ossa-bcc kit final

102
የባህሪ ለውጥ መግባቢያ ኪት አዘጋጅ፡ ውብሸት ታደለ (ዴር ኮንሰልታንት) መስከረም 2002 ዓ.ም

Upload: tagewub4

Post on 08-Apr-2015

532 views

Category:

Documents


0 download

TRANSCRIPT

Page 1: Ossa-bcc Kit Final

የባህሪ ለውጥ መግባቢያ ኪት

አዘጋጅ፡

ውብሸት ታደለ (ዴር ኮንሰልታንት)

መስከረም 2002 ዓ.ም

Page 2: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

2

መቅድም

ይህ ኪት በኤች አይ ቪ ዙሪያ መሰረታዊ መረጃዎች

የተካተቱበት የመረጃ መድብል ሲሆን በህፃናት ላይ በሚደርስ

መገለልና መድልኦ ዙሪያ እንዲያተኩር ተደርጎ የተዘጋጀ

ነው።

ኪቱ በኤድስ መከላከያና ማህበራዊ አገልግሎት ድርጅት

(OSSA) እና የዴንማርክ ህፃናት አድን ድርጅት (Save the

Children-Denmark) ትብብር የተዘጋጀ ነው።

ኪቱ የተዘጋጀውና የተቀናበረው በዴር የማህበራዊና ስነ-

ልቦናዊ ጉዳዮች አማካሪ ድርጅት (DARE Consultant)

ነው።

በመጨረሻም ለዚህ ኪት ዝግጅት መሳካት የበኩላቸውን

ላደረጉ ሁሉ ምስጋና ይድረስ!

Page 3: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

3

ማውጫ

መግቢያ ----------------------- 5

የኤች አይ ቪ ምንነት ------------- 7

ኤች አይ ቪን መከላከል ------------------ 13

ህይወትና ባህርይ ------------------- 17

ኤች አይ ቪና የወሲብ ባህርይ ------------------ 19

የኤች አይ ቪ መተላለፊያ መንገዶች ----------- 24

ኤች አይ ቪ የማይተላለፍባቸው መንገዶች -----32

ኤች አይ ቪ እና ማህበራዊ ችግሮች -------- 36

ኤች አይ ቪ፣ስርዓተ-ፆታና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች- 39

አደገኛ ዕፆች፣ አልኮልና ኤች አይ ቪ ------ 53

Page 4: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

4

የበጎ ፈቃድ የስነ-ምክር አገልግሎትና ኤች አይ ቪ - 60

የስሜት ልዕልና/ማዕምር -------------- 71

ስለ ሌሎች ማሰብ (Empathy) -----------------72

መገለልና መድልኦ ----------------79

የመገለልና መድልኦ ዓይነቶች ------ 81

መገለል፣ መድልኦ እና ህፃናት ------- 88

የመገለልና መድልኦ ውጤቶች ----- 95

Page 5: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

5

መግቢያ

ይህ ኪት በኤች አይ ቪ/ኤድስ ዙሪያ መሰረታዊ

የሚባሉ መረጃዎችንና የባህርይ ለውጥ ለማምጣት

የሚያግዙ አቅጣጫዎችን አካቶ የያዘ ሁለ-አቀፍ

የመረጃ መድብል (Information Education &

communication /Behavioral Change Communication Kit)

ነው።

ኪቱ ከኤች አይ ቪ ጋር