚችለው ..ልማታዊ መንግስት.. በሚል የሀገሪቱን የኢኮኖሚ አቅጣጫ በቀየሰውና ..አብዮታዊ ዴሞክራሲ.. በሚል ርዕዮተ ዓለም በሚመራው በኢህአዴግ ፍላጐት ብቻ ተመሥርቶ ስለመሆኑ ጥያቄ የለውም፡፡

እዚህ ላይ የንብረት ባለቤትነት መብት /ፕሮፐርቲ ራይት/ ምን ያህል እየተሸረሸረ እንደሆነ በአዋጁ ግልፅ ሆኖ ይታያል፡፡ ..ነፃ ገበያ.. ነው የኢኮኖሚ መርሔ ብሎ የዛሬ 20 ዓመት በይፋ ያወጀው ኢህአዴግ ምን ያህል ከ..ነፃ ገበያ.. ኢኮኖሚ ተፈናጥሮ ወደ ..እዝ ኢኮኖሚ.. ዘሎ እንደገባ ከላይ የተጠቀሰው አዋጅ ፍንትው አድርጐ ያሳያል፡፡ ሊበራል ኢኮኖሚ የሚባለው ነፃ ገበያ፣ ከነፃ አስተሳሰብ፣ ከመድበለ ፓርቲ፣ ከፍትሃዊ ምርጫ፣ ከነፃ ሚዲያ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት እንዳለው ሁሉ በዴሞክራሲ ሀገራቸውንና ህዝባቸውን ለብልፅግና ያበቁት የዓለማችን ሀብታም ሀገሮች በተግባር አረጋግጠዋል፡፡

ኢህአዴግ ከነፃ ገበያ ወደ ..ልማታዊ መንግስት.. ወደ ሚለው የኢኮኖሚ ፖሊሲ ምን አንሸራተተው? ወይስ ቀደም ብሎ በአሜሪካ አቀናባሪነት ስልጣን ላይ ሲወጣ፣ አሜሪካንና ሌሎች ምዕራባውያን ሀገሮችን ለመሸንገል የተጠቀመበት የ..ፖለቲካ ቆረጣ.. መንገድ መሆኑ ነው? በሌላ በኩልም ቀደም ብለው የያዙትን የኮሚኒዝም ርዕዮት፣ በተለይ የቻይና ኮፒ ፔስት የሆነውን የአንድ ፓርቲ ስልጣንን በብቸኝነት ይዞ ለዘመናት ለማቆየት የተነደፈ ታክቲክና ስትራቴጂ ይሆን?

ኢህአዴግ በዘንድሮው የአምስት ዓመት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ ላይ የግሉ የኢኮኖሚ ሴክተር ሰፊ ቦታ እንዲኖረው አላደረገም፡፡ ምንም እንኳን እቅዱ መተግበር ተጀምሯል ከተባለ ከአንድ ዓመት በላይ ቢሆነውም ይህ ነው የሚባል ተጨባጭ የሆኑ የእቅዱ አካሎች ያሳዩት አንዳችም ውጤት እንደሌለ አጠቃላይ የሀገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በቂ ማረጋገጫ ነው፡፡ እርግጥ በመንግስት ሚዲያ እዚህ ግቡ የማይባሉ የንግድና የምርት እንቅስቃሴዎች ተጋነው ሲዘገቡ ይታያሉ፡፡ የአምስት ዓመቱ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ለነፃ ገበያ እንቅስቃሴ እንደ እዝ ኢኮኖሚ ጋሬጣ ሆኖበት ይታያል፡፡

በመሰረቱ የግል ይዞታ ባለንብረትነት መብት በተግባር ባልተረጋገጠበት የአምባገነን መንግስታት ሀገራት ውስጥ በግል በሚገኙ ምርታማነትና ታታሪነት የሚገኙ ሀብቶች በግል ይዞታ የመቆየት ዋስትናቸው የመነመነ ነው፡፡ በእነዚህ ሀገራት ቢያንስ በጊዜያዊነት የግል ባለሀብቱ ዋስትና ሊያገኝ የሚችለው የመንግስትን ሥልጣን ከጨበጠው ሀይል ወይም ፓርቲ ጋር የጥቅም ሽርክና እስካለው ድረስ ብቻ ነው፡፡ አለበለዚያ ለንግድና ለምርታማነት ማደግና መስፋፋት ከሚያስፈልጉት ግብአቶች ውስጥ ዋና ዋና የሆኑትን መሬትና ካፒታል ማግኘት የማየታሰብ ነው፡፡

በሀገራችን እንደ ኤፈርት ያሉ የሀገሪቱን ንግድና ኢንቨስትመንት በሞኖፖል የያዙና ሌሎች ከኢህአዴግ ጋር እጅና ጓንት የሆኑ የንግድና የኢንቨስትመንት ተቋማት ለሥራቸው የሚያስፈልጋቸውን ካፒታልና መሬት ለማግኘት የሚያስፈልጋቸው በወረቀት ላይ የሰፈረው የንግድና የኢንቨስትመንት ህግ አይደለም፡፡ በቀላሉ የገዢው ፓርቲ ቁንጮ የሆኑ ሀላፊዎች የሚያደርጓቸው የስልክ ጥሪዎች መሬትና ካፒታል እንዲያገኙ ያስችላቸዋል፡፡ በርካታ የኢንቨስትመንትና የንግድ መረጃዎች እንደሚያስረዱት ከሆነ ጉዳያቸውን በቀጭንም ሽቦ የሚጠናቅቁ ንኪኪዎች ባለጉዳዮቹ ባንክ ሲደርሱ የብድሩ ውልና የሚያውልና የብድሩ መጠን ተዘጋጅቶ ይጠብቃቸዋል፡፡ ስራቸውን የሚሰሩበትን ቦታም ምንም ውጣ ውረድ ሳይገጥማቸው በሆነ የሊዝ ተመን ቦታቸውን ይረከባሉ፡፡ ብድራችሁን መክፈል ባለባችሁ ሰዓት እስከ ወለዱ ክፈሉ ብሎ የሚያስገድድ ባለስልጣን አይኖርም፡፡ ካለም የራሱን የእንጀራ ገመድ ያሳጥር እንደሆነ እንጂ ብዙም የሚያስገኘው ለውጥ የለም፡፡ የተለየ ክፍተት ተፈልጐለትም ከሥልጣኑ ለማንሳት የእዝ አለነው ..ልማታዊ.. ኢኮኖሚ ለሚከተሉ መንግስታት እዳው ገብስ ነው፡፡

በእዝ ኢኮኖሚ የሚመራ መንግስት ወይም ደግሞ ቃሉን ለማለዘብ ..ልማታዊ መንግስት.. ብንለውም በእንዲህ ዓይነት ሥርዓት ውስጥ የሚገኙ የግል ባለሀብቶች የሚያደርጓቸው የንግድና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴዎች እጅግ የጠበቡ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ከሚያገኙት ትርፍም በውስጠ ታዋቂነት ለባለስልጣናቱ የማካፈል ግዴታ የተጣለባቸውም ይመስላል፡፡ ይህንን በዘመኑ ቋንቋ ሙስና ወይም በኢህአዴግ ቋንቋ ኪራይ ሰብሳቢ የሚሉት ዓይነት መሆኑ ነው፡፡ በመሰረቱ እንዲህ ዓይነቱ የኢኮኖሚ ሥርዓት የሚታየው በንክኪው ነጋዴና በባለሥልጣን ምህዋር ውስጥ የሚሽከረከር ለሀገርም ለህዝብም ጥቅም የማይሰጡ ጥቂት የሀገሪቱ ዜጐች ብቻ የቅምጥል ኑሮ የሚኖሩበት የኢኮኖሚ ኡደት ነው፡፡ ..ንክኪዎቹ.. የግል ባለሀብቶች የባንክ ብድርም ሆነ መሬት የማግኘት ተስፋቸው የሚንጠለጠለው በገዢው ባለስልጣናት ላይ ሆኖ ይታያል፡፡

የግል ባለሀብት ከልማታዊ መንግስት ጋር የፍጥጫው ..ሀሁ.. የሚጀምረው ገና የንግድ ፈቃድ ለማውጣት ታች ላይ ሲል ነው፡፡ ፈቃዱ እንደተገኘና ወደ ኢንቨስትመንቱ ሲንደረደር ደግሞ ቀደም ብሎ በኢንቨስትመንት ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የተገቡት የተስፋ ቃሎች ባዶ መሆናቸውን መረዳት ይጀምራል፡፡ የንግድና የምርት እንስቃሴውም በታታሪነት፣ በፈጠራ ችሎታ ላይ እንዲሁም በገበያው ላይ የተመሰረቱ አለመሆናቸውን ቢሮክራሲው አንድ ሁለት እያለ ይኮረኩመዋል፡፡ በዚህ በቢሮክራሲው ኩርኩም በርካታ ከውጭ ሀገራት ከፍተኛ ካፒታል ይዘው መጥተው የነበሩ ኢትዮጵያውያን ንብረታቸውንና ጊዜያቸውን አባክነው ተመልሰው ወደ አሜሪካና ወደ አውሮፓ የተመለሱ ኢትዮጵያውያን እንዳሉ ብዛት ያላቸው ማስረጃዎች ያረጋግጣሉ፡፡ ኢህአዴግም አይክደውም፡፡

በልማታዊ መንግስት ስር በቀላሉና በአጭር ጊዜ ጥቅም የሚያስገኙ ንግዶች በኩል በምንም ዓይነት የግል ባለሀብቶች እድሉን እንዲያገኙ ስርዓቱ አያመችም፡፡ የተሻለ ገበያ ያስገኛሉ የሚባሉ ምርቶች ወይ በመንግስት ሥር ይሆናሉ ወይ ደግሞ ከገዢው ፓርቲ ጋር የጥቅም ተካፋይ የሆኑ ..ንክኪ.. ነጋዴዎች እንዲይዙት ይደረጋል፡፡ ..ንክኪውም.. ቢሆን ትንሽ ሸርተት ካለ ለሀብቱ ምንም ዋስትና አይኖረውም፡፡ መላ ይፈለግለትና እንዲወገድ ይደረጋል፡፡

Page 27: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ኢትዮጵያ ነፃ ገበያ ትከተላለች ይባላል በአንድ በኩል፤ በሌላ በኩል ደግሞ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ አቅጣጫ ..የልማታዊ መንግስት.. ነው ተብሎ በኢህአዴግ በይፋ ተነግሮ እየተሰራበት ነው፡፡ እነዚህ ሁለት የኢኮኖሚ ስርዓቶች እርስ በርሳቸው የሚጣረሱ እንጂ የሚደጋገፉ አይደሉም፡፡ በነፃ ኢኮኖሚ ስርዓት ስር የሚኖረው የግለሰብ የንብረት ባለቤትነት መብት በህግ የተደነገገና በተግባርም የሚተገበር ሲሆን፣ በልማታዊ መንግስት ስር ግን የግል ንብረት የባለመብትነትን መብት ቅድሚያ የሚሰጠው ለመንግስት ነው፡፡ በቅርቡም የከተማ የግል ይዞታ መብት ከባለንብረቱ ወደ ሊዝ እንዲዘዋወር የማድረግ ሂደት መጀመሩ የነፃ ገበያ ስርዓት በልማታዊ መንግስት ጡንቻ ከጨዋታ ውጭ እንዲሆን ለመደረጉ በቂ ማረጋገጫ ሆኖ ሊወሰድ ይችላል፡፡ የገጠር የእርሻ መሬት የገበሬው እንዳልሆነ ሁሉ የከተማውም መሬት ሙሉ በሙሉ ወደ ሊዝ እንዲገባ መደረጉ በዚች ሀገር ላይ የግል ንብረት ባለመብትነት አደጋ ላይ መውደቁን ያመላክታል፡፡

Page 28: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

የፍትህ ዓምድ ህግ የሚወጣው ለማን ነው? በጌታቸው ታምራት (LLB)

በየሀገሪቱ የሚኖረው ማህበራዊ፣ ምጣኔ ሀብታዊ እና ፖለቲካዊ ኡደት መለያየት የየሀገራቱ ህግ በውስጡ በያዘው ፍሬ ነገር መካከል ልዩነት እንዲኖር ተፅዕኖ መፍጠሩ አይቀርም፡፡ ሌላው ቀርቶ በአንድ ሀገር ውስጥ ባሉ የተለያዩ ከተሞች ወይም ክልሎች መካከል የማህበራዊ መስተጋብር ልዩነት መኖሩ እየተስተዋለ ያለ ሃቅ ነው፡፡ ለምሳሌ በሀገራችን ባሉ የተለያዩ ብሄር ብሄረሰቦች መካከል መሰረታዊ የሆነ የማህበራዊ እና የምጣኔ ሀብታዊ ልዩነት ያስተውላል፡፡ በአንድ የክልል አካባቢ እንደ መልካም እና ቅዱስ ተግባር የሚከውን ስራ በሌላው ክልል የተወገዘ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህ የሚሆነው አንድ ክልል ውስጥ የሚካሄደውን ማህበራዊ ወይም ምጣኔ ሀብታዊ ሂደት ለመኮነን አልያም ለመደገፍ ሳይሆን በዚያ ክልል ውስጥ በእለት ተእለት እንቅስቃሴ ውስጥ አብሮ የኖረ በመሆኑ ነው፡፡ ህግ በባህሪው በማህበረሰብ ውስጥ ያሉ እሴቶች በተገቢው መንገድ ጠብቆ ፖለቲካዊ ሂደትን የሰመረ በማድረግ ምጣኔ ሀብታዊ እድገት ፍትሃዊ በሆነ መልኩ የሚመጣበትን መንገድ ማመቻቸት ይጠበቅበታል፡፡ ሌባ፣ ቀማኛ፣ ነውረኛ፣ አረመኔ ወዘተን ለመቅጣት ህግ የማስፈለጉን ያህል በሰው ህይወት እና በሀገር ሀብት የሚቀልድ መንግስት እንዳይኖር የህግ ሚና ወደር የለውም፡፡ ህግ አግባብ ባለው መንገድ ከተጠቀሙበት በየትኛውም ዘርፍ ለሀገር እድገት እና ለዜጐች ነፃነት መስፈን የማይተካ ሚና ይጫወታል፡፡ በአንድ ሀገር ውስጥ የሚፀድቁት እና በተግባር ላይ የሚውሉ ህጐችም ሀገራቱ የደረሰበትን የስልጣኔ ደረጃ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ያሳያሉ፡፡ በዛሬው ፅሁፌ የህግ ሚና በተለያዩ የመንግስት ስርዓቶች ውስጥ ምን ይመስላል? ህግ ሲወጣ ለተጠቃሚነቱ ማንን ታሳቢ አድርጐ ይወጣል? የሚሉትን እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን እናያለን፡፡

ህግ በዴሞክራሲያዊ ስርዓት ውስጥ የመንግስትን ስርዓት ዴሞክራሲያዊ ነው ወይም አምባገነናዊ ከሚያሳብሉት አበይት ጉዳዮች አንዱ በሀገሩ ያለው ህግ እና

ተፈፃሚነቱ ነው፡፡ ህግ በህዝቡ ተቀባይነት እንዲያገኝ እና ዴሞክራሲያዊ ስያሜ እንዲሰጠው የህብረተሰቡን ችግር መፍቻ መፍትሄ፣ የእድገት መንገድ የሚመቻችበት እና አላስፈላጊ የሆነ የማህበረሰብ አሜኬላዎች የሚነቀሉበት ስልት ነው፡፡ ህጐች ወጥተው ለተግባራዊነት ወደ ማህበረሰቡ ከመውረዳቸው በፊት ሰፋ ያለ ምርምር በህብረተሰቡ ውስጥ ተሰርቶባቸው አስፈላጊነታቸው ሊታመንበት ይገባል፡፡ ህግ በሚጸድቅበት ወቅት በህጉ ዙሪያ ክርክር፣ ስምምነት ወይንም ተቃርኖ የሚያሳዩት የህግ አውጭ አካላት ህጉ ማካተት ባለበት ጉዳይ፣ ህጉ በያዘው ፍሬ ነገር እና የህግ ሙያ ከሚጠይቀው መሰረታዊ ፍላጐቶች እና ከሙያው ስርዓት ጋር ብዙም ግንኙነት ስለማይኖራቸው አብዛኛውን ጊዜ ፖለቲካዊ ጥቅምን በማስቀደም የህጉ ሚና እንዲያንስ ያደርጉታል፡፡ እንዲህ የሚሆንበት ወቅት ህጐች ማካተት የሚገባቸውን መልካም እሳቤዎች ሳይዙ እንዲቀሩ ስለሚያደርጓቸው ወደ ህብረተሰቡ በሚወርድበት ወቅት ትልቅ ችግር ይገጥማቸዋል፡፡ ይህ እንዳይሆን ህግ ከመውጣቱ በፊት የህጉ አስፈላጊነት ብቃት ባለው ባለሙያ ተጠንቶ ከነጥቅም እና ጉዳቱ ለህግ አውጪ ው አካል ሊቀርብ ህግ-አውጭው አካል ሁኔታውን መዝኖ እንደ አስፈላጊነቱ መካተት ወይም መውጣት ያለበትን ጉዳይ ምክንያታዊ በሆነ መልኩ አስደግፎ ከተወያየ እና ከመከረ በኋላ የሚገባውን ማድረግ አለበት፡፡ ምርምር ህጐችን የህዝብን መሰረታዊ ፍላጐት ያማከሉ እንደሆኑ ትልቅ ድርሻ አለው፡፡ በውስጡም ካለው የጊዜው ሁኔታ ጋር እንዴት አብሮ ተግባራዊነቱ በምን መልኩ መሆን እንዳለበት እንዲሁም ከዚህ ቀደም የነበሩ ህጐች ምን ጠቀሜታ እና ጉዳት እንደነበራቸው የመሳሰሉትን በማጥናት የህጉን አስፈላጊነት ለሚመለከተው ክፍል ያቀርባል፡፡ በሀገሪቱ የህግ አውጪ ነት የሚመለከተው አካል የምርምሩን ውጤት ካጤነ በኋላ ባለሙያዎች በዚህ ዙሪት ምርምሩን መሰረት አድርገው ህዝቡን አማክረው፣ አለም አቀፍ ስምምነቶችን ጠብቀው እና ሀገሪቷ በህጉ ልትጠቀም የምትችልበትን ሁኔታ መዝነው ህጉን ያረቁታል፡፡ ህግ አውጭው አካል በረቂቅ ህጉ ላይ በቂ ጊዜ ሰጥቶ ከተወያየ በኋላ ዴሞክራሲያዊ በሆነ ሂደት ህጉ እንዲፀድቅ ያደርጋል፡፡ እንዲህ አይነቱ ህግ በምርምር፣ በሙያ ድጋፍ፣ በህዝብ ተሳትፎ፣ በዴሞክራሲያዊ ሂደት የሚመጣ በመሆኑ ከአስፈላጊ ፖለቲካዊ ብዥታ የፀዳ ስለሚሆን ተግባራዊነቱ ላይ የጐላ ችግር አይገጥመውም፡፡ በእንዲህ አይነት ስርዓት ውስጥ ያለፈን ህግ የህጉ ምሁር ፍሬዴሪክ ባስትያት በህዝቡ ፍላጐት ውስጥ ተፈትኖ የወጣ ለህዝቡ ሲባል በተወከሉ አካላት አማካኝነት ተግባራዊ የሚሆን፤ በተገደበ ስልጣን ውስጥ የሚንቀሳቀስ የዜጐች ንፁህ መሳሪያ ነው ይሉታል፡፡ በዚህ ዓይነት ሂደት ውስጥ ያለፈ ህግ በየትኛውም ሀገር የመንግስት ስርዓት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ነበር ብሎ አፍን ሞልቶ መናገር አይቻልም፡፡ ቀድሞ የነበሩት ህጐችም ሆኑ አሁን እንደ አዲስ ወጥተው በስራ ላይ ያሉ ህጐች ተግባራዊነታቸው ላይ ብዙ ሳንካ የሚገጥማቸው እና እንዲቀየሩ የሚሆኑት ነባራዊውን እውነታ መዝነው የህዝቡን ፍላጐት ማሟላት ስለሚከብዳቸው ነው፡፡ ዜጐች በህጉ ሙሉ ለሙሉ ከመጠቀም ይበልጥ በህጉ መካከል ባሉ ክፍተቶች በመጓዝ ብልፅግናን እንዲመኙ ከሚያደርጋቸው ምክንያቶች ዋነኛው በሀገራችን የሚወጡ ህጐች የህዝቡን ፍላጐት እና ተቃርኖ ማማከል ስለሚከብዳቸው ነው፡፡ መሆን ግን ይገባው ነበር፡፡ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ በኋላ የወጡ የሊዝ አዋጅን የመሳሰሉ ህጐች የመቀየራቸው ዋናው ሚስጢር ከዚሁ የራቀ አይደለም፡፡ በዚህ አይነት ሁኔታ ህዝቡን ሳያማክል የሚቀጥል ከሆነ ፓርላማው በየጊዜው አንድን ህግ እያፀደቀ ሌላውን እየሻረ የሚቀጥልባት ሁኔታ ይኖራል ማለት ነው፡፡

2. ህግ አምባገነን ስርዓት ውስጥ

አምባገነናዊ ስርዓት ውስጥ ከዜጐች የስልጣን ባለቤትነት ይበልጥ የግለሰቦች ውሳኔ ፍላጐት ይንፀባረቅበታል፡፡ ለይስሙላ

የሚቀመጡ ህግ አውጭ አስፈፃሚም ሆነ ህግ ተርጓሚ አካላት ቢኖሩም የሁሉም አካላት ስልጣን ተደፍጥጦ ስርዓቱን ለማስጠበቅ ብቻ ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ይህ ማለት ግን በዚህ ስርዓት ውስጥ ህግ የለም ማለት አይደለም፡፡ ህግ አለ በአምባገነናዊ መንገድ ለመግባትም አምባገነናዊ ህግ ይኖራል፡፡ አልያም ደግሞ የተፃፈ ህግ- ቢኖርም ግለሰቦች ከህዝቡ ፍላጐት እና ከህጉ በላይ ገዝፈው ህዝቡን እንደፈለጉ የሚያደርጉበት ስርዓት ነው፡፡ በዚህ ስርዓት ውስጥ ያሉ ህጐች ብዙውን ጊዜ በቀጥታ ስልጣን ማስጠበቂያ መሳሪያ ሆነው ሲያገለግሉ አንዳንዴ ደግሞ ስልታዊ በሆነ መልኩ ለዚሁ ተግባር ሲውሉ ይታያል፡፡ በመንግስታት ታሪክ ውስጥ የአረመኔ እና ጨካኝ አምባገነኖች ቁንጮ ሆኖ የሚጠቀሰው የሂትለር ናዚ ስርዓት ስርዓቱን ለመጠበቅ ታቅዶ የተዘጋጀ የራሱ የሆነ ህግ ነበረው፡፡ በዚሁ ህግ መሰረት ህዝቡንም በግዴታ እና በውዴታ እየቀላቀለ ያስተዳድር ነበር፡፡ ሆኖም እንዲህ ዓይነቱ ህግ የህዝቡ ነፃ ፍላጐት የተንፀባረቀበት ነው

Page 29: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ብሎ ደፍሮ መናገር ግን አይቻልም፡፡ እንዲህ አይነት ቀጥተኛ አምባገነናዊ ህጐች የህዝቡ ፍላጎት ስለማይንፀባረቅባቸው በህዝቡ ተጠልተው ከሆነ ጊዜ በላይ ወደፊት እንዳይጓዙ ያደርጋቸዋል፡፡ ብዙውን ጊዜም መጨረሻቸው ቅርብ ነው፡፡ ነገር ግን ስልታዊ የአምባገነን ህጐች ለሁሉም ነገር የማስመሰል ገፀ-ባህርይ ስለሚጫወቱ ህዝቡ ችግራቸውን ለመረዳት ጊዜ ይወስድበታል፡፡ በዚህ የተነሳ ቆይታቸው ረዘም ያለ ይሆናል፡፡ የዚህ ዓይነቱን ህግ የሚያወጡ አምባገነኖች ስልታዊ አምባገነኖች (Technical tyrants) ይባላሉ፡፡ ይሁንና ቀጥተኛ ሆነ ስልታዊ አምባገነኖች ውጤታቸው ተመሳሳይ ነው፡፡ ሁሉም ስልጣን ማስጠበቂያ፣ የህዝቡን ነፃ ፍላጐት ማፈኛ፣ ከዘመኑ ጋር አብረው የሚራመድ በመምሰል፣ የጥቂት ደጋፊዎቻቸውን ፍላጐት በሚሊዮን በማባዛት እንደ አብዛኛው ህዝብ ፍላጐት በማስመሰል መደስኮር እና የስልጣንን ዘመን ማራዘም ነው፡፡ ሁለቱም አይነት አምባገነናዊ ስርዓት በሀገራችን ታሪክ ውስጥ አልፈዋል፤ አብረውንም እየኖሩ ናቸው፡፡ ስልታዊ አምባገነኖች የሚባሉት ለሀገራቸው ቀናዒ በመምሰል ራሳቸው ለህጉ የሚገዙ በማስመሰል ህዝቡን በስልታቸው ልምጥለፍ በህጉ በማስገደድ ፍላጐታቸውን ያሳካሉ፡፡

ህዝቡ ወዲህ ህጉ ወዲያ

ከላይ ለማስቀመጥ እንደሞከርኩት የህግ መሰረታዊ ሚና የማህበረሰቡን መልካም እሴቶች ጠበቆ በማቆየት ለሌሎች ዘርፎች መንገድን በማመቻቸት ህዝቡን ወደ ስልጣኔ መስመር ማምጣት ነው፡፡ ህግ በአግባቡ ከተጠቀሙበት ጥቅሙ አሌ የማይባል እንደመሆኑ ያህል ባልሆነ አቅጣጫ ከተሰደደ ለአምባገነኖች ስልታዊ መሳሪያ ይሆናል፡፡ ይህ ሁኔታም ስልታዊ አምባገነኖች እንዴት እንደሚጠቀሙበት ከላይ በግልፅ ተቀምጧል፡፡ ህግ በማህበረሰቡ ውስጥ የተበላሹ አካሄዶችን ለማከም የመድሀኒትነት ዋጋ አለው፡፡ መድሀኒት በአግባቡ ካልተጠቀሙበት ጉዳቱ የከፋ እንደመሆኑ መጠን ህግም በግለሰብ ላይ ብቻ ሳይሆን በህብረተሰብ ላይ የሚያደርሰው ጥፋት መጠነ ሰፊ ነው፡፡ በሀገራችን ከቅርብ አመታት ወዲህ የሚወጡ ህጐች የዜጐችን ነፃነት የሚያፍኑ፣ ኢኮኖሚያዊ መብትን የሚጨቁኑ እና ዜጐች በሀገራቸው ዋስትና እንዲያጡ የሚያደርጉ ሆነው አይተናቸዋል፡፡ አዲሱ የፕሬስ ህግ፣ የፀረ-ሽብርተኝነት አዋጅ፣ የጡረታን አዋጅ፣ አዲስ የሊዝ አዋጅ የመሳሰሉትን ብንጠቅስ ለተነሳንበት መከራከሪያ ጥሩ ማስረጃ ይሆነናል፡፡ በፕሬስ ህጉ የተቀመጡ አፋኝ አንቀፆች በተገቢው ሁኔታ እንዳያድግ አንቆ ይዟታል፡፡ ጋዜጠኞች ከሙያ ስነ-ምግባሩ ውጭ በህጉ አስገዳጅነት በቂ መረጃ ወደ ህዝቡ እንዳያደርሱ ህጉ በውስጡ ያስቀመጣቸው አንቀፆች ቀፍድደው ይዘውታል፡፡ በሌላ ወገን የፀረ-ሽብርተኝነት ህጉ ዜጐች በሀገራቸው በነፃነት እንዳይኖሩ፣ የሰቀቀን ኑሮ እንዳንሰራፉ ከህጉ በላይ ለፖሊስ እና ለደህንነት ተቋማት ከፍተኛ ስልጣን ይሰጣል፤ የሊዙ ህግ የንብረት ባለቤትነትን መብት ይጋፋል፤ ዜጐች በፈለጉት መንገድ በንብረታቸው የመጠቀማቸውን ኢኮኖሚያዊ መብት ያፍናል፡፡ አዲሱ የጡረታ አዋጅ ግለሰቦች ያለፍላጐታቸው በዚህ እቅድ ውስጥ መካተት እንዳለባቸው ይናገራሉ፡፡ ሆኖም ሁሉም ህጐች የህዝቡን ፍላጐት፣ የባለሙያን እይታን እና ተሞክሮ ጥቅም እና ጉዳት በበቂ ሁኔታ ያንፀባረቁ አይደሉም፡፡ ነገር ግን ከጀርባቸው ከያዙት አጀንዳ በተቃራኒው ለህዝቡ የልማት አጋርነት መንፈስ እንዳላቸው በአደባባይ በመደስኮር ህዝቡም ለህጉ ተገዢ መሆን እንዳለበት በፕሮፓጋንዳ በማሳመን እና በህይል በማስገደድ ተግባራዊ መሆን እንዳለባቸው ይወተውቱታል፡፡ የህዝቡ ፍላጐት ወዲህ ህጉ ወዲያ፡፡ የህዝቡ ፍላጐት ይቅደም ወይስ ስልታዊ ህጐች ይፈፀሙ? ይህ መሰረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ ለሄንሪ ዴቪድ ቶረው ግን የአብዛኛው ህግ ፍላጐት ከስልታዊ እና አምባገነናዊ ህጐች ጋር ለንፅፅር የሚቀርቡ አይደለም እሱ እንደሚለው ህግ የአብዛኛውን ህዝብ ፍላጐት ማንፀባረቅ የግድ ይለዋል፡፡ ካልሆነስ ካልሆነማ ...ቸር እንሰንብት፡፡

Page 30: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ኪነ-ጥበብ

ፊደሎች እንድሪያስ ስዩም ከተፈጥሮ አለዚያስ ከማህበራዊ ሳይንስ ምሁራን መጣ? እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ አንድ የተለመደ ማሳመኛ ሲነገር እሰማለሁ፡

፡ እንዲህ እይተባለ፡፡ ..ግማሹ ድረስ ውኃ የተሞላ ጠርሙስ ጠረጴዛ ላይ ተቀምጧል አንድ ሰው ምን እንደሚታየው ሲጠየቅ ግማሽ ጠርሙስ ውኃ

እንደሚታየው ተናገረ፡፡ ሌላ ሰው ደግሞ ተመሳሳይ ጥያቄ ሲቀርብለት ግማሽ ሆዱ ባዶ የሆነ ጠርሙስ ይታየኛል ሲል ተናገረ፡፡ ይህን ሀተታ በተለያየ የኑሮአችን አጋጣሚ ሰምተነው ይሆናል፡፡

ዛሬም እኔ ይህንን የመሠለ ነገር ለማንሳት ፈለግሁ፡፡ የአማርኛ ቋንቋ ፊደሎችን እንደተጠያቂዎች ሁሉ በሁለት ከፍለው የሚመለከቱ ኢትዮጵያዊያን አሉ፡፡

በቀደምት ደራሲነት ከሚጠሩት መካከል ሊጠቀሱ ከሚቻላቸው ኢትዮጵያዊ ደራሲ ሀዲስ አለማየሁ በ1958 ዓ.ም ባሳተሙት ፍቅር እስከ መቃብር የአማርኛ ቋንቋ ውስጥ ያሉ ፊደላት መብዛትና የአንዳንዶቹ መደጋገም እንዳሳሰባቸው ጠቅሰው ሊሆን ይችላል ባሉት መልኩ አንዳንድ ፊደሎችን ከእነ እርባታቸው ዘርዘዋል፡፡

ባመዛኙ በዚህ ዘመን /ከወጣቶች/ ከሚጠቀሱ የስነ-ጥበብ ሰዎች አንዱ የሆነው ገጣሚና ፀሐፊ ተውኔት ግርማይ ኃይሌ በ፣ባተሌው፣ ቴአትር ላይ መከራከሪያውን ያንፀባርቃል፡፡ የአማርኛ ፊደላት መብዛት መልካም ልዩነት ሲልም ውበትና ስልት ናቸው ብሎ ይሞግታል፡፡

በአማርኛ ቋንቋ ውስጥ የተሰባሰቡ ሆሄዎችን ማጥናት ያለ ምንም ስስት እየመነዘሩ ለመጠቀም ያስችላል ይልና ፣አበበ በሶ በላ፣ ብሎ ለመፃፍ ሰባት የአማርኛ ሆሄያትን መጠቀም እንደሚበቃ በእንግሊዝኛ ቢፃፍ ግን /Abebe ሯስቋቄሯስቁሮ/ ተብሎ እንደሚፃፍ ይህም ከአማርኛው እጥፍ ሆሄያትን መጠቀም ግድ እንደሚል በማሳያነት ያነሳዋል፡፡

የአማርኛ ቋንቋ ፊደላትን መብዛትና መደጋገም በተመለከተ በየጊዜው እሰጥ እገባዎች ይካሄዳሉ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በቤተ ክህነትና በዩኒቨርስቲ ሊቃውንት መካከል የሚደረግ የቋንቋ ውጊያ እስኪመስል ድረስ፡፡

ዘመናዊ ትምህርት ቀመስ የሆኑት የተደጋጋሚ ፊደሎች ጋጋታ ምንም ጥቅም የለውም የሚል አቋም ሲይዙ የቤተክህነቶቹ ግን ሁሉም የአማርኛ ፊደላት ዋጋ አላቸው ይላሉ፡፡ በነገራችን ላይ የአማርኛ ፊደላት ስል አማርኛ እየተጠቀመባቸው ያሉ ፊደላትን ማለቴ ነው፡፡ ይህም ነገር ይመስላል የክርክሩ መንስኤ፡፡ አብዛኛዎቹ የአማርኛ ፊደላት ከግዕዝ የወረዱ ስለሆኑ የግዕዝ ቋንቋ ፀባይ በአማርኛ ውስጥ ያገኛሉ አያገኙም የሚል ይዘት አለው፡፡

ከፍ ሲል እንዳልኩት የፊደሎቹ መብዛትና መደጋገም ዋጋ የለውም የሚለውን ሐሳብ የዩኒቨርስቲ ምሁራን ይበልጡን ይደግፉት እንጂ አበራ አዳሙን የመሠሉ የቤተክህነት ሊቃውንት በይፋ ሲደግፉት ይስተዋላል፡፡

አበራ አዳሙ በሁለት መጽሐፎቹ ውስጥ እንደ ሀዲስ አለማየሁ ሁሉ ተደጋጋሚ ሆሄያትን አስወግዶ መጻፍን መርጧል፡፡ ይህንን ማድረጉም ትክክል እንደሆነ ይናገራል፡፡

የቤተ ክህነት ሊቃውንት በተለይ ከቃላት ትርጉም ጋር ተያይዞ እያንዳንዱ ሆሄ አስፈላጊ ነው ብለው ሲከራከሩ የሚከተሉትን አይነት ምሳሌዎች ይሰጣሉ፡፡ምሁር ማለት የተማረ ሲሆን ምሑር ማለት ደግሞ ምሕረት የተደረገለት ነው፡፡ ሰዓሊ ማለት ስዕል የሚስል ሰው ሲሆን ሰአሊ ማለት ለማኝ ማለት ነው፡፡ ኃ/ማርያም ተብሎ ቢፃፍ ኃይለ ማርያም ሀ/ማርያም ተብሎ ቢፃፍ ሀብተ ማርያም ብለን እናነባለን ይላሉ፡፡

ባንፃሩ የዩኒቨርስቲ ምሁራን እንዲህ ለሚሉት መከራከሪያዎች ውሃ የሚቋጥር ምላሽ የሰጡበት ጊዜ የለም፡፡ ይህ የግዕዝ ቋንቋ ባህርይ ነው ከእለት ውጭ፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎች ግን በእለት ከእለት ንግግራችን የምንጠቀምባቸው ከአማርኛ አፍ ጐንም ያልራቁ መሆናቸው ይታመናል፡፡

የአማርኛ ቋንቋ ፊደሎችን በተመለከተ በሀገር ውስጥና በውጭ የቋንቋ ምሁራን ተደጋግመው የሚነገሩ ነገሮች የፊደል መብዛትና ድግግሞሽን የሚመለከቱ ይሆኑ እንጂ አንባቢዎችን ለማመልከት የሚረዱ ምልክቶች አንድ አይነት /ወጥ/ አለመሆን የማጥበቂያና የማላያ ምልክት አለመኖር የተናባቢና አንባቢ አለመለየትም የቋንቋው ፊደላት ዶክመቶች መሆናቸውን ምሁሮች ይጠቅሳሉ፡፡

ከዚህ በተቃራኒው አንድ ፊደል የሚጠራው በአንድ ድምፅ ብቻ በመሆኑ ማለትም ሲነበብ የሚወክለው አንድን ብቻ ድምፅ መሆኑ ከሌሎች ቋንቋዎች የተለየ የሚያደርገው ባህሪይ መሆኑን ይስማማሉ፡፡

ይህ የቋንቋ ውዝግብ በተለያየ ጊዜ ምሁሮቹን ለልዩ ልዩ የውሳኔ ሐሳብ ሲያነሳሳቸው ይታያል፡፡ ቀደም ሲል የገለፅነው 1985 የሀዲስ አለማየሁ የፊደል ግርዛት እንደተጠበቀ ሆኖ መንስኤ ኃዘን ወልደ ቂርቆስ የኢትዮጵያን ጽሕፈት ሁለት አይነት ማድረግ ሳይሻል እንደማይቀር በዘመናቸው ጠቁመዋል፡፡ ይኸውም ለነባር ኢትዮጵያዊ ጽሕፈት አማርኛን መጠቀም ሀጢአት እንደሌለው ለዘመናዊት ኢትዮጵያ ግን የላቲን ፊደላትን ለመፃፊያነት መጠቀም መልካም እንደሆነ ሐሳባቸውን ሰንዝረዋል፡፡

ይህንን ሀሳብ የሚደግፉ ምሁር በ1990ዎቹ መጀመሪያ ብቅ ብለው ነበር፡፡ አማርኛ ቋንቋ የሚጠቀምባቸውን ፊደላት እርግፍ አድርገን ትተን በላቲን ፊደሎች ሙሉ በሙሉ እንጠቀም ያሉት መላኩ ሙሉአለም፡፡

በሙሉም ይሁን በከፊል የአማርኛ ፊደላትን እንተዋቸው ያሉት ሰዎች እኒህ ብቻ አልነበሩም፡፡ በተለያየ ጊዜ ብቅ ያሉት ደራሲዎችና ምሁሮች የራሳቸውን አማርኛ ሐሳብ ያቀርቡ ነበር፡፡ በላንቃ የሚጠሩ /የሚወጡ/ ሆሄያትና የሚደጋገሙ ፊደላትን ከአማርኛ ጽሕፈት ለማስወገድ በአፄ ሚኒሊክ ዘመንም ጥረት ይደረግ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ከዚህ ባለፈም አናባቢ ድምፃችን (ሁ-ኡ ሂ-ኢ ሃ-አ ሄ-ኤ ህ-እ ሆ-ኦ) ግዕዞቹን ፊደሎች ማለትም የመጀመሪያዎቹን ፊደሎች /ሀ.ለ.ሐ/ በሌሎች ዘመናዊ ቅጥያዎች በመታገዝ መጠቀምንም እንደ ሐሳብ ያነሱ ነበሩ፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ክፍ ሲል ከወጣቶች እንደጠቀስኩት ገጣሚና ፀሐፊ ተውኔት ግርማይ ኃይሌ ሁሉ አቤ ጉበኛም በዘመኑ ይደረጉ የነበሩ የፊደል እንግሊዝ ስብሰባዎችንና ውሳኔዎችን አምርሮ ይቃወም ነበር፡፡

ጨከን ካለው አንዴ ከተማሩት እድሜ ልክ እይመነዘሩ ለመጠቀም የሚያስችል ሀብትን መሰብሰብ ነው፡፡ ስለዚህም የፊደላት መብዛት በጐ ቢሆን እንጅ ከፉ ሊሆን አይችልም ብሎ ተሟግቷል አቤ ጉበኛ፡፡ በየጊዜው የሚነሱ የፊደላትን እንቆራርጥ ሐሳቦችን

Page 31: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

የተቃወመው አቤ ብቻ አይደለም፡፡ የቤተክህነት ምሁራንም ድምፃቸውን ያሰሙ ነበር፡፡ ይቀነሱ የሚባሉ ፊደሎች መቀነስ ሌላው ቀርቶ ቀደም ብለው የተፃፉ ጽሑፎችን መቼም ትውልድ እንዳያነባቸው ማዕቀብ መጣል ይሆናል፡፡ ይላሉ፡፡ በተጨማሪም ፊደሎች ከቀደምት ታሪክና ስላጣኔ ብሎም ነበር ኢትዮጵያዊ ፍልስፍና ጋር የደምና የስጋ ያህል ቁርኝት ያላቸው ናቸውና ማንነትን እንደመሸጥ ነው ይላሉ፡፡

ይህ መሠሉ ሙግት በዚህ ዘመንም አልረገበም፡፡ አሁንም ከቤተ ክህነት ይሁን ከዩኒቨርስቲ የሚወጡ ምሁራን የየራሳቸውን አስተሳሰብ ያንፀባርቃሉ፡፡ ከዩኒቨርስቲ ከሚወጡት የፊደላት ዝባዝንኬ መሸከም አንፈልግም ስልሆነም ስብስብ ይደረጉ አለዚያም በላቲን ፊደል ይተኩ እስከማለት የሚደፍሩ አሉ፡፡

ከቤተ ክህነት የሚወጡት ደግሞ ይህ የእውቀት ማነስ ነው እያንዳንዱ ፊደል ምን እንደሆነ ጠንቅቆ ካለማወቅ የሚመጣ ነው፡፡ እያሉ ችግሩን ያብራራሉ፡፡ አንድን ፊደል በአንድ ቃል ውስጥ እንዴትና መቼ መጠቀም እንዳለባቸው ስለሚያውቁ ወይም ማወቅ ስለማይፈልጉ ፊደል ይቀነስ ይላሉ፡፡ በማለት ተቃራኒዎቻቸውን ይወረፋሉ፡፡

በአማርኛ ስነ ጽሑፍ /በታተሙ መጽሐፍት/ ወጥ የሆነ የፊደል አጠቃቀም ማየት አዳጋች የሆነው ለዚህ ይመስለኛል፡፡ ሐሳብን በተለያዩ መጽሐፍት ውስጥ በልዩ ልዩ ሁኔታ ተፅፎ ልናገኘው እንችላለን፡፡ (ሀሳብ፣ ሐሳብ፣ኃሳብ፣ ሃሳብ፣ ሓሳብ፣ ሀሣብ፣ ሐሣብ፣ ወዘተ) ይህ በተለይ በንባብ ላልጐለበተ ለጋ አንባቢ አስጨናቂ ሊሆን ይችላል፡፡

አማርኛን እየለመደ ያለ ከሆነም ፍፁም የሆነ ውዥንብር ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ ደራሲዎቹ በራሳቸው እንዴት መፃፍ እንዳለባቸው ግራ የተጋቡ ይመስላል፡፡ አንዳንዶቹ ልቅም አድርገው ተገቢውን ሆሄ በተገቢው ስፍራ ይደራደራሉ፡፡ ሌሎች በአቋም አንዳንድ ሆሄዎችን ብቻ ይጠቅማሉ፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ግራ በመጋባት ውስጥ ሆነው የፃፉትን ለአርታኢ ይሰጣሉ፡፡ አለዚያም ከነግሳንግሱ ለህትመት ያበቁታል፡፡

ወደፊት ምን ሊሆን ይችላል? የየትኛው ሐሳብ ግዙፍ ነው? የአማርኛን ፊደሎች መጐነዳደሽ? ወይስ የሆሄያቱን ስሪት ማጥናት? ወይስ በላቲን መቀየር? የምናውቀው ነገር የለም፡፡ ኢትዮጵያዊኛ ግን ምንጊዜም ቅድሚያ ቢሰጠው ደስ ይለኛል፡፡ መልካም ሳምንት

Page 32: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

አዎን ቴዲ አይከናችን ነው! ገንዘቡም ሊመለስለት ይገባል

ዳዊት ሠለሞን (የዘገነርስ ስፖርት ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ)

ህዳር 15/2004ዓ.ም ለንባብ በበቃችው ተወዳጇ ፍትህ ጋዜጣ የነፃ አስተያየት አምድ ስር ..ከተማ ውስጥ ላለነው መንደር

አታሳዩን.. በሚል ርዕስ ግዛው ታዬ የተባሉ ሰው ያቀረቡትን መላ ቅጡ የጠፋበትን ጽሑፍ ደግሜ ደጋግሜ አነበብኩት፡፡ ነገር ግን የአንድ ምስኪንን ኢትዮጵያዊ ነፍስ የታደገውን አቀንቃኙን ቴዲ አፍሮንና ብቸኛውን ተቃዋሚ የፓርላማ አባል የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉን የተቃወሙባቸው ምክንያቶች ውሃ የሚያነሱ ሆነው አላገኘኋቸውም፡፡

የሎሚ መጽሔት (እንዲህ አይነት መጽሔት መኖሩን ከዚህ ቀደም ስለመስማቴ እርግጠኛ አይደለሁም) ማኔጂንግ ዳይሬክተር የሆኑት ግዛው የተከበሩ አቶ ግርማ ከሳምንት በፊት ..የቴዲ አፍሮ ገንዘብ ሊመለስለት ይገባል.. በማለት ያስተላለፉት ወቅቱን የጠበቀ መልእክት ክፉኛ አሟቸዋል፡፡ ቆርቁሯቸዋል፡፡ በራሳቸው አባባል ደግሞ ..አስደንግጧቸዋል..፡፡

የተከበሩ አቶ ግርማ ቴዲን የልጅ አዋቂ በማድረግ ትውልዱን የቀደመ ማለታቸው በግሌ ስህተቱ የቱ ጋር እንደሆነ ሊገባኝ አለቻለም፡፡ አዎን ቴዲ የልጅ አዋቂ ትውልዱን የቀደመ ስለፍቅርና ይቅርታ በዘፈኖቹ የነገረን ሐዋርያ ነው፡፡ አድማጭ ቢኖረው በኢትዮጵያ ምድር የንጉስ ለውጥ እንጂ ምንም አይነት የመንግስት የቅርጽ ለውጥ እንዳልተደረገ የተናገረ ነው፡፡ አቶ ግዛው ግን አቀንቃኙ 15 ሪከርዶችን ሰብሯል (በነገራችን ላይ ኃይሌ ከ26 በላይ ሪከርዶችን ነው የሰበረው) ካሉለት ሻለቃ ኃይሌ ገ/ስላሴ ቀደም ብሎ በተቃዋሚው አመራር ብዕር መጠቀሱ አስደንግጧቸው ..የተከበሩ ግርማ ቴዲን አስቀድመው ሀይሌን አስከትለው የአይከን ደረጃ ሲያወጡ ቢያንስ የቴዲን አንዳንድ ግጥሞች በስህተት የታጨቁ እንደሆኑ አልገባቸውም.. ብለውናል፡፡ በግዛው እምነት የቴዲ የዘፈን ግጥሞ የተሳሳቱ ወይም ከስህተት የጸዱ ባለመሆናቸው ልጁ ተምሳሌት ሊደረግ አይገባውም፡፡ የፀሐፊውን ገለፃ የበለጠ አስቂኝ አልያም በምርቃና የተቸከቸከ አድርገን እንድንመለከተው የሚያደርገን ..ቴዲ በዘፈኑ ከአፈር የሰራሃት ነፍሴ ናት ብቸኛ.. ማለቱን ነው፡፡ ጽሑፋቸውን ሳይቋጩ ሃይማታዊ ካባ ለብሰው ብቅ ያሉት ግዛው ቴዲ ነፍስ ከአፈር እንዳልተፈጠረች የ1ኛ ክፍል ተማሪ እያወቀ አለማወቁ ያሳዝናል፡፡ ይህንን ሰው አይከን ማድረጋችንም ይገርማል ይሉናል፡፡ የሎሚው ማኔጂንግ ዳይሬክተር ነፍስ ከአፈር አለመፈጠሯን በየትኛው ምርምርዎ አረጋገጡ? ወይስ ከሰማይ ተገለጠልዎ? እስኪ እባክዎን የየትኛው ትምህርት ቤት የ1ኛ ክፍል ተማሪዎች ናቸው ነፍስ ላይ የደረሱባት? በሉ እንግዲህ በነካ እጅዎ ይንገሩን፡፡

ግዛው ይቀጥላሉ በአንድ ዘፈኑ ቴዲ ..ዘዴ ካለ ብዬ መጣሁ አንተ ጋር.. በማለት መዝፈኑን ..እንዴት አምላክን ዘዴ ካለህ ብዬ መጣሁ ይለዋል.. በማለት ከአምላክ ጭምር ሊያጋጩት ይታትራሉ፡፡ ለመሆኑ ሰው ወደ አምላኩ የሚጸልየው መፍትሄ አለው በማለት አይደለምን? ቴዲ ታዲያ መፍትሄ ካለህ ብዬ ወደ አንተ መጣሁ በማለቱ ስህተቱ ምንድን ነው?

ግዛው የለውጥ አቀንቃኙን የሚጠሉበት ሌላ ስውር አጀንዳ እንዳላቸው ለመመልከት ይህን ብቻ ማንበብ ይበቃል ..ለጊዜያዊ እውቅና እጅ ባለመስጠት ለዚህ ሁሉ የተከፈለ ዋጋ ሳናይ ስለተሰበክን ብቻ ደግሞም ብስለት በሌለበት ቃል እንገዛ ዘንድ ተጠይቀናል.. ቴዲ ከሸገር ሬዲዮ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ የስኬቱ ምስጢር ምን እንደሆነ ተጠይቆ ነበር፤ በምላሹም ..ለጊዜያዊ እውቅና እጅ አለመስጠት ብሎ ነበር.. ግዛው ደግሞ አባባሉ ከንክኗቸዋል፡፡ እናም ቴዲ የቱ ጋር ነው ዋጋ የከፈለው በማለት ይጠይቃሉ፡፡ በዚህ ገጽ ቴዲ የከፈላቸውን ዋጋዎች መዘርዘር አይዳዳኝም፡፡ ነገር ግን የ1997ቱን ምርጫ ተከትሎ በተፈጠረ አለመግባባት መንግስት በንጹሐን ዜጐች ላይ የወሰደው እርምጃ የሁሉንም ኢትዮጵያዊ ልብ አድምቷል፡፡ በዚህ ወቅት ግን ከታዋቂ ሰዎቻችን መካከል ከጎናችን ያገኘነው ቴዎድሮስ ካሳሁንን ስለመሆኑ ለማስታወስ እፈልጋለሁ፡፡ የወገኖቹ ደም እየፈሰሰ በተዘጋጀለት መድረክ ማይክ በመጨበጥ ለማቀንቀን የሚያስችለው ሞራል አልነበረውም፡፡ እናም ኮንሰርቶችን በመሰረዝ የህዝብ ልጅ መሆኑን አስመስክሯል፡፡ ግዛው ከቴዲ በላይ ሊቀመጥ ይገባዋል የሚሉለት ኃይሌ ግን የትኛውን የሩጫ ውድድር ሰረዘ? ኃይሌን ተምሳሌት የሚያደርገው ሪከርዶችን መሰባበሩና ኢትዮጵያን ማስጠራቱ ከሆነ በድፍረት እላለሁ ይህንን ያደረጉና በማድረግ ላይ የሚገኙ ብዙ አትሌቶች ነበሩን፤ አሉን፡፡ ወደ ፊትም ይኖሩናል፡፡

የሎሚው መጽሔት ባልደረባ ቴዲን ለማንኳሰስና ኃይሌን ለማንገስ በጣሩበት አሸማቃቂ ብዕራቸው ..አንድ ድምጻዊ ቴዲን ተከትሎ ለውጤት ሲበቃ ሳናይ፤ ቴዲ የትውልዱ አይከን ተደረገልን፡፡ አትሌቶቻችን በስማቸው የአትሌቲክስ ማሰልጠኛ እየከፈቱ ተተኪዎችን ሲያፈሩ ለዝነኞች ብቻ ግጥምና ዜማ እየሰጠ ስሙን የገነባ አርቲስት አይከናችን ሲደረግ ያሳዝናል.. ብለውናል፡፡ ይህ አባባል እኛ የምናውቀውን ቴዲን መግለጽ ስልመቻሉ አልያም ስለ እርሱ በመነገሩ አፍራለሁ፡፡ አዎን ግዛው እንዳሉት ቴዲ ምናልባት ያወጣቸው የዘፈን ካሴቶች ከሁለት አይበልጡ ይሆናል፡፡ ቁም ነገሩ ግን ቁጥር አይደለም፡፡

ቴዲ በህዝቡ ልብ ውስጥ ለመግባት የበቃው ግዛው እንደሚሉን ግጥምና ዜማ ለሌሎች በመስጠቱ አይደለም፡፡ ነገር ግን ሌሎች ዘፋኞች ጭንና ዳሌን የሚያሞጋግሱ ግጥሞችን በሙዚቃ አስደግፈው ሲያቀርቡልን እርሱ ግን ከዚያ ያለፈ ነገር ማየት በመቻሉ ነው፡፡ ብስለት የሌለው ቃል በማለት የቴዲን የዘፈን ግጥሞች ለማጣጣል የደፈረ ከእርስዎ ሌላ አላገጠመኝምና ወዳጄ ምናልባት ዘፈኖችን አልሰሟቸው እንደሆነ አድራሻዎን ይላኩልኝና በቅንነት ልስደድልዎ፡፡

አንድ ልጨምር፡፡ አትሌቶቻችን በስማቸው የአትሌቲክስ ማሰልጠኛ እየከፈቱ ነው ብለውናል፡፡ ነገሩ እንዴት ነው? ስለየትኞቹ አትሌቶች ነው የሚያወሩት? ኃይሌ የቱ ነው ማሰልጠኛ የከፈተው? በእጄ ያለው መረጃ የሚነግረኝ ግሎባል አዲስ ለተባለ ማሰልጠኛ መዘጋት ትልቁን ጠጠር ስለመጣሉ ነው፡፡ ለሰንዳፋው ማሰልጠኛም ከሆነ ከዚህ ቀደም ብዙ ስሞታዎች ሲነገሩ ማድመጣችን አይዘነጋም፡፡ ብርቅዬውን አትሌታችንን እናወድሰዋለን፡፡ እንኳን ተወለደልን እያልን ዘወትር ጠዋት ማታ ስለኃይሌ አምላክን እናመሰግናለን፡፡ ነገር ግን ለምን ተፈጠረ የምንልባቸው ምክንያቶች የሉንም ማለት አይደለም፡፡

ኃይሌ ከኢትዮጵያ አልፎ በአለም ትልቅ ስም መገንባት የቻለ ነው፡፡ ነገር ግን ከአትሌቲክሱ ውጪ ይህን ሰው የት አገኘነው? በእርሱ ደረጃ የሚገኙ ሰዎች ስማቸውን እየተጠቀሙ የእርዳታ ፋውንዴሽኖችን በመክፈት ለብዙዎች ደርሰዋል፡፡ በቅርቡ ቶተንሃም ሆትስፐረስ በውስት በመጫወት ላይ የሚገኘው አማኑዌል አዴባዬር ያደረገውን በምሳሌነት ላንሳ ቶጎዊው በሳምንት 160000 ፓውንድ ደሞዝ ያገኛል፡፡ ቶትንሃሞች ደግሞ በቋሚነት ሊያጫውቱት በመፈለግ እባክህን ደሞዝህን ቀንስልን አሉት፡፡ አፍሪካዊው መለስ በ..ደሞዜ ቶጎና አይቨሪኮስት ውስጥ የሚገኙ የእርዳታ ድርጅቶችን የምደግፍበት ስልሆነ መቀነስ አልችልም፡፡ ምክንያቱም ለምኖርበት ማህበረሰብ በምላሹ የሆነ ነገር መስጠት ስለሚገባኝ ነው.. አለ፡፡

Page 33: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ኃይሌ ከአዴ ባየር የተሻለ ዝና እና ተቀባይነት አለው፡፡ ነገር ግን የሚበዛውን ጊዜ እያሳለፈ የሚገኘው የራሱን ኢምፓየር በመገንባት ነው፡፡ እውቅናው ከአገሩ ያላለፈው ቴዲ ግን ብዙ እየሰራ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም መሳለሚያ አካባቢ ለሚገኙ የልጅነት ትምህርት ቤቶቹ ኮምፒውተሮችን በልግስና አበርክቷል፡፡ የጎዳና ተዳዳሪዎችን ለመርዳት በተደረገ ኮንሰርት በማቀንቀን ህይወት ታድጓል፡፡ ወ/ሮ አበበች ጎበናም ሰው አጣሁ በሚሉበት ወቅት የልጅ ትልቁን ቴዲን አግኝተውታል፡፡

እስር ቤት በተወረወረበት ስዓት (አቶ ግዛው በመኪናው ገጭቶ የታሰረ ብለውናል፡፡ ልዩነቱ የሚበዛው ኢትዮጵያዊ የቴዲ እስር ሌላ ምክንያት እንዳለው መገመቱ ነው፡፡ እርስዎን እርግጠኛ ያደረግዎት ምንድን ነው?) ፍርድ ቤት በዋስ እንዲወጡ ወስኖላቸው ገንዘብ በማጣት ብቻ ለተቀመጡ ተጠርጣሪዎች ገንዘብ በመስጠት ከቤተሰቦቻቸው እንዲቀላቀሉ አድርጓል፡፡ መቼም ሰው ገድሎ ያመለጠ በሌላ ጊዜ የአንድ ወጣት አንገት ሊቀነጠስ የቀረው የ24 ሰዓታት እድሜ ብቻ ነው ሲባል ሊደነግጥ አይችልም፡፡ ቴዲ ግን ሪፖርተር ላይ ባነበበው ዜና ተደናግጧል፡፡ እርሱ ዘፋኝ ብቻ አይደለም የምንለው ለዚህ ነው፡፡ 700..000 ብር በማውጣት ልጁን በሞት ለተነጠቀው ኢትዮጵያዊ ወጣት ደርሶለታል፡፡ አቶ ግዛው ህይወቱ ሊያልፍ የነበረው ኢትዮጵያዊ የስጋ ወንድምዎ አይደለምና የቴዲ ቤዛነት ምን ያህል ዋጋ እንዳለው ሊገባዎ አልቻለም፡፡ ይህንን የልጁ ቤተሰቦች በደንብ አድርገው ይረዱታል፡፡ ያልረዱት የመንግስት ባለስልጣን ቢሮ አልነበረም፡፡ ነገር ግን መሪዎቻችን ከዚህ ቀደም በብዙ ተፈትነው በመውደቃቸው አዲስ ነገር መፍጠር አልቻሉም፡፡ ቴዲ የፑንትላንድ አመራሮች እንደተናገሩ አድርገውት ቢሆን ኖሮ ሊሰማን ከሚችለው ሀፍረት ገላግሎናል፡፡ በሩቅ ለሚገኘው ኢትዮጵያዊ ወንድማችን ደርሶለታል፡፡ አቀንቃኙ እኮ በዚህ ገንዘብ የፈቀደውን ሊያደርግ ይችል ነበር፡፡ ወይም እንደሌሎቹ ጨማምሮ አይሱዙ ማስገባት አያቅተውም ነበር፡፡

ቴዲ የሰራው ስራ የእርሱ ኃላፊነት ወይም ግዴታ አልነበረም፡፡ ዜጎቹን የመታደግ ግዴታ የመንግስት ነው፡፡ ይህ አልሆነም፡፡ ዋናው ነገር የልጁ ህይወት መትረፉ ነው፡፡ ተወዳጁ ድምፃዊ የወጣቱን ህይወት ለመታደግ ገንዘቡን ወጪ አድርጓል፡፡ እናም ገንዘቡን ሲሆን ሲሆን መንግስት በመመለስ ለስራው እውቅና መስጠት ይጠበቅበት ነበር፡፡ ስለዚህ የተከበሩ አቶ ግርማ ገንዘቡን ልንመልስለት ይገባናል ብለዋል፡፡ እኔም እላለሁ አዎን የቴዲ ገንዘብ ሊመለስለት ይገባል፡፡ በዚህች አጋጣሚም የተከበሩ ግርማ እንቅስቃሴ ከጀመሩ የሚደርስብኝን ለማዋጣት የመጀመሪያው ሰው መሆኔን ልነግራቸው እፈልጋለሁ፡፡ እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ

Page 34: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ሞትን በሰላም ማግኘት መብታችን ነው ኤድስ ለብዙሃን ኢትዮጵያውያን ስቃይ ሆኖ ለጥቂቶች ሲሳይ ሆኖ እስከመቼ ቢንያም ተስፋዬ Bebay የክርስቶስ አህያ..የተስፋጐ መስራች)

በደሜ ውስጥ ኤች አይ ቪ ኤድስ መኖሩን ተገንዝቤ ለጓደኞቼ እና ለቤተሰቦቼ በድፍረት ገልጬ የማስተማር ተልእኮዬን

እንደጀመርኩኝ የደረሰብኝ ፈተና ህልውናዬን የሚፈታተን ነበር፤ ምሳሌ ለመጥቀስ ያህልም ከቤተሰቤም ሆነ ከጓደኞቼ ፈጽሞ መገለል ደርሶብኛል፡፡ ከቤት ወጥቻለሁ የሚያስጠጋኝ ወዳጅ ዘመድ በማጣቴ ለሶስት ወራት ያህል በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል አካባቢ በምትቆም በተበላሸች ታክሲ ውስጥ ለመኖር ተፈርዶብኛል፡፡ እንዲሁም ከተከራየሁበት ቤት ለሰላሳ አንድ ጊዜ የመወርወር ግፊቱን በፀጋ ተቀብያለሁ፡፡ በንግድ ዓለም ውስጥ የማውቃቸው አብረውኝ ሲነግዱ የነበሩ ጓደኞቼ ወደ ድርጅታችን እንዳትመጣ በማለት አግልለውኛል፡፡ በአንድ ወቅትም በራስ ሆቴል ህንፃ ላይ ሳሌም የኮምፒዮተርና የጋዜጠኝነት ማሰልጠኛ ተቋም ለመማር ተመዝግቤ ትምህርት እንደጀመርኩኝ በሁለተኛው ቀን የከፈልኩትን ብር በመመለስ ከነምህርት ቤቱ አባረውኛል፡፡ ምክንያቱን ስጠይቅ ተማሪዎቹ በጠቅላላ ካንተ ጋር አብረው መማር ስለፈሩ ነው ተባልኩኝ፡፡ በተመሳሳይ በተግባረ ዕድ ምህርት ቤት በተዘጋጀ የወጣቶች ፌስቲቫል ላይ አስተምሬ ወደ ቤተ በመመለስ ላይ እያለሁ የወረዳ ሶስት ፖሊሶች በፓትሮል መኪናቸው ጭነው ከወሰዱኝ በኋላ ምርመራ ክፍል ውስጥ አስገብተውኝ፣ ማንን ነው የምታታልለው በማለት በዱላ ቀጥቅጠው ወደ እስር ቤት ከተውኛል፡፡ በኋላም በዘውዱ ጌታቸው (በማህበራችን ፕሬዘዳንት) ጥረት ልፈታ ችያለሁ፡፡ እናም ከ1987-2004 ድረስ ለእኔ የስቃይ ጊዜዎች ናቸው፡፡ ትላንት ታሪክ ሆኖ ቢያልፍም ነገም ሚስጥር ነው አይታወቅም፤ ዛሬ ግን ለህይወት ቅርብ ነውና ዛሬን እየኖርኩኝ የበደሉኝን ይቅር ብዬ ከቂም በቀል ነፃ በሆነ መንፈሴ አስተምራለሁ፡፡ ከቫይረሱ እና ከህብረተሰቡ ጋር በሰላም መኖርን ምርጫዬ አድርጌዋለሁ፤ ለነገሩ ተስፋዬን ከማለምለም ውጪ ስ ምን አማራጭ አለኝ፡፡

የሆነ ሆኖ ለኤች አይቪ ያጋለጠኝ ከተለያዩ ሴቶች ጋር የነበረኝ ወሲባዊ ግንኙነት ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ እንደ አብዛኛቹ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ጓደኞቼ በመድረክ ሲያስተምሩ እንደሚሉት ..ጥርሴን ሳስነቅል ነው በበሽታው የተያዝኩት.. ብዬ መዋሸት አልፈልግም፡፡ በሀገራችን የማግለልና አድልዎ አጥር ጥሶ በመውጣት ትውልድን ከኤች አይ ቪ/ኤድስ ጥቃት ለመከላከል በተካሄደው ሀገር አቀፍ ዘመቻ ውስጥ ስሳተፍ የሀያ አምስት ዓመት ወጣት ነበርኩኝ፡፡ ከራሴ የህይወት ልምድ በመነሳት በተለያዩ የማስተማሪያ እና መልእክት ማስተላለፊያ መንገዶች በፖስተር፣ በሬዲዮ፣ በቢልቦርድ በተሌቪዥን፣ በጋዜጣ፣ በሙዚቃ በመጠቀም ከፍትኛ አስተዋጽኦ አድርጌአለሁ፡፡ በዚህም በእኛ ይብቃ፤ ትውልድ ይዳን የሚለውን ታሪካዊ ዓላማ ወደ ተግባር በመለወጥ ታሪክ ከማይረሳቸው ከበላይነህ ጥላሁንና ከዘውዱ ጌታቸው በመቀጠል በግልፅነትና በፅናት አስተምሬአለሁ፡፡ ክቡር የኢፌዴሪ የቀድሞ ፕሬዘዳንት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ በኤግዚቢሽን ማዕከል በተደረገ የምሳ ግብዣ ላይ በቀይ ምንጣፍ በክብር ተቀብለውኛል፡፡ እግዚአብሔር ያክብራቸውና በጣም የምወዳቸውና የማከብራቸው፤ በልቤ ውስጥም በከፍታ የተቀመጡ ሰው ናቸው፡፡ የኤድስ ታሪክ ሲወሳም ሲታወሱ ይኖራሉ፡፡ የዘንድሮውንም የዓለም ኤድስ ቀንን ምክንያት በማድረግ ተገልለው እንደተቀመጡ ያለፉትን ወገኖች በክብር በማስታወስ በህይወት ያለነውንም የአደራ ቃላችንን ለመጠበቅ ይህን ፅሁፍ አዘጋጅቼ አለሁ፡፡ እድሉን ለሰጡኝ የፍትህ ጋዜጣ አዘጋጆችም ምስጋናዬ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡

በኤድስ ታማሚዎችና ከቫይረሱ ጋር አብረው በሚኖሩ ዜጐች ላይ ህብረተሰቡ የሚያሳድረውን ተፅዕኖ የማልቀበልበትና የማልስማማበት በቂ ምክንያትና እውነት እንዳለኝ ከላይ የዘረዘርኳቸው የደረሱብኝ በደሎች ይመሰክራሉ፡፡ በማህበረሰቡ ውስጥ የኤድስ ህሙማን የሚገባቸውን ቦታ በመስጠት ካቀረብናቸው የኤድስን ስርጭት ለመግታትና ለመከላከል እጅግ አስፈላጊ የህብረተሰብ ክፍሎች ናቸው፡፡ መገለልና አድልዎን እናስወግድ በሚለው ቃል ብቻ ሳይሆን ህገ መንግስታዊ የሆኑ መብቶቻችን በሙሉ ሊከበሩ ይገባል፡፡

ባለፈው ሳምንት በፍትህ ጋዜጣ ላይ ያነበብኩት የጉለሌዋ እህታችን ላይ የደረሰው በደል አስደንግጦኛል፡፡ ከኤች.አይቪ ቫይረስ ጋር የምትኖረው ይህች ሴት ከህፃን ልጇ ጋር ምንም አይነት ተቀያሪ መጠለያ እንደሌላት እየታወቀ፤ በፍርድ ቤት የአጐቷ ወራሽ እንደሆነች እየታወቀ፤ በግብረኃይል በአጭር ጊዜ አስወጥቶ ማሸግ ምን አመጣው? በአንድ ወቅት በጥቁር አሜሪካውያን ላይ የሚፈፀመውን ግፍ አስመልክቶ የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዘዳንት የነበሩት አብርሃም ሊንከን ..በሌላ ሰው ጀርባ ላይ ጅራፍ ሲያርፍ እያየ ዝም ለሚል ሰው አዝንለታለሁ.. ብለው ተናግረው ነበር፡፡

እህቴ ሆይ፡- እኔም ዝም አልልም፤ ከጠቀመሽ በቅርቡ ያጋጠመኝን የግሌን ታሪክ ልንገርሽ፡፡ እኔ በግልፅ ለህዝብ ወጥቼ በማስተማሬ ብዙ ሰው በፍቅር ተቀብሎኛል፤ ባለመታደሌ ግን የቤተሰቤ አባላት በጠቅላላ በጥላቻና በአዋረድከን ሰሜት እንዲሁም የሚከተሉትን ያፈነገጠ እምነትና አምልኮ ባለመከተሌ ..አንተ ካልሞትክ እኛ አያልፍልንም፤ በአዋቂ ተነግሮናል.. በሚል አጉል መንፈስ በመነሳሳት ተደጋጋሚ ሰብዓዊ ጥሰቶች ሲፈጥሩብኝ፤ እኔ ግን ከሶስት ዓይነት ህመም ጋር ስለምኖር ህመሞቼን እየታገልኩኝ፣ እነሱን እየታገስኩኝ ቆየሁ፡፡ በመስከረም 12 ቀን የቲቪ መድሀኒቴን፣ የኤች አይቪ መድሀኒቴን፣ የዋርት መድሀኒቴን ሃያ ሚ.ግ ስድስት መቶ ስልሳ ብር የምገዛውን፣ የምቀይረውን ልብስ ፖሊስ አምጥተው በህግ ሽፋን በህገወጥ መንገድ ወርውረውብኛል፡፡ ልዩነቱ የአንቺ ጉለሌ፣ የእኔ ተ/ሃይማኖት መሆኑ ነው፡፡ አቤቱታዬን ይዤ መብቴ እንዲከበር አመለከትኩኝ፡፡ ምንም መልስ አላገኘሁም በኢትዮጵያችን የሚደሰኩረው ሌላ፣ የሚተገበረው ሌላ እየሆነ በጋርዮሽ ጊዜ እንኳን ሊታሰብና ሊታመን በማይችል ኋላቀር አስተሳሰብ የተወጠሩ ግለሰቦችም ሆኑ የፍትህ አካላትና የመስተዳድር ተቋማት አደብ የሚገዙት ህዝባዊ መንግስት ሲመሰረት ብቻ ነው፡፡ እስከዚያው ግን ህመምሽ ይሰማኛል፤ እናም አይዞሽ በማለት ወደ ፅሁፌ መነሻ ሀሳብ እሸጋገራለሁ፡፡

ከኤች አይቪና ከአባላዘር በሽታዎች ጋር የሚኖሩ ሰዎች ኤድስን ለመከላከልና የሚተላለፍበትን መንገድ ለመግታት ትልቁን ሚና የሚጫወቱ የህብረተሰብ ክፍሎች ናቸው፡፡ በአብዛኛው የአባለዘር እና ኤች.አይ.ቪ ኤድስ በሚገኝባቸው ሀገሮች እነዚህ ሰዎች ከቤተሰብ፣ ከጓደኛ፣ ከጐረቤት እና ከስራ ቦታ መገለልን ስለሚፈሩ አባላዘር ወይም ኤች አይቪ አለብኝ ብሎ ከማመን መገለልና ብቸኝነትን ይመርጣሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ከመረጃ፣ ከጥንቃቄ፣ ከምክር አገልግሎትና ከህክምና ራሳቸውን ያቆራርጣሉ፤ ይህ ደግሞ ሌላውን ሰው በበሽታው ለማስያዝ የተመቸ መንገድን ይፈጥራል፡፡

በበሽታው ላይ ድልን ለማምጣት አስቸጋሪ ምክንያት የሆነውና ኤች አይቪን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ትልቁ ችግር ማህበረሰቡ የፈጠረው ተፅዕኖ ነው፤ የማህበረሰቡን ተፅዕኖ መታገል በሞራል ላይ ጥሩ አመለካከት ለማምጣት ብቻ ሳይሆን የኤች አይቪ ኤድስንና የአባላዛር በሽታዎችን ብክለት እና ስርጭት ለመቆጣጠር ተገቢ መንገድ ነው፡፡

Page 35: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

በአካባቢያችን ሁለት ወረርሽኞች አሉ፤ የመጀመሪያው ኤድስ ሲሆን ሁለተኛው ኤድስን በተመለከተ ያለው ተፅዕኖ /ASSR AIDS/ Acute social stigma regarding Aids ነው፡፡ የህክምና ሳይንስ እንደሚያስረዳን ሁለተኛው ዝም ብሎ የሚተላለፍ ሳይሆን በወሬ፣ በመጠቃቆም፣ ስሜታዊ አመለካከትን በመንዛት አዝናኝ ሚዲያዎች እና ማህበራዊ ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ አላስፈላጊ የኤድስ ሰበካዎችን /ASSRAIDS/ ሲሰነዝሩ ነው፤ ይህን ግን ከኤች አይቪ ቫይረስ ጋር አብረን የምንኖር ዜጐች የማንቀበለውና የማንስማማበት በቂ ምክንያት እና ሐቅ አለን፡፡ የተወሰኑትን ለማየት ብንሞክር፡-

1. ኤድስ ሀጢአት ነው፡፡ የሀጢአት ውጤት ደግሞ ሞት ነው የሚሉ አሉ፣ በኤድስ የተያዘ ሰው ሀጢዓቱ ነው ያመጣበት፤ ስለዚህ ሊሞት ይገባል የሚለው አመለካከት በህብረተሰቡ ውስጥ ያለ ይመስለኛል፡፡ በሬዲዮና በቴሌቪዥን ኤድስን ለመከላከል በሚደረግ ትምህርትና ፌስቲቫል ላይ ..ቁጣህን አብርደው.. እየተባለ ሲሰማ ስለነበረ ህዝቡም መፍትሄውን ከሰማይ አንጋጦ እንዲጠብቅ ተደርጐአል፡፡ ኤች አይቪ ምድር ላይ የሚንቀሳቀስ እና የሰው ልጅ ስሜቱን ለመወጣት በሚያደርገው ወሲባዊ ግንኙነት የሚተላለፍ በሽታ ሆኖ ሳለ ከሰማይ ለሀጢያተኞች የወረደ መቅሰፍት ተደርጐ በመታየቱ ጠቅላላ የኤድስ ታማሚ በአምላክ ቁጣ የተቀጣ ሀጢአተኛ ተደርጐአል፡፡ ይህም እምነት በህብረተሰቡ ውስጥ ሰርፆ በመግባቱ የሚገባንን ቦታ እንዳናገኝ ተገፍተናል፡፡

2. በኤድስ የተያዙ ታማሚዎችን ስናቋቁም እና ስናስታምም ጊዜያችንንና ገንዘባችንን የምናጠፋበት ምንም ምክንያት የለንም፤ የሚል አቋም ያላቸው ቤተሰቦችም አሉ፡፡

3. ኤች አይቪ ኤድስ የሚጠፋው በሽታው የያዛቸው ሰዎች ተገልለው በአንድ ካምፕ ውስጥ ሲኖሩ ብቻ ነው የሚሉ አሉ፡፡ የተለየ ቦታ ተሰጥቷቸው ለምን ለብቻቸው አይቀመጡም እያሉም በድፍረት ይናገራሉ፡፡ የዚህ አይነት ንግግር የሚናገሩ ሰዎች መጥፎ አመለካከታቸውን በይፋ አውጥተው አይከረከሩበትም፤ ነገር ግን በመንደራቸው ተሸሽገው መንደራዊ አስተሳሰባቸውን /village mentality/ በመጠቀም የበሽተኛውን ሞራልና ስብዕና ይቀጠቅጡታል፡፡

4. አንድ በበሽታው የተያዘ ሰው ራሱን አጋልጦ ብዙ ሰዎች በተሰበሰቡበት፤ በትምህርት ቤቶች፣ በእድር፣ በቤተክርስቲያንነት፣ በጐዳናዎች፣ ላይ ትምህርት የመስጠት ዘመቻ ቢያካሂድ ሶስት ዓይነት ..ምክሮችም.. ያጋጥሙታል፡፡ የመጀመሪያው ባለአወሊያ የታወቁ ሼክ አሉ፤ እሳቸው ይፈውሱሃል የሚል ሲሆን፤ ተከታዩ ደግሞ በእግዚአብሔር የተቀባ ፓስተር አለ፤ በእሱ ትፍወሳለ የሚል ነው፡፡ ሌላው ደግሞ ..ስምንት ዓመት ሙሉ እህል ያልቀመሱ ባህታዊ አሉ.. እሳቸው ጋር ሂድ በቅብዓ ቅዱስ ይፈውሰሱሀል የሚሉ ናቸው፡፡ በእርግጥ ሁሉም ቢያድኑኝና ቢፈውሱኝ ደስተኛ ነኝ፡፡ የማንንም ሃይማኖትና እምነት አልቃወምም፤ ሁሉም የሚፈልገውን እምነት የመከተል መብት አለውና፡፡ ችግሩ ግን እኔም የፈለግኩትን እምነትና ሃይማኖት የመከተል መብት እንዳለኝ አለማወቃቸው ነው፡፡ ነጋ ጠባ የእነሱ ጉትጐታ ልብን ያወልቃል፤ የእነሱን እምነት ካልተቀበልክ ደግሞ ኤች አይቪ አለብኝ እያለ የሚያስተምረው ለብር ብሎ እንጂ ውሸቱን ነው እያሉ መልካም ስምህን ለማጉደፍ ይሞክራሉ፡፡ በዚህ ሂደት የሚያሳዝነው ግን የምትከፍለው መስዋዕትነት ዋጋ ማጣቱ ነው፡፡

የኤድስ በሽተኛ ማለት አእምሮው የጨለመ፣ ፍቅር የተራበ እውነት የተጠማ ሁልጊዜ በፀፀትና በንዴት የሚመላለስ የህብረተሰቡ አንዱ ክፍል ነው፡፡ የኤድስ በሽተኛ የሚፈልገው ፍቅርና እንክብካቤ ነው፡፡ እንክብካቤ ደግሞ የሚገለፀው አንዳችን ለአንዳችን በሚኖረን መተሳሰብ ላይ ነው፡፡ ከቫይረሱ ጋር የምንኖር ሁሉ ላልተያዘው ሰው የማሰብና የመጠንቀቅ ሀላፊነት ሲኖርብን ጤነኛው ህብረተሰብ ክፍል ደግሞ ከማግለል እና አድልዎ ከመፈፀም መቆጠብ አለበት፡፡ ማንም ሰው ፈልጐ አይታመም፡፡ ከሱፐርማርኬት አልገዛነውም፡፡ እንዲሁም የወደቀን መርገጥ ከጀግና አያስቆጥርምና በተግባር የታጀበ ፍቅር እንፈልጋለን፤ ፍቅር ከማንኛውም ሰው ሰራሽ መድሀኒት የበለጠ የፈውስ ቅባት በውስጡ አለውና፡፡

ፍቅር ማለት በወንድና በሴት የሚደረግ ግንኙነት ብቻ አይደለም፡፡ ፍቅር ማለት ታሞ በአልጋ ላይ የወደቀውን በሽተኛ ማስታመም፣ ማፅናናትና ማበረታታት ጭምር ነው፡፡ ከዚህ በፊት በኤድስ የሞቱ ወገኖቻችን በሀዘንና በመገለል ህይወት አስጠልታቸው ሞትን እንኳን በሰላም መቀበል አልቻለም፡፡ ክቡሩ የሰው ልጅ ቢያንስ ሞቱን በሰላም ማግኘት መብቱ ነው፡፡ የኤድስ በሽተኛ ፍቅር ከተሰጠው መንፈሳዊ መሰናድኦ አድርገው ሞትን በፀጋ ይቀበላሉ፡፡

በተለይ እንደእኔ ከቫይረሱ ጋር አብረው የሚኖሩ ዜጐች እንዲሁም ኤድስ ያለ ወላጅ ያስቀራቸው ህፃናት በህብረተሰቡ በኩል ተገቢውን ፍቅርና እንክብካቤ ማግኘት እንዳለባቸው አጥብቄ እመክራለሁ፤ ኤድስን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ያለውን ተፅዕኖ ፊት ለፊት መጋፈጥ ይቻላል፤ የማይለወጥ ነገር ቢኖር ራሱ ለውጥ ብቻ ነው፡፡ እናም ምድራዊ ተልዕኮዬን በድል አጠናቅቄ እስካሸልብ ድረስ ለእግዚአብሔር ፀሎቴን የማደርሰው ተጨማሪ እድሜ ሰጥቶኝ ቤተሰቤ ለሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ የድርሻዬን ለማበርከት ነው፡፡ /ይቀጥላል/

Page 36: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

አለም አቀፍ

“በአልሸባብ ላይ ድል እየተቀዳጀሁ ነው” ኬኒያ “የኬኒያ ጦር እንደተዋረደ የኢትዮጵያም ጦር ይዋረዳል” አልሸባብ

ልዑል ሰንደቁ እ.ኤ.አ ከ1991ዓ.ም በኋላ በተቀሰቀሰ የእርስ በእርስ ጦርነት መንግስት አልባ የሆነችው ሱማሊያ ለአካባቢው አገራትና ለአለም ስጋት

ሆናለች፡፡ በተለይ በ2006ዓ.ም በአገሪቱ እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው አልሸባብ አል-ኢስላሚያ (Al Shabaab AlIslamiya) የተባለው አሸባሪ በሱማሌያ የነበረውን ቀውስ የበለጠ እንዳባባሰው ይታወቃል፡፡ እስላማዊ ጽንፈኛ በሆነው በአልሸባብ ምክንያት በርካታ ሱማሌያዊያንና የውጭ አገር ዜጐች ለህልፈት የተዳረጉ ሲሆን፣ ሌሎች ደግሞ ቀያቸውን ለቀው ተሰደዋል፡፡ በሱማሊያ የፌዴራል የሽግግር መንግስት ቢመሰረትም አልሸባብ አብዛኛውን ደቡባዊውን ክልል በቁጥሩ ስር አድርጓል፡፡ በሌላም በኩል የሽግግር መንግስቱ የአልሸባብን እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር ያለው አቅም ደካማ መሆኑና እርስ በእርስ በመከፋፈሉ አንድነት እንደሌለው ይገለፃል፡፡ በተጨማሪም በርካታ የሽግግር መንግስቱ ባለስልጣናት በሙስና ውስጥ መዘፈቃቸው ይጠቀሳል፡፡

አንዳንድ አለም አቀፍ ሚዲያዎች ደግሞ የሶማሊያ የፌደራል የሽግግር መንግስት ከሞቃዲሾ ውጭ ያሉትን ግዛቶች መቆጣጠር እንደማይችል ዘግበዋል፡፡ ከአልሸባብ ባልተናነሰ የተለያዩ ተቃዋሚ አንጃዎች መኖራቸው ለሽግግር መንግስቱ እጅግ ፈታኝ መሆናቸው ይገለፃል፡፡

በጥቅምት ወር ውስጥ ከመንግስት ሕንፃ አካባቢ በሚገኝ ቦታ ላይ በደረሰው ተደጋጋሚ የቦንብ ፍንዳታ ወደ 20 የሚጠጉ ሶማሌያዊያን ሲሞቱ በርካቶችም ሊቆስሉ ችለዋል፡፡ አልሸባብ በዋና ከተማዋ እያደረሰ ካለው ቦንብ ፍንዳታ ከተማዋን እንደገና ለመቆጣጠር መቃረቡን ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ከመስከረም ወር ጀምሮ ከሱማሊያ ውጭ በመንቀሳቀስም በኬኒያ ድንበር ላይ አደጋ ማድረሱ ይታወቃል፡፡ በኬኒያ ድንበር ላይ ደብሊይ የተባለው የገበያ ቦታ ላይ ከኬኒያ ወታደሮች ጋር ውጊያ አካሄዷል፡፡

ከፍተኛ የቱሪስት ገቢ የምታገኘው ኬኒያ አልሸባብ ወደ አገሪቷ በሚገቡ ቱሪስቶች ላይ የሚፈጽመው ጥቃት ስጋት ውስጥ በመግባቷ በጥቅምት ወር ላይ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወታደሮችን ወደ ደቡባዊ ሱማሊያ በመላክ ከአልሸባብ ጋር ውጊያ አድርገዋል፡፡ በተጨማሪም የኬኒያንና የሱማሊያ መንግስት አልሸባብን በጋር ለመዋጋት ስምምነት አድርገዋል፡፡ ይሁን እንጂ የሱማሊያ የፌደራል የሽግግር መንግስት ፕሬዘዳንት የሆኑት ሼክ ሸሪፍ ሼክ አህመድ፣ ኬኒያ ከአልሸባብ ውጭ በንፁሃን ሱማሌያዊያን ላይም ጥቃት እየፈጸመች ነው በማለት ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡

በ2006 የሶማሊያ እስላማዊ ፍርድ ቤቶችን ህብረት በመቃወም በሶማሊያ የሽግግር መንግስት ጥሪ እንደተደረገለት የገለፀው የኢትዮጵያ መንግስት ወደ አካባቢው ጦሩን በማሰማራት አክራሪ ኃይሉን ከሞቃዲሾ በማጥፋት ከሶስት አመት ቆይታ በኋላ መመለሱ ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ በሱማሊያ ከተሰማራው የውጭ ኃይል ሁሉ አገሪቷን በተሻለ ሁኔታ ማረጋጋት የቻለው በ2007 ወደ ሱማሊያ የዘመተው የአፍሪካ ህብረት የሰላም አስከባሪ ጦር ነው፡፡ የአፍሪካ ህብረት የሰላም አስከባሪ ጦር በሱማሊያ የሚገኘው በርካታ የአልሸባብ ይዞታዎችን ነፃ ለማድረግ እንደቻለ ይጠቀሳል፡፡

የኬኒያ ጦር ከስድስት ሳምንታት በፊት በደቡባዊ ሶማሊያ በኩል በመግባት በአልሸባብ ላይ በከፈተው ጦርነት የአማፂ ኃይሉ ይዞታዎች ላይ በእግረኛ ወታደሮችና በጦር ጀቶች እገዛ የታጀበ ድብደባ አድርሷል፡፡

ባለፈው ሳምንት የወጡ መረጃዎች እንደሚያሳዩት፣ የኬኒያ ወታደራዊ ጥቃት የአልሸባብ ጠንካራ ይዞታ የነበረችውን የኮልቢዮን እና የቡርን ከተማ ለማስለቀቅ የቻለ ሲሆን፣ በጦርነቱ ሁለት የኬኒያ ወታደሮች ሞተዋል፡፡

በኬኒያ መከላከያ ኃይል ውስጥ ከፍተኛ የጦር አዛዥ የሆኑት ኮሎኔል ሳይረስ አጉና እንደተናገሩት፣ ..ለአልሸባብ ወታደራዊ ታክቲክ መልስ መስጠት ባንችል ኖሮ አሁን የተገኙት ወታደራዊ ስኬቶች እውን ሊሆኑ አይችሉም ነበር.. በማለት ተናግረዋል፡፡

ኬኒያ በአልሸባብ ላይ በከፈተችው ጦርነት የምትከተለው ወታደራዊ ስትራቴጂ የአማፂ ኃይሉን የገቢ ምንጮች ሰንሰለትን መበጣጠስ ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡

ባለፈው ሳምንት ሲናይ በተባለች የሱማሌያ ግዛት ውስጥ በተከፈተው ጦርነት አምስት የአልሸባብ ታጣቂዎች የተገደሉ ሲሆን፣ ኮልቢዩ የተባለች ከተማም በኬኒያ ጦር ቁጥጥር ስር ገብታለች፡፡ ከተማዋ ለኬኒያ ጦር ያላት ጠቀሜታ ወሳኝ እንደሆነ ተገልጿል፡፡

በአልሸባብ ላይ የተከፈተው አዲሱ ጦርነት በተለይ የኬኒያ፣ የኢትዮጵያና የሱማሌያን ድንበር ማዕከል ያደረገ ሲሆን፤ ለወታደራዊ ጥቃት ስኬታማነት የአገሪቷ ዜጐች የሚሰጡት መረጃ ከሁሉም በላይ ወሳኝ ነው ተብሏል፡፡

ከሁለት ሳምንት በፊት በናይሮቢ ተገኝተው የመከሩት የሶማሊያ፣ የኬኒያ እና የኡጋንዳ መሪዎች በአልሸባብ ላይ የተከፈተውን ጦርነት የገመገሙ ከመሆኑም በላይ በተለይ ኬኒያ ከከፈተችው ጦርነት ጋር ተያይዞ ኬኒያ በከፍትኛ ሁኔታ በስደተኞች እየተጥለቀለቀች መምጣቷን ተከትሎ ሰብዓዊ እርዳታ ለማቅረብ እንደተቸገረች ገልጻለች፡፡

ከአልሸባብ ቁጥጥር ስር የወጡ የደቡብ ሱማሌያ ከተሞችን በራሳቸው በሶማሊያዊያን እንዲተዳደሩ እየተደረገ ይመጣል የሚሉት ኮሎኔል አጉና፣ ኬኒያ እንደ ወራሪ ሀይል ተደርጋ መቆጠር አትፈልግም ይላሉ፡፡

አሁን አሁን አልሸባብ ለቆ በወጣባቸው ከተሞች ህይወት ቀስ በቀስ ወደቀድሞ ቦታው መመለሱን አንዳንድ ምንጮች የገለፁ ሲሆን፤ ከዚህ ጋር ተያይዞ የአልሸባብን የገቢ ምንጭ ለማድረቅ በመሬት ላይ የሚሰሩ ውጤታማ የስለላ ስራዎች በአግባቡ እየተካሄደ መሆኑ ተገልጿል፡፡

በድጋሚ ወደ ሱማሊያ የገባው የኢትዮጵያ ጦርም በአካባቢው ከተሰማራው የአፍሪካ ህብረት ሰላም አስከባሪ ኃይልና በቅርቡ ሶማሌያ ከገባው የኬኒያ ጦር ኃይል ጋር ተቀላቅሎ አንድ የተጣመረ ኃይል እንዲፈጠር ተወስኗል፡፡

ከአንድ ሳምንት በፊት በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የተመራው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግስታት ድርጅት (ኢጋድ) የመሪዎች ስብሰባ ላይ ኢትዮጵያ በአልሸባብ ላይ ለሚካሄደው ዘመቻ ድጋፍ እንድታደርግ በይፋ ጥያቄ ቀርቦላታል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የሆኑት አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ለአገር ውስጥ ጋዜጠኞች ሲናገሩ፣ ኢትዮጵያ የሱማሊያን የሽግግር መንግስት፣ የአፍሪካ ህብረት የሶማሊያ የሰላም አስከባሪ ሀይልን እና ኬኒያን የምትረዳው በወታደራዊ፣ በዲፕሎማሲያዊና በፖለቲካዊ ነው ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ባለፈው ሳምንት የአልሸባብ ቃል አቀባይ እንደገለፀው የኢትዮጵያ ጦር ወደ ሶማሊያ ተመልሶ የገባው፣ የኬኒያን ወታደራዊ ጥቃት መክተን ካሸነፍን በኋላ ነው ብሏል፡፡ የአልሸባብ ቃል አቀባይ አያይዞም ሲገልጽ ..የኢትዮጵያ ወታደሮች ከዚህ በፊት ሶማሊያ ላይ ዘምተው አስከሬን አሸክመናቸው ነው የላክናቸው፤ አሁንም ተመሳሳይ ነው.. ብሏል፡፡ በሌላ በኩል የሶማሊያ የሽግግር መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣን የኢትዮጵያ ጦር ወደ ሱማሊያ እንዲገባ ፕሬዘዳንት ሼክ ሸሪፍ እንደማይፈልጉ በመግለጽ፣ ጦሩ እንዳይገባ ለማድርግ አቅሙ ስለሌላቸው ግን ምንም ማድርግ እንደማይችሉ ገልጸዋል፡፡

Page 37: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

እውነትም እንፈራለን! በዳንኤል ሰለሞን

ፒያሳ አካበቢ የሚገኝ አንድ አነስተኛ ኢንተርኔት ካፌ ውስ ተቀምጬአለሁ፡፡ ባለቤቱ ወዳጄ ነው፡፡ ሰሞኑን ስለተከሰቱ ጉዳዮች እየተጨዋወትን እያለ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ወደ ኢንተርኔት ቤቱ መለስ ቀለስ ማለት ስላበዙት ..ጥቁር እንግዶች.. ደብቆ የያዘውን ምስጢር ሹክ አለኝ፡፡ ..ጥቁር እንግዶቹ.. ወደ ኢንተርኔት ካፌው መምጣት የጀመሩት ከሁለት እና ሶስት ወራት ወዲህ እንደሆነ ነገረኝ፡፡ ..ጥቁር እንግዶቹ.. አመጣጣቸውም ሆነ የሚፈጽሙት ድርጊት ተመሳሳይ እንደሆነ አስረዳን፡፡

..የሚመጡት በተመሳሳይ ሰዓት ነው፡፡ ቀጥሎ ሰዎች የሚያዩዋቸውን ድረ ገጾች ይቃኛሉ፡፡ አልፎ አልፎ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎችን ጠርተው ምክር ይሰጣሉ.. አለኝ፡፡

የሰማሁትን ለማመን አስቸገረኝ፡፡ ..ጥቁር እንግዶቹ.. እነማን እንደሆኑ ብጠረጥርም ለማረጋገጥ ጓደኛዬን ጠየቅሁት፡፡ ..ማንነታቸውን ጠይቀህ ታውቃለህ? እንዴት ነው የሚንቀሳቀሱት? ምን ዓይነት ናቸው?.. ጥያቄዎቼን አከታተልኩኝ፡፡ ..ጱረ..... ያምሃል እንዴ?.. በመገረም አየኝ፡፡ ..በፍጹም ጠይቄ አላውቅም፡፡ ፊታቸው ላይ ካለው የባለቤትነት ስሜት አንጻር

እነማን እንደሆኑ እረዳለሁ፡፡ የመጀመሪያ ሰሞን ግራ እጋባ ነበር፡፡ በኋላ ላይ ግን በጋራ ነው የምንሰራው.. ሲል ነገሩን ለማለዘብ ቀለደ፡፡ ..ትርፍ የምትጋሩ ነው የምትመስለው.. ቀልዱን በሽሙጥ አጀብኩት፡፡ ..ስንት ሆነው ነው የሚመጡት? አንተ ግን በገዛ ቤትህ እንዴት ጥያቄ መጠየቅ አቃተህ?..፡፡ ጥያቄዬ አላባራም፡፡ ወዳጄም መልስ መለሰልኝ፡፡ ..መጀመሪያ... እፈራለሁ፡፡ ቀጥሎ ደግሞ ቢዝነሴን እፈልገዋለሁ፡፡ ስራዬን እስካላቆሙኝ ቢመጡ ቢሄዱ ምን አገባኝ?.. አለኝ፡

፡ ..በቃ.. ፍርሃታችን እዚህ ደረጃ ደርሷል.. ስል ራሴን ጠየቅሁ፡፡ ከቀናት በኋላ ታክሲ ላይ ያጋጠመኝ ግን ፍርሃታችን የት ጥግ

እንደደረሰ አመላክቶኛል፡፡ ያን ቀን ሁሌም እንደማደርገው በእለቱ የታተሙ ጋዜጦችን በእጄ አንጠልጥዬ ነበር ወደ ታክሲ የገባሁት፡፡ አጠገቤ የተቀመጠ ወጣት ..ይቅርታ ልየው.. ሲል ከያዝኳቸው ጋዜጦች አንዱን እንድሰጠው ጠየቀኝ፡፡ ..ፍትህ.. ጋዜጣን ሰጠሁት፡፡ የጋዜጣውን የፊት ለፊት ገጽ ገረፍ ገረፍ አድርጎ አየውና ጥያቄውን ወረወረ፡፡

..አትፈራም.... ግራ ገብቶት ጠየቅኩኝ ..ምኑን?.. ..ጋዜጣ በአደባባይ ይዘህ ስትሄድ ነዋ? በተለይ እንዲህ አይነቱን ጋዜጣ?.. ጋዜጣውን በእጁ እየጠቆመ መለሰልኝ፡፡ ..እንዴ... ፍቃድ ኖሮት የሚታተምና በአደባባይ የሚሸጥ ጋዜጣ እኮ ነው?.. ..ሆሆይ..... ወጣቱ ቀጠለ፡፡ ..ሰሞኑን እየሆነ ያለውን አልሰማህም? ህዝቡ ፣አየገባ፣ እኮ ነው..፡፡ ከዚያ ደንገጥ ብሎ ቀጠለ፡፡

..እኔ እንኳን አልከታተልም ሲያወሩ ምናምን ስሰማ ግን አርፈን መቀመጥ እንዳለብኝ አስባለሁ.. አለኝ፡፡ መልስም ሳልሰጠው በትካዜ በመስኮት ወደሚታዩት የአዲስ አበባ ፎቆች ፊቴን መለስኩ፡፡ ጭንቅላቴ ውስጥ የነበረው ቃል

አንድ ብቻ ነበር፡፡ ..ፍርሃት.. ፍርሃት.. ፍርሃት.. ፍርሃት.... እውነትም እንፈራለን፡፡ ግን ለምን? ፍርሃት ለኢትዮጵያውያን አዲስ አይደለም፡፡ አውቀንም ሆነ ሳናውቀው እያበረታታን ካሳደግነው አለመተማመን መንጭቶ ዛሬ

የሁላችንም የእለት ተእለት እንቅስቃሴ በዚሁ የተሞላ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ ጎረቤታችንን፣ ጓደኛችንን፣ የስራ ባልደረባችንን፣ የመጠራጠር ማህበራዊ አባዜ ለአስፈሪዎቻችንም የተመቻቸ ከባቢ የፈጠረላቸው ይመስላል፡፡ እንኳን ጠንከር ያለ የሚያስደነግጥ ዜና በየምሽቱ አይተን ቀርቶ እርስ በእርሳችን መጠባበቅ ከጀመርን አመታት ተቆጠሩ፡፡ አብዮቱን ተከትሎ የማጣው የጥርጣሬ አባዜ የወለደው ፍርሃት፤ ሲደበዝዝ ሲደምቅ ከርሞ አሁን ደግሞ ..ፏ.. ብሎ መታየት ጀምሯል፡፡

ዛሬ ታክሲ ውስጥ አጠገባችን የሚቀመጠውን ሰው ..አሸባሪ ነው.. ወይስ አይደለም በሚል ጥርጣሬ ነው የምናየው፡፡ የሌሎች ሰዎችን ፖለቲካ ቀመስ ጨዋታ ላለመስማት የሚጠነቀቁ ብዙዎች ያሉባት ሀገር ሆናለች የዛሬይቱ ኢትዮጵያ፡፡

መንግስት ከአመታት በፊት በዘራው የእርስ በእርስ የመጠራጠርና የመፈራራት አባዜ ላይ ልዩነትን የማጉላት ፖለቲካ ሲጨምርበት ከርሟል፡፡ የምድር ውጤቱን ግን እንደሰሞኑ ጎልቶ ያየሁበት ጊዜ በግሌ ትዝ አይለኝም፡፡ የትኛው አሸባሪ እንደሚያስብል በማይታወቅበት ሁኔታ ቀጣዩ አሸባሪ ላለመሆን አሊያም ላለመባል ከፍተኛ ጥንቃቄ ውስጥ ያለን ነው የሚመስለው፡፡

ከሰሞኑ በተናጥል ሆነው ጋዜጣ የሚያነቡ ሰዎች ቁጥር ቀንሷል፡፡ በኢንተርኔት ካፌዎች ውስጥ ሆኖ የተቃውሞ ድምጽ የሚያሰሙ ድረ ገጾችን መመልከት ብርድ ብርድ የሚያሰኘው ሰው በዝቷል፡፡ ከሀገር ውስጥ ሆኖ የፌስ ቡክ ገጾች ላይ በመንግስት ድርጊቶች እና እየወሰዳቸው ባሉ እርምጃዎች ላይ ሂስ ወይም ተቃውሞ መግለጽ በጣሙኑ ተገድቧል፡፡ በፌስ ቢክ ገጻቸው የተለያየ ሃሳቦችን ያንጸባርቁ የነበሩ ወጣቶች ቁጥር እየመነመነ መጥቷል፡፡ በርትተው የቀጠሉትም ከገጻቸው ሲጠፉ በስጋት የምንጠያየቅበት ጊዜ ሆኗል፡፡

ማን ይጠቀማል? ዜጐች /ተገዢዎች የሚለው አባባል ይበልጥ ያስማማል መሰል/ በመፍራታቸው ማን ይጠቀማል? ሁልጊዜ ለራሴ የማነሳው

ጥያቄ ነው፡፡ ነገሩን ከላይ ከላይ ስናየው አዎ.. መጀመሪያ መንግስት ይጠቀማል፡፡ ዜጐች ለማንበብ ሲፈሩ አማራጭ መረጃ አያገኙም፡፡ አማራጭ መረጃ ያላገኙ ዜጐች አይጠይቁም፣ አይቃወሙምም፡፡ መጠየቅና መቃወም ቀርቶ ሀሳባቸንው ለጓደኛቸው እንኳን ለመግለጽ ይፈራሉ፡፡ ስለነባራዊው ሁኔታ መወያየት አደጋ እንዳለው ይገምታሉ፡፡ ስለዚህ በፍፁም አይወያዩም፡፡ ያልተወያዩ ዜጐች ደግሞ የተባበረ ጥያቄ፣ የተያያዙ መልሶችና የጋራ መግባቢያ የላቸውም፡፡ ስለዚህ የማይግባቡ ህዝቦች፣ የማይተዋወቁ ህዝቦች የጋራ ጥያቄ ለማንሳት ይከብዳቸዋል፡፡

ፍርሃትን ከላይ ከላይ ስንመለከተው መንግስት የሚያበረታታውና የሚደግፈው አንድ ነገር ቢሆን አይገርመንም፡፡ የገዢዎች እድሜ ማራዘሚያ መሆኑንም ለመገመት ቀላል ነው፡፡ ህዝብም ቢሆን በፍርሃት ተጠቃሚ እንደሆነ ማሰቡ የማይቀር ነው፡፡ ከተለመደው የመፈራራት ባህል አንድ እርከን ተሻግረው ደፈር ብለው የሚናገሩ ወይም የተሸፈኑ ሃቆችን የሚያወሩ የደረሰባቸውን እና እየደረሰባቸው ያለውን በምሳሌነት በማጣቀስ ..ዝም አይነቅዝም.. ይላሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ..መድፈር.. ትልቅ ሞኝነት ፍርሃት ደግሞ የብልጥነት መገለጫ ከሆኑ ሰነባበቱ፡፡

Page 38: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ዜጐች የሚፈሩት የሚያስፈራ ነገር ስላለ ብቻ ሳይሆን መንግስት ሲፈራም ጭምር ነው፡፡ የማይፈራ መንግስት ህዝቦች እንዲፈራ አያደርግም፡፡ አያበረታታም፡፡ የሚፈራ ህዝብ አለ ማለት የሚፈራ መንግስት፣ የሚሸፈን፣ የማይወራ ነገር ያለው መንግስት አለ ማለት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ፊት ለፊት ለማየት ወደሚያስቸግረው የፍርሃት ጉዳዮች ይወስደናል፡፡

አማራጭ ሀሳቦች አለማቅረባቸው ለሀገሪቱ እድግት ይጠቅማል የሚለውን ጥቅል እና የተለመደ አባባል ትተን ራሱ መንግስት ላይ የሚያመጣውን ጉዳት እንመልከት፡፡ የሚፈራ ህዝብን ማስተዳደር ትልቅ ችግሩ የተዛባ መረጃ የመስጠት እድሉ ሰፊ መሆኑ ነው፡፡ የሚያስበውን የማይናገር ህዝብ አደጋ አለው፡፡ ዝም የሚል ህዝብ ሁሉም ነገር ተስማምቶት እየኖረ ነው ማለት አይደለም፡፡ ተናገር ተብሎ ሲገደድ የሚናገረውም ከሚያስበው በተቃራኒ ያለውን ነው፡፡

ይህ በፊት ለፊት መድረኮች ሲሆን የሚስተዋል ነው፡፡ ኦፌሴሊያዊ ባልሆኑ የመረጃ መሰብሰቢያ መዋቅሮች ያለው ሁኔታም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ በዚያ ላይ በየሰፈሩ የተሰማሩ መረጃ ሰብሳቢ /ሰጪ / አካላት ከህዝቡ የሚደርሳቸውን በቀጥታ ወደ መንግስት የሚልኩ አይደሉም፡፡ ህዝቡ የተናገረውን ወይም ተናገረ የተባለውን ከአንዱ ወደ አንዱ ሲያቀባብሉት በስተመጨረሻ ለቁንጮዎቹ ሰዎች የሚደርሰው መረጃ የተዛባና እውነተኛውን የህዝብ ሁኔታ የማያሳይ ይሆናል፡፡

ጎልተው የሚታዩት የኑሮ ውድነት እና የድህነት መረጃዎች እንኳን ባሉበት ደረጃ ወደላይ አይሻገሩም፡፡ በመሆኑም የመረጃ እጥረት ያለበት አገዛዝ የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ መጨረሻው አያምርም፡፡ ህዝብና ገዢዎች በተለያየ መንገድ የሚሄዱበት አገዛዝ ምንም ጊዜው ይዘግይ እንጂ መውደቁ አይቀርም፡፡

..አይ... እየመከርኩ ነው.... አሁን አሁን ህዝቦች የማይፈሩበት ጊዜ የማይመጣ ይመስል ጀምሯል፡፡ ፍርሃት ግን በተፈጥሯዊ ባህሪው ገደብ ያለው ስሜት

ነው፡፡ ተፈጥሯዊ የገደብ መጠኑ ያለፈ እለት ደግሞ በጣም መፍራት ከመድፈር እኩል ይሆናል፡፡ በጣም ከፍትኛ ደረጃ ላይ የሚደርስ ፍርሃት በቅጽበት ወደ ድፍረት የሚቀየርበት እድል በጣም ሰፊ ይሆናል፡፡

ገደቡን ያለፈ የፍርሃት ስሜት ማባባል የሰለቸው ህዝብ (ብዙ ቁጥር መሆኑን ሳንዘነጋ) አንድ ቀን ሊወስደው የሚችለው ደፋር እርምጃ ውጤቱ ያልተጠበቀ እና አስደንጋጭ ሊሆን ይችላል፡፡

..በፀረ-ሽብር ህግ..፣ በእርስ፣ በክትትል ስጋት፣ የሚኖር ህዝብ በጥቂት ጊዜ ውስጥም ባይሆን የሆነ ጊዜ ላይ በቃ.. ሊል እንደሚችል መጠርጠር ጥሩ ነው፡፡ ..የሚፈራ፣ የሚደበቅና የሚያስፈራራ መንግስት አልፈልግም.. የሚልበት ጊዜም እንደሚመጣ ማሰብ ጥሩ ነው፡፡

መንግስት ላለመፍራት መውሰድ ያለበት እርምጃዎች አሉ፡፡ የማይፈራ መንግስት የማይፈራ ህዝብ እንደመፍጠሩ መጠን የተሻለ የመረጃ ፍሰት ለመፍጠር እና አዳማጭ መንግስት ለመሆን መዘጋጀት ይኖርበታል፡፡ አለያም አልሰማም ከሚል መንግስት ይልቅ አይኑን የሚከፍት፣ ጆሮ የሚሰጥ መንግስት አላማው ስልጣን ማረዘምም እንኳን ቢሆን ሳይፈራ ለረዥም ጊዜ ስልጣን ላይ መቆየት ይችላል፡፡

በእኛ በተገዢዎች በኩልስ ማድረግ የምንችለው ምንድን ነው? ይህ የፍርሃት፣ የመፈራራት እና የማስፈራራት ጊዜ በአጭር እንዲቀጭ ቀን መቁረጥ ከባድ ቢሆንም ከፈሪ መንግስት እንዲሰውረን ማድረግ ያለብንን ለመነጋገር ቢያንስ መፍራት አይኖርብንም፡፡ በእርግጥ ለትግል ራሳችንን ሰጥተናል የሚሉት የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ለንግግራቸው በሚጠነቀቁበት በዚህ ወቅት ..አትፍሩ.. ማለት ከባድ እንደሆነ ይገባኛል፡፡ ግን መሞከር አለብን፡፡ እንደ ዶክተር ኃይሉ አርአያ ሁኑ ማለቴ ግን አይደለም፡፡ የመድረክና የአንድነት ፓርቲ አመራር የሆኑት ዶክተር ኃይሉ አርአያ የሰሞኑን ..የአሸባሪዎች.. እስር ተከትሎ ይህንን ተናገሩ፡፡ በ..ፊዚክስ.. አሉ ዶክተር ኃይሉ በ..ፊዚክስ ለእያንዳንዱ ተግባር ተመጣጣኝ የምላሽ ተግባር አለው፡፡ መንግስት በሚወስዳቸው እርምጃዎች ተያይዞ የሚመጣውን የተግባር ምላሽ መገመት አለበት.. አሉ፡፡ ..መንግስትን እያስጠነቀቁ ነው ወይ?.. ተብሎ ጥያቄ ቀረበላቸው፡፡ መልሳቸው በፍርሃት የተለወሰ ነበር፡፡ ..አይ... እየመከርኩ ነው..፡፡

Page 39: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

“ይሄ ትልቅ የታሪክ ስህተት ብቻ ሳይሆን አሳፋሪ ፖለቲካ በእዛች ሀገር እንዳለ ነው የምገነዘበው” ዳዊት ከበደ ፍትህ፡- በ1998 በሀዳር ጋዜጣ ምክንያት ታስረህ በይቅርታ ተፈተሀል፡፡ ሆኖም ብዙዎች ወደ ውጪ ሀገር ሲሰደዱ አንተ አውራምባ ታይምስን መስርተህ ስራ ጀምረሃል፡፡ ወደ ስራው ስትገባ ይሄ ይመጣል (ይቅርታዬ ሊነሳ ይችላል) ብለህ አላሰብክም ነበር? ዳዊት፡- በእርግጥ ከእስር ቤት እንደወጣን ትንሽ ተስፋ አስቆራጭ ነገር ነበር፡፡ ብዙዎቹ የሙያ ጓደኞቼ ..ከዚህ በኋላ ኢትዮጵያ ውስጥ መስራት አይሞከርም፤ መሰደድ ነው ያለብን.. ብለው ሲሰደዱ በተወሰነ መልኩ ከውሳኔያቸው ጋር ብስማማም በወቅቱ የእኔ አቋም የነበረው ምንም ይሁን ምን ያለውን ነገር ተቋቁሜ እቀጥላለሁ የሚል ነበር፡፡ እንዲህ ያልኩበት ምክንያት ተስፋ ስለነበረኝ ነው፡፡ እናም በዛ መሰረት ነው አውራምባን የመሰረትኩት፡፡ ከሱ በኋላም በቻልነው አቅም አውራምባን አንባቢያን ዘንድ ለማድረስ ጥረናል፡፡ ፍትህ፡- እኔ እስከማውቀው ድረስ አውራምባን ከመሰረትክ ጀምሮ ከተለያዩ ጫናዎች በተጨማሪም የተከሰስክበት ሁኔታም ነበር፡፡ ያንን ሁሉ አልፈህ አለም አቀፍ ተሸላሚ ሆነሃል፡፡ ታዲያ አሁን ለመሰደድ ያበቃህ ምክንያት ከበፊቱ የከፋ ሆኖ ነው? ዳዊት፡- አዎ.. እንደምታውቀው የተመስገን ደሳለኝን ያህል 35 ክስ ባይኖብኝም እኔም ላይ እስከ ስድስት የሚደርሱ ክሶች ነበሩብኝ፡፡ ሆኖም ቀደም ብዬ ይሄ ሊኖር እንደሚችል አውቄ ስለነበረ ወደ ስራው የገባሁት ብዙ አላስደነገጠኝም ነበር፡፡ ነገር ግን አሁን የመጣው ፍፁም የተለየ ነው፡፡ አንተም እንደምታውቀው አንድ ፅሁፍ በፃፍኩ ቁጥር ከኤርትራ መንግስት እና ከሽብርተኝነት ጋር በሚመስላቸው መንገድ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ እና በዛሚ ሬዲዮ ጣቢያ ላይ ለማገናኘት ሲሞክሩ ነበር፡፡ እንዲሁም ይቅርታውን ሊያስነሳ የሚችል ነገር እየሰራሁ እንደሆነ እየቀሰቀሱ ነበር፡፡ ይሄ ሁኔታም ወደ ስጋት ይከትሃል፡፡

ሆኖም ከሀገሬ እንድወጣ ያደረገኝ ይቅርታውን አንስተው እና ሌላም ነገር አምጥተው እድሜ ልክ የሚያሳስር እንቅስቃሴ ማድረግ መጀመራቸውን በተጨባጭ መረጃ ስለአገኘሁ ነው፡፡ እናም ሳስበው ብታሰርም ጋዜጣው ይቆማል፡፡ ብሰደድም ያው ጋዜጣው ይቆማል፡፡ ሁለቱም አደጋዎች ለጋዜጣው የሚጠቅሙ አይደሉም፡፡ ስለዚህ ዝም ብሎ እስር ቤት ገብቶ ከመጐዳቱ በቀር የሚያመጣው ለውጥ የለም በሚል ነው መሰደዱን የመረጥኩት፡፡

ፍትህ፡- አንተ ከተሰደድክ በኋላም ሆነ በፊት በተለይ ከመንግስት በኩል የሚቀርብብህ ስሞታ አለ፡፡ ከአውራምባ ታይምስ ጀርባ ሌሎች በውጭ ሀገር የሚገኙ ተቃዋሚዎች አሉ የሚል፡፡ ዛሬ ራሱ (ቃለ መጠይቁ የተደረገው እሮብ ህዳር 20 ነው) የወጣው አዲስ ዘመን ጋዜጣ አንተ ፎቶህን እና ስምህን እንደ አከራየህና ፅሁፎቹን የሚፅፉት ግን ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ሰዎች እንደሆኑ ይገልጻል፡፡ በዚህ ላይ ምን ትላለህ? ዳዊት ከበደ፡- ምንም ልልክ አልችልም፡፡ ምክንያቱም ይሄ አይነቱ ስራ ከዚህ በፊት አቶ አማረ አረጋይ እንዳለው ..ዘማዊ ጆርናሊዝም.. ነው፡፡ ለዚህ ቃል ግን የፍትህ አንባቢዎችን ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡

እንግዲህ እኔ ለማን እንደማከራየው አላውቅም፡፡ እነሱ ግን በማከራየት ስለሚያምኑ ነው፡፡ ሆኖም ሞራል በሌላቸው ሰዎች የሚመራ ጋዜጣ ከዚህ በላይም ቢፅፍ አይገርመኝም፡፡ አሁን እንደፈለጉ ይፃፉ ሜዳው የእነሱ ነው፡፡ አሁን ያለው አንድ ፍትህ ጋዜጣ ነው፡፡ እሱም መቀጠል እስከሚችል ድረስ ማለቴ ነው፡፡ ከዛ ውጭ ግን ያሉት በሙሉ እነሱ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ አስር በማይሞሉ ሰዎች መልካም ፍቃድ ብቻ የሚኖርበት ሀገር በመሆኗ ነው፡፡

ሌላው ጉዳይ እነሱ የራሴ የሚሉት ምንም ነገር የላቸውም፡፡ ሌላው ቀርቶ ይሄንን አባባል ራሱ ከፍትህ ጋዜጣ የኮረጁት ነው፡፡ ፍትህ ጋዜጣ ከዚህ በፊት ኢትዮ ቻናል ጋዜጣን ..የራሳቸው የላቸውም ስማቸውን አከራይተውት ነው፤ ጋዜጣ የሚያሳትሙት፡፡ መንግስትም ቢሆን አቋም የሌላቸውን ሰዎች እየፈለገ እንዲህ ማደረጉ ጎጂ ነው.. ተብሎ ተፅፎ ያነበቡትን ነው አሁን መልሰው ለእኛ የሰጡን፡፡

የሆነ ሆኖ አንባቢ ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ እያንዳዳችን የምንፅፈው ይታወቃል፡፡ ብናከራየውም ደግሞ ደግ አደረግን.. የራሴ ጋዜጣ ነው፡፡ ከአመንኩበት በአከራየውም የራሴ ስልሆነ መብቴ ነው፡፡ እንደነሱ ዜጎች በሚከፍሉት ግብር የተቋቋመ ጋዜጣ አይደለም፡፡ በዜጎች ገንዘብ የተቋቋመ ጋዜጣ እንኳ በጣም ቆሻሻ ለሆነ ፖለቲካ እራሱን አከራይቶአል፡፡

ፍትህ፡- አዲስ ዘመን ከተነሳ አይቀር ስሜን አጠፋኝ ብለህ ክስ መስርተህ መፍትሄም እንዳላገኘ አስታውሳለሁ... ዳዊት፡- ልክ ነው፡፡ በነገራችን ላይ እኛ ፍርድ ቤት ድረስ የሄድነው በሀገራችን ለመስራት ካለን ጉጉት የተነሳ ነው፡፡ ሆኖም መጀመሪያ አካባቢ እኛ እና አዲስ ነገር ላይ ሲፅፉብን፤ እኛ ጉዳዩን በትዕግስት ነበር የያዝነው፡፡ አዲስ ነገሮች አዝማሚያው ገብቶአቸው ከሀገር ሲወጡ እኛ ግዴለም እስቲ ነገሮችን ኮምፕሮማይዝ አድርገን እንቀጥል ወደሚል አቅጣጫ ነበር የሄድነው፡፡ ለዚህም ነው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት የወሰድነው፡፡በፍርድ ቤትም ምንም መፍትሄ አለማግኘታችን እና እነሱም ከቀን ወደ ቀን ውንጀላቸውን እያበረቱ መሄዳቸው ሁኔታዎችን ወደ መጥፎ ደረጃ እያደረሰቸው ሄደ፡፡ ከዚህ በኋላ የትም ልትሄድ አትችልም፡፡ እናም ውንጀላውን ወደ ተግባር ሊለወጡ ሲንቀሳቀሱ ትቼላቸው ወጣሁ፡፡ ፍትህ፡- በእርግጥ መንግስት ለመሰደድህ አንተ ..ይቅርታዬ ሊነሳ ነው.. ያለከውን ምክንያት አልተቀበለውም፡፡ እንዲያውም ጋዜጣው እየከሰረ ስለሄደ ነው ዘግቶ የተሰደደው ብሎአል፡፡ ትቀበለዋለህ? ዳዊት፡- እኔ እንግዲህ ስለዚህ ጉዳይ ምንም ልልህ አልችልም፡፡ አንተ ራስህ የምታውቀው ነው፡፡ በተጨማሪም አንተ ሀገር ቤት ነው ያለከው፡፡ እናም አውራምባ ታይምስ በሳምንት ምን ያህል ኮፒ እንደሚታተም አጣርተ እውነቱን ልታወጣው ትችላለህ፡፡

Page 40: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ሆኖም እዚህ ጋር አንድ ነገር ልንገርህ፡፡ ኢህአዴግ 20 ዓመት ሙሉ የፕሮፓጋንዳ ስልቱን የሚቀየር አይደለም፡፡ በ1980ዎቹ አጋማሽ ለኦነግ የተጠቀመበትን ፊልም፤ ዛሬ አርቲስት ደበበ እሸቱ ላይ ሲጠቀመው ታያለህ፡፡ አሁን አውራምባ ላይ የተጠቀመውን (ከስሮ ነው የሚለውን ማለቱ ነው) የማስተባበያ ዘዴ አዲስ ነገር ጋዜጣም ሲዘጋ ተጠቅሞበታለ፡፡ ነገም ፍትህ ጋዜጣ ላይ አንድ ነገር ሲያደርሱ፤ ዘዴውን ሲጠቀሙበት ታያለህ፡፡ ምን አለ ብለኝ፡፡ ይሄ በጣም ያሳዝናል፡፡

አንዳንዴ ውሸት እኮ የራሱ የሆነ ዝግጅት ያስፈልገዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች ለማዋሸት እንኳ ምንም ዝግጅት ሲያደርጉ አታይም፡፡ የትኛው ያስገምተናል፤ የትኛው አያስገምተንም ሳይሉ የሚዋሹ ናቸው፡፡ እናም እኔ ይሄ ምንም አይመስለኝም፡፡ እንደቁም ነገርም አልቆጥረውም፡፡ የሆነ ሆኖ እነዚህ ሰዎች ሃያ አመት ሙሉ ሲዋሹ የነበሩ ናቸው፡፡ እናም እነሱ የሚሉትን የኢትዮጵያ ህዝብ አምኖ ይቀበላል ማለት ስህተት ነው፡፡

ፍትህ፡- ሁለት ጋዜጦች ነበሩክ ሁለቱም ተዘግተዋል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ የሲፒጄ ተሸላሚ ነህ፡፡ ከዚሀ አነፃር በአሁኑ ወቅት ያለውን የኢትዮጵያ ሚዲያን እንዴት ትገልፀዋለህ? ዳዊት፡- እኔ እስከማውቀው ድረስ ሚዲያው መስቀለኛ መንገድ ላይ ነው፤ በሀገሪቱ ያለው አንድ ጋዜጣ ብቻ ነው፡፡ እናም አንድ ሀገር ያውም የ3ሺ ዓመት ታሪክ ያላት ሀገር አንድ ጋዜጣ ብቻ ይዛ ወዴት ልትራመድ እንደምትችል ወደፊት የምናየው ነው የሚሆነው፡፡ ሆኖም ይሄ ትልቅ የታሪክ ስህተት ብቻ ሳይሆን አሳፋሪ ፖለቲካ በእዛች ሀገር እንዳለ ነው የምገነዘበው፡፡

ፍትህ፡- ዳዊት ከሀገር ስትወጣ ከሌሎች የአውራምባ ባልደረቦች ጋር አለመወያየትህን ተከትሎ፤ ትክክል አይደለህም የሚሉ አሉ፡፡ እንደገና ደግሞ ለመወያያ ጊዜ ስላልነበረው ነው የሚሉም አሉ፡፡ አንተ የትኛው ነው ትክክል ትላለህ? ዳዊት ፡- ከእነሱ ጋር ለመወያየት ምንም ጊዜ አልነበረኝም፡፡ ሀሙስ ወደ ማታ ነው ይሄንን ነገር የሰማሁት፡፡ በማግስቱ ደግሞ አርብ ነው፡፡ የግድ የተጀመረ ጋዜጣ መሰራት ነበረበት፡፡ ስለዚህ አርብ ለመወያየት አመቺ አልነበረም፡፡ ይሄ ሁኔታ አስገድዶኝ ነው ላንወያይ የቻልነው፡፡ ፍትህ፡- ከዚህ በኋላ ዳዊት ከበደ በአሜሪካን ሀገር የሚኖረው እጣ ፈንታ ምንድን ነው? በሚዲያ ስራ ላይ ልትሰማራ ትችላለህ? በአጠቃላይ ቀጣዩ እቅድህ ምንድን ነው? ዳዊት ፡- የመጀመሪያው እቅዴ ትምህርቴን መቀጠል ነው፡፡ ሁለተኛው እቅዴ ደግሞ በሰሜን አሜሪካ ሶስት ትልልቅ ከተሞች ማለትም በዋሽንግተን፣ በአትላንታ እና በሲያትል አውራምባ ታይምስ እንዲቀጥል አደርጋለሁ፡፡

ከዚህ በፊት ሀገር ቤት ታትሞ ነበር ወደ እዚህ የሚመጣው፡፡ አሁን ደግሞ እዚህ ታትሞ ወደ ሀገር ቤት ይሄዳል፡፡ እናም እዚህ ካሉት ጋዜጠኞችም ጋር ሆነ ከሀገር ቤት ባልደረቦቼ ጋር ተባብሬ አውራምባን ማስቀጠል ነው እቅዴ፡፡

ፍትህ፡- ይሄ እቅድ ከመቼ ጀምሮ ነው ተግባራዊ የሚሆነው? ዳዊት፡- በአጭር ጊዜ ውስጥ ተግባራዊ ይሆናል፡፡ አሁን ጥናቱን ጀምረናል፡፡ እናም ጋዜጣው መታተም ሲጀምር በምናስነግረው ማስታወቂያ በኩል ኢሜል አድራሻቸውን ለሚልኩልን የሀገር ቤት አንባቢዎች በሙሉ በነፃ እንልክላቸዋለን ማለት ነው፡፡ ፍትህ፡- እሺ ሁለት የመጨረሻ ጥያቄ ደርቤ ላቅርብልህ፡፡ የመጀመሪያው ከሀገር በመሰደድ ምን አይነት ስሜት አደረብህ? ሁለተኛው አራት አመት ከአውራምባ ታይምስ ጋር ለቆዩ አንባቢዎች የምትለው ነገር አለ? ዳዊት፡- እንግዲህ ማንም ሰው የሚያውቀው ነው፡፡ ስደት ማለት በጣም መራር ነገር ነው፡፡ ህይወትን ከዜሮ ነው የምትጀምረው፡፡ በሀገር ቤት ከባልደረቦቼ ጋር ሆኜ የእግዚአብሔር ፍቃድ ተጨምሮበት አውራምባ ጥሩ ደረጃ ደርሳ ነበር፡፡ ከ17 ያላነሱ ሰራተኞች ነበሩባት፡፡ እንግዲህ እነዚህን ሁሉ ሰራተኞች ትቼ ነው ወደ ውጭ እንድወጣ የተገደድኩት፡፡ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረስኩት በጣም አስገዳጅ ነገር ስልገጠመኝ ነው፡፡ እናም እስከዛሬ ከአውራምባ ጋር አብረው ለዘለቁ አንባቢዎች አንድ ቀን በሙያዬ ዳግም እንደማገለግላቸው ያለኝን ተስፋ እገልፃለሁ፡፡ ደግሞም እርግጠኛ ነኝ ያ ቀን እንደሚመጣና እሩቅ እንደማይሆን፡፡ ፍትህ፡- እሺ ጋዜጠኛ ዳዊት ከበደ ከአሜሪካ በስልክ ለሰጠኸን ቃለ መጠይቅ በፍትህ አንባቢ ስም አመሰግናለሁ፡፡ ዳዊት፡- እኔም በጣም አመሰግናለሁ፡፡

Page 41: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

መለስ እና ስድቦቻቸው ተመስገን ደሳለኝ ክፍል ሶስት

የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ..ስድቦች..ን ከፖለቲካዊ አንድምታ አኳያ ማየት ከጀመርን እነሆ ሶስተኛው ሳምንት ላይ

ደርሰናል፡፡ በሁለት ክፍሎች ላቀረብኩት ፅሁፎች በዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ የህይወት ታሪክ ዙሪያ የተፃፈውን ..የነጋሶ መንገድ.. መጽሐፍ እንደ መግቢያ መጠቀሜ ይታወሳል፡፡ ለዛሬው ጹህፌ ደግሞ መግቢያ ይሆነኝ ዘንድ የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ አባት አቦይ ዜናዊ አስረስ ከ..ኢንፎቴይመንት.. መጽሔት ጋር በ1996ዓ.ም ህዳር ወር ላይ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ላይ አቶመለስ ክፉ ቃል ወጥቶአቸው እንደማያውቅ በተናገሩት ብንጀምር መልካም ነው፡-

“በእኔ በኩል መለስ አርሞ የሚናገርና የሚያደርግ ሰው ነው ባይነኝ፡፡ ሌሎች በዚህ ላይሰማሙ ይችላሉ? በእኔ በኩል ግን ከመለስ አፍ ግፍ ወጥቷል አልልም፡፡ ለዚህም እኮ ነው ትምክህተኛ አይደለም የምለው፡፡ መለስ የሚናገረው በህግ እንጂ በትምክህት አይደለም፡፡”

ይሄ አቦይ ዜናዊ ስለልጃቸው መለስ ዜናዊ ባህሪ ከተናገሩት የተቆነጠረ ነው፡፡ የሆነ ሆኖ አቦይ ዜናዊ ..መለስ አርሞ የሚናገር... መለስ የሚናገረው በህግ እንጂ በትምክህት አይደለም.. የአሏት ነገር

የአባትነት ወግ ስለሆነች እንለፋት፡፡ምክንያቱም የትኛውም አባት ስለልጁ ከዚህ ያነሰ ሊል አይችልምና፡፡ ስለዚህ እሳቸው የአባትነታቸውን መስክረዋል፡፡ የእኔ ድርሻ ደግሞ ምስክርነት ሳየሆ ምልከታ ነው፡፡ የምልከታዬ መነሻ እና መድረሻም ፖለቲካ ነው፡፡ በእርግጥ አቦይ ዜናዊ እንዳሉት መለስ ከፖለቲካ ውጪ ሲናገሩ አርመው ሊናገሩ ይቻሉ ይሆናል፡፡ ቅርበቱ ስለሌለኝ መረጃው የለኝም፡፡ በፖለቲካ ጉዳይ ላይ ግን ..ማረም.. የሚለውን ቃል የሚያውቅ ..መዝገብ ቃላት.. እንደሌላቸው የአየነው ነገር ነው፡፡ አናም ስልጣናቸው ከእጃቸው እንዳይወጣ ከአደረጉባቸው ስልቶች አንዱ ..ፖለቲካዊ ስድቦቻቸው.. ነው፡፡

የሆነ ሆኖ እንቀጥል፤መለስ ለስልጣናቸው ስጋት አድርገው ከሚመለከቱት አንዱ ሚዲያ ነው፡፡ ሚዲያውን በጣም ይፈሩታል፡፡ ምን አልባትም በትጥቅ ትግሉ ዘመን ከነበረው አስፈሪ ዘመንም በላይ የሚፈሩት ይመስለኛል፡፡ በእርግጥ ፍራቻቸው ከሜዳ የመጣ አይደለም፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ሚዲያው በእጅጉ ወሳኝ የሆነበት አጋጣሚዎች ጥቂት አለመሆኑን ጠንቅቀው ስለሚያወቁ ነው፡፡ ለምሳሌ የአሁኑ ..ሽብርተኛ.. ኦነግ በሽግግር መንግስቱ ዘመን ከኢህአዴግ ጋር በጋራ ስልጣን ይዞ የነበረው ድርጅት ከሽግግር መንግስቱ ከወጣ በኋላ ከአገኛቸው ወታደራዊ ድሎች ይልቅ በሚዲያ የአገኘው ሽፋን ይበልጣል፡፡ እስከ 1997 ድረስ የኦነግ ደጋፊ የሆነ ጋዜጦች ነበሩ፡፡ እናም ጋዜጦቹ ስለኦነግ በሚዘግቡት ዘገባ ኦነግን ከባሌ ተራራ አውርደው እንጦጦ አድርሰውት ነበር፡፡ ነገር ግን ሚዲያዎቹ ድህረ ምርጫውን የተነሳውን ሁከት እንደምክንያት በመጠቀም እንዲዘጉ ከተደረገ በኋላ ኦነግም አብሮ የተዘጋ እስኪመስል ድረስ እንኳን ዳናው ድምፁም የለ፡፡ ይሄ የሚያሳየው የሚዲያውን ጉልበት ነው፡፡

ሌላ ልጨምር፡፡ በምርጫ 97 ወቅት ከቅንጅት ተጽዕኖ ይልቅ የነፃው ሚዲያ ተፅዕኖ የበለጠ እንደነበረ ይታወሳል፡፡ ቅንጅት ከአገኘው አቅም አብላጫው በሚዲያው አስተዋጽኦ የተገኘ ነው፡፡ እንደምናስታውሰው ደግሞ በምርጫው የመለስ ስልጣን ወድቆ ያልተሰበረ እንቁላልን ያህል ነበረ የአጋጠመው አደጋ፡፡ መለስም ጊዜ ወስደው ሲያስቡበት ቆይተው የቅንጅቱ ሰዎችን ማሰር ብቻውን ፤ እስረኛ የሞላባትን እስር ቤት በሩን ዘግቶ መስኮቱን ያለመዝጋት ያህል ሆኖ ተሰማቸው፡፡ እናም የነፃው ፕሬስ አባላትን በሙሉ አፍሰው አሰሯቸው፡፡ ከእስሩ በፊት ግን ሚዲያው ላይ የማንቋሸሽ ዘመቻ መክፈት የግድ ነውና ዘመቱበት፡፡በስድብ፡፡መለስ ተሳደቡ፡፡ የፖለቲካ ስድብ፡፡ “Ghetto and Gutter press” (ምናምንቴ እና የዘቀጠ ፕሬስ) ሲሉ፡፡ ምናምቴም ሆነ የዘቀጠ ስድብ ነው፡፡ የኢህአዴግ ጀማም ተቀባበለው፤ ስድቡን፡፡ እዚህ ሀገር ያሉ ነፃ ጋዜጦች በሙሉ የዘቀጡ ናቸው፡፡ ምናምንቴ ናቸው... መለስ እንዲህ እንዲህ እያሉ በሚዲያው ላይ በከፈቱት ጦርነት ከደጋፊዎቻቸው በተጨማሪም ከተቃውሞም ሆነ ከድጋፉ ገለልተኛ የሆኑ ሰዎችን በመጠኑም ቢሆን ለማሳመን ረድቶአቸዋል፡፡ ፕሬሱ ምናምንቴ እና የዘቀጠ እንደሆነ፡፡ ከዚህ በኋላ ያን ምናምንቴ አፍሶ ማሰር ከባድ አልነበረምና አፍሰው አሰሩት፡፡ ...ከአረብ ሀገራት አብዮት በኋላ በተለያዩ ሀገራት ያሉ አምባገነን ገዥዎች እንቅልፍ አጥተዋል፡፡ ከእነዚህ ተኝተው ከሚያድሩ ገዥዎች ደግሞ አንዱ መለስ ዜናዊ ናቸው፡፡ ህዝባዊ ቁጣ ይነሳ ይሆን? በሚል ማለቴ ነው፡፡ በእርግጥ በኢትዮጵያ ካለው ነባራዊ ሁኔታ አንፃር መለስ መስጋታቸው ተገቢ ይመስለኛል፡፡ የኑሮ ውድነት፣ የዋጋ ግሽበት፣ ስራ አጥነት፣ የግብር መብዛት፣ የሊዝ አዋጅ፣ የፀረ-ሽብርተኛ ህጉ... የመሳሰሉት ተደማምረው ምን ሊፈጥሩ እንደሚችሉ መገመቱ አይከብድም፡፡ እንደ መለስ ያለ በብዙ አደጋ ውስጥ ያለፈ መሪ ደግሞ ህዝባዊ ቁጣው ካልተጠበቀ ቦታ ሊፈነዳ እንደሚችል ያውቃል፡፡ መፈንዳት ብቻ ደግሞ ሳይሆን አንዴ ህዝብ ..ሆ.. ካለ ወንበራቸው ላይ እንደ ዘንዶ መጠምጠሙ አይቀሬ መሆኑንም ያውቃሉ፡፡

ይሄ ሊሆን የሚችለው ደግሞ የአረብ ሀገራት የተሳካ ተሞክሮን እግር በእግር እየተከታተሉ እና ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ጋር እያነፃፀሩ የሚያቀርቡ ሚዲያዎች የሙያ ግዴታቸውን ሲወጡ እንደሆነ ወለል ብሎ ታይቶአቸዋል፡፡ እናም ጥቂት ተሰሚነት ያላቸውን ሚዲያዎች በአይነ ቁራኛ ከመከታተልም አልፈው ጫና ያሳድሩባቸው ጀመር፡፡ ጥቂት ጋዜጠኞችንም አሰሩ፡፡ ከዚህ በኋላም ለቀጣዩ እርምጃ ይረዳ ዘንድ መለስ እራሳቸው በፓርላማው ቀርበው በነፃው ፕሬስ ውስጥ ያሉትን ጋዜጠኞች ..ጋጠ-ወጥ.. ሲሉ ሰደቧቸው፡፡ የፖለቲካ ስድብ፡፡

ከዛስ ምን ተከተለ? ያው እንደተለመደው ደጋፊዎቻቸው ነፃ ፕሬሱን ..ጋጠ-ወጥ.. እያሉ እንዲቀባበሉት አደረጉ፡፡ ከዚህ በኋላ ደግሞ የአውራምባ ታይምስ ጋዜጣ ይዘጋ እና ባለቤቱ ይሰደድ ዘንድ የማይታይ እጃቸውን ዘረጉ፡፡ ተሳካላቸውም፡፡

ሁኔታውም በአንድ ወቅት የሪፖርተር ጋዜጣ ባለቤት አማረ አረጋዊ ፒተር ጊል በተባለ ፈረንሳዊ በተፃፈው Famine and foreginers’ Ethiopia since live aid መፀሀፍ ላይ እንዲሂ ሲል የተናገረው ሆነ፡- ..በመጀመሪያ የነበረንን የፕሬስ ነፃነት ከምዕራባዊያኑ ጋር አወዳድረን ነበር፡፡ ቀጥሎም ከገና እና ከደቡብ አፍሪካ ጋር ለማሰተያየት ሞክርናል፡፡ይህንንም ታግስን ነበር፡፡አሁን ያለን የፕሬስ ነፃነት ግን ከሱማሊያ ጋር የሚነፃፀር ነው፡፡..ጋዜጣ ከሚኖረኝ ግሮሰሪ መክፈት ይሻለኝ ነበር፡፡.. ይቀጥላል

Page 42: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

ጊዜ ለኩሉ

“ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከወንድ ጋር ቢተኛ ሁለቱ ፀያፍ ነገር አድርገዋል፤ ፈጽመው ይገደሉ”

ኦሪት ዘሌዋውያን ም.20 ቁ.13 ..ሁለቱም መላእክት በመሸ ጊዜ ወደ ሰዶም ገቡ፤ ሎጥም በሰዶም በር ተቀምጦ ነበር፡፡ ሎጥም ባያቸው ጊዜ ሊቀበላቸው

ተነሳ፤ ፊቱንም ደፍቶ ወደ ምድር ሰገደ፤ አላቸውም፡- ጌቶቼ ሆይ ወደ ባሪያችሁ ቤት አቅኑ ከዚያም እደሩ፤ እግራችሁንም ታጠቡ፤ ነገ ማልዳችሁም ትሄዳላችሁ፡፡ እነርሱም፡- በአደባባዩ እናድራለን እንጂ አይሆንም አሉት፡፡ እጅግም ዘበዘባቸው፤ ወደ እርሱም አቀኑ ወደ ቤቱም ገቡ፤ ማዕድ አቀረበላቸው፤ ቂጣንም ጋገረ እነርሱም በሉ፡፡ ገናም ሳይተኙ የዚያች ከተማ የሰዶም ሰዎች ከብላቴናው ጀምሮ እስከ ሽማግሌው ድረስ በየስፍራው ያለው ህዝብ ሁሉ ቤቱን ከበቡት ሎጥንም ጠርተው እንዲህ አሉት፡- በዚህ ሌሊት ወደ ቤትህ የገቡትን ሰዎች ወዴት ናቸው? እናውቃቸው ዘንድ ወደ እኛ አውጣቸው፡፡ ሎጥም ወደ እነርሱ ወደ ደጅ ወጣ፤ መዝጊያውንም በኋላው ዘጋው፤ እንዲህም አለ፡- ወንድሞቼ ሆይ ይህን ክፉ ነገር አታድርጉ፤ እነሆ ወንድን ያላወቁ ሁለት ሴቶች ልጆች አሉኝ፤ እነርሱን ላውጣላችሁ፤ እንደወደዳችሁም አድርጓቸው፤በእነዚህ ሰዎች ብቻ ምንም አታድርጉ፤ እነርሱ በጣራዬ ጥላ ስር ገብተዋልና፡፡ እነርሱም፡- ወዲያ ሂድ አሉት፡፡ ደግሞም እንዲህ አሉ፡- ይህ ሰው በእንግድነት ለመኖር መጣ፤ ፍርዱንም ይፈርድ ዘንድ ይፈልጋል፤ በአንተ ከእነርሱ ይልቅ ክፉ እናደርግብሃለን ሎጥንም እጅግ ተጋፉት፤ የደጁንም መዝጊያ ለመስበር ቀረቡ፡፡ ሁለቱም ሰዎች እጃቸውን ዘርግተው ሎጥን ወደ እነርሱ ዘንድ ወደ ቤት አገቡት፤ መዝጊያውንም ዘጉት፡፡ በቤቱ ደጃፍ የነበሩትንም ሰዎች ከታናሻቸው ጀምሮ እስከ ታላቃቸው ድረስ አሳወሩአቸው፤ደጃፉንም ለማግኘት ሲፈልጉ ደከሙ.. (ኦሪት ዘፍጥረት ም.19 ቁ.1-11)

ሰሞኑን አዲስ አበባን የሚያንቀጠቅጥ ፤ ሰዶምና ገሙራ የጠፋበት አይነት ወሬ እየሰማን ነው፡፡ ወሬውም ቅዳሜ ህዳር 23ቀን 2004ዓ.ም ከጠዋቱ 2፡30-11፡00 ሰዓት ድረስ፤ ከ25 አገሮች የተወጣጡ 200 ሰዎች ..ግብረ ሰዶማዊነት..ን እንደ መልካም ነገር የሚያወድስ ጉባኤ አዲስ አበባ በሚገኘው ጁፒተር ሆቴል ያደርጋሉ የሚል ነው፡፡ ይህንን ተከትሎ በርካታ ኢትዮጵያውያኖች በ..ፌስ ቡክ.. እና በመሳሰሉ ማህበራዊ ድረገፆች ተቃውሞአቸውን እየገለፁ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን፣ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት፣ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን እና የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተክርስቲያን መካነ ኢየሱስ መሪዎች ይህ የግብረሰዶሞች ስብሰባ በአዲስ አበባ እንዳይካሄድ የሚቃወም እና የሚያወግዝ ጋዜጣዊ መግለጫ ሊሰጡ ከተዘጋጁ እና ጋዜጠኞችም በቦታው ከደረሱ በኋላ በመንግስት ጣልቃ ገብነት ጋዜጣዊ መግለጫው እንዲቋረጥ መደረጉ ከተሰማ በኋላ ብዙዎችን አስቆጥቶአል፡፡

አዎን.. ኢትዮጵያ በእጅጉ ደሃ ነች ፡፡ በፖለቲካውም ቢሆን የምትወገዝ እና ትችት የሚቀርብባት ሀገር ነች፡፡ ይሄ ሁሉ ሆኖም ግን ህዝቦቿ የራሳቸው መገለጫ የሆኑ የሞራል እሴቶች ባለቤቶች ናቸው፡፡ ይሄ የተከበረ የሞራል ልዕልና ካደጉትም ሆነ ካላደጉት ሀገራት በይበልጥ የሚንፀባረቀው በኢትዮጵያ እና በኢትዮጵያውያን ብቻ ነው፡፡ አሁን መንግስት እየተከተለ ያለው አካሄድ ግን ይሄን ለዘመናት ተጠብቆ የቆየ ልማድ የሚጥስ ነው፡፡ ግብረ ሰዶማዊነት በኢትዮጵያ ይስፋፋ ዘንድ መንገድ በማመቻቸት፡፡

የሃይማኖት አባቶች የተቃውሞ መግለጫ ይቋረጥ ዘንድ ራሳቸው የጤና ጥበቃ ሚኒትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም በቦታው ተገኝተው ተፅዕኖ መፍጠራቸውም ምክንያታቸው ምንም ይሁን ምን ፍፁም ተቀባይነት የለውም፡፡ ዶ/ሩ ከሚያገለግሉት መንግስት በፊት የነበሩት መንግስታት የቱንም ያህል አምባገነን ቢሆኑም፣ የቱንም ያህል ለድህንነታችን ተጠያቂ ቢሆኑም ግብረ ሰዶም በሀገራችን እንዳይስፋፋ ግን ህግ ጭምር በማውጣት የቻሉትን ያህል አድርገዋል፡፡ ይሄ ፖለቲካ አይደለም፡፡ ይሄ የስልጣን ጥያቄ አይደለም፡፡ ይሄ የእኛነታችን መገለጫ የማንነታችን መታወቂያ ጉዳይ ነው፡፡

ከግብረ ሰዶሞቹ ስብሰባ አንድ ቀን በኋላ ከህዳር 24 ጀምሮ ለአምስት ቀን የሚደረገው የ..አይካሳ.. አለም አቀፍ ጉባኤን አስታኮ በኢትዮጵያ እንዲደረግ የተመረጠው ግብረሰዶማዊነትን የሚያበረታታው ውይይት የሉአላዊነታችን መደፈር ያህል ለእኛ ኢትዮጵያውያኖች ይቆረቁረናል፡፡ እናም መንግስት ዛሬ የሚደረገውን ይህንን ኢ-ሞራላዊ ከኢትዮጵያ ጨዋነት በእጀጉ የራቀ አጀንዳ የሚነሳበት ጉባኤ እንዳይደረግ መከላከል ምርጫው ሳይሆን ግዴታውም መሆኑን ማወቅ ይኖርበታል፡፡ ሌላው ቀርቶ በአይካሳ ጉባኤ ላይ ግብረሰዶማዊውያን አጀንዳ ይዘው የሚቀርቡበት ጉባኤ በአዲስ አበባ እንዲደረግ መፍቀዱ በእጅጉ ትውልድን የሚጎዳ ነው፡፡ ከቀን ወደ ቀን መከራዋ እየበዛ ለሄደው ሀገራችንም ከድጡ ወደ ማጡ ነው የሚሆነው፡፡

..ሁለቱም ሰዎች ሎጥን አሉት፡- ከዚህ ሌላ ማን አለህ? አማችም ቢሆን ወንድ ልጅም ቢሆን ወይም ሴት ልጅ ብትሆን በከተማይቱ ያለህን ሁሉ ከዚህ ስፍራ አስወጣቸው፤ እኛ ይህን ስፍራ እናጠፋለን፤ ጩኸታቸው በእግዚአብሔር ፊት ትልቅ ሆኖአልና፤ እናጠፋውም ዘንድ እግዚአብሔር ሰድዶናል፡፡ ሎጥም ወጣ፤ ልጆቹን ለሚያገቡት፣ ለአማቶችም ነገራቸው፤ አላቸውም፡- ተነሱ፤ ከዚህ ስፍራ ውጡ፤ እግዚአብሔር ይችን ከተማ ያጠፋልና፡፡.. ኦሪት ዘፍጥረት ም.19 ቁ.12-14

ሁለቱ መላእክትም ሎጥን ከነቤተሰቡ እና ከእነአማቹ ከሰዶም ከተማ እንዲወጣ ካደረጉ በኋላ ዞዓር ወደ ተሰኘች ከተማ አደረሷቸው፡፡ እናም ወደ ኋላ ማንም ሰው እንዳይዞር ብለው ተናገሩ፡፡

..ሎጥ ወደ ዞዓር በገባ ጊዜ ፀሐይ በምድር ላይ ወጣች፡፡ እግዚአብሔርም በሰዶምና በገሞራ ላይ፤ ከእግዚአብሔር ዘንድ ከሰማይ እሳትና ዲኝ አዘነበ፤ እነዚያንም ከተሞች በዙሪያው የለውንም ሁሉ፤ በከተሞቹም የሚኖሩትን ሁሉ የምድርንም ቡቃያ ሁሉ ገለበጠ፡፡ የሎጥም ሚስት ወደ ኋላው ተመለከተች፤ የጨው ሐውልትም ሆነች፡፡ አብርሃምም በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ ወደ ነበረበት ስፍራ ለመሄድ ማልዶ ተነሳ፤ ወደ ሰዶምና ወደ ገሞራ በዚያች ሀገር ወዳለውም ምድር ሁሉ ተመለከተ፤ እነሆም የአገሪቱ ጢስ እንደ እቶን ጢስ ሲነሳ አየ፡፡ እግዚአብሔርም እነዚያን የአገር ከተሞች ባጠፉ ጊዜ አብርሃምን አሰበው፤ ሎጥ ተቀሞጦበት የነበረውንም ከተማ ባጠፉ ጊዜ ከዚያ ጥፋት መካከል ሎጥን አወጣው.. (ኦሪት ዘፍጥረት ም.19 ቁ.23-29)

እነሆ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ወንድ ለወንድ፣ ሴት ለሴት የሚደረግ ወሲባዊ ግንኙነት በዛች በእሳትና በዲኝ ዝናብ ነዳ በጠፋችው ከተማ ስም ..ግብረ ሰዶም.. (የሰዶማውያን ስራ) ተብሎ በእርኩሰት ይታያል፡፡ የአደጉ ሀገራት ይህንን በእግዚአብሔር ዘንድም ሆነ፤ በሰው ልጅ ክብር ዘንድ አፀያፊ የሆነውን ተግባር እንደ ህጋቸው ፍቃድ መስጠታቸው ይታወቃል፡፡ ኢትዮጵያ ግን ከዚህ በተቃራኒው የዚህ አይነት እርኩሰት የሚፈፅም ካለ ከ10-15 ዓመት የሚያስቀጣ ህግ እርቅቃ ..ግብሩ.. በህገወጥ መንገድ ካልሆነ በቀር በገሃድ

Page 43: 164

[Type the document title]

ቅዳሜ ህዳር 24 2004ዓ.ም ቁጥር 164

እንዳይፈፅም ስትከላከል ቆይታለች፡፡ ዛሬ ግን መንግስት ራሱ ግብረሰዶም ፈፅመው የሚገኙ ወንጀለኞችን የሚቀጣ ህግ ታቅፎና እየቀጣም እያለ እንዲህ አይነት ጉባኤ ከሀገሪቱ ህግ ጋር የሚፃረር መፍቀዱ በእጅጉ የሚያሳዝን ብቻ ሳይሆን ውሎ አድሮ ከፍተኛ መዘዝ ሊያመጣ የሚችል ነው፡፡

ይሄ ሀገር ኢትዮጵያ ነው፡፡ እኛም ኢትዮጵያውያኖች ነን፡፡ እናም ለዘመናት ከአባቶችን ሲወርድ ሲዋረድ ቆይቶ የጠበቅነውን ባህል ለማበላሸት የሚደረግ ማንኛውንም እንቅስቃሴ እስከመጨረሻው ድረስ እንታገለዋለን፡፡

ሆኖም ይሄ ጉባኤ አዲስ አበባ እንዲደረግ በመፈቀዱ የሚያስገርመው ሀገሪቷን የሚያስተዳድረው ገዢው ፓርቲ (ኢህአዴግ) ለ20 አመት ሲያቀነቅንለት የነበረው (“Group Right”) (የቡድን መብት) ዛሬ የት ሄዶ እንደሆ አለመታወቁ ነው፤ በግልፅ የቡድን መብትን የሚጥስ ጉባኤ እንዲካሄድ የፈቀደው?

እናም ይሄ ..የራስ ማድረግ፣ ማሳደግና ቀጣይነት.. በሚል መሪ ቃል በሀገራችን በጁፒተር ሆቴል ሊካሄድ የታሰበው የግብረሰዶማዊያን ጉባኤ ከብዙ የሀገሪቱ ሁኔታዎች ጋር የሚጣረስ ነው፡፡ ኢህአዴግ እከተለዋለሁ ከሚለው አብዮታዊ ዴሞክራሲ፣ ከሀገሪቱ የወንጀለኛ መቅጫ ህግ፣ ከባህል፣ ከእምነት፣ ከኢትዮጵያዊነት... ከመሳሰሉት ጋር የሚጋጭ ነው፡፡ እንዲህ አይነት ጉባኤንስ ፈቅዶ፤ ከዚህ በኋላ በግብረሰዶማዊ ተግባር ተሰማርተው የሚገኙ ዜጎችን እንዴት ተብሎ ነው በህግ የሚጠየቁት? ወይስ ህጉም ሊሻረ ነው?

ሙሴ ከእግዚአብሔር ከተቀበለው ትእዛዛት አንዱ እንዲህ ይላል ..ማናቸውም ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ፤ ከወንድ ጋር ቢተኛ ሁለቱ ፀያፍ ነገር አድርገዋል፤ ፈጽመው ይገደሉ፤ ደማቸው በላያቸው ነው.. (ኦሪት ዘሌዋውያን ም.20 ቁ.13)

ሀዋርያው ጳውሎስም ወደ ሮሜ ሰዎች በላከው መልእክቱ ..ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ሴቶቻቸውም ለባህሪያቸው የሚገባውን ሰራ፤ ለባህርያቸው በማይገባው ለወጡ፤ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባህሪያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው፤ እርስ በእርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፡፤ ወንዶችም በወንዶች ነውር አድርገው በስህተታቸው የሚገባውን ብድራት በራሳቸው ተቀበሉ.. (ሮሜ ም.1 ቁ.26-27) ሲል ስለ ግብረ ሰዶም ነውርነት ገልጿል፡፡

ራሱ ጳውሎስ ወደ ጤሞቴዎስ በላከው የመጀመሪያ መልእክቱ ህግ ሊተገበር እንደሚገባው ሲገልፅ ደግሞ እንዲህ ብሎአል ..ነገር ግን ሰው እንደሚገባ ቢሰራበት ህግ መልካም እንደሆነ እናውቃለን፤ ይኼውም ለበደለኞች ለማይታዘዙ፤ለዓመፀኞችና ለሀጢአ ተኞች፤ ቅድስና ለሌላቸውና እርኩሳን፤ አባትንና እናትን ለሚገድሉ ለነፍስ ገዳዮችና ለሴሰኞች፤ ከወንድ ጋርም ለሚተኙ..... (1ኛ ጤሞነዎስ ም.1 ቁ.8-11) እያለ ዘርዝሮ የህጉን አስፈላጊነት ገልጿል፡፡

እነሆም ግብረ ሰዶም ነውር እና ሀጢአት ከመሆኑም በላይ ሀገርንም ሊያጠፋ የሚችል ስለመሆኑ ከመፀሐፍ ቅዱስ አንፃር ይፃፍ ከተባለ እንኳንም የጋዜጣ አምድ ቀርቶ ብዙ ገፅ ያለው መጽሐፍም አይበቃውም፡፡

የሆነ ሆኖ እኛ ኢትዮጵያውያኖች እምነታችን የተለያየ ቢሆንም በእንዲህ አይነት ኢ-ስነምግባር እና ኢ-ሞራል ተግባር ላይ ተመሳሳይ አቋም አለን፡፡ ትውልድ ይቀጠል ዘንድ ይሄ የግብረሰዶም ጉባኤ እዛው የተጀመረበት ሀገር እንጂ በኢትዮጵያ እንዳይካሄድ አጥብቀን እንጠይቃለን፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ለሁላችንም ልቦና ሰጥቶን ከዚህ ጥፋት እና እርኩሰት ተግባር ይመልሰን፡፡ አሜን ይመልሰን፡፡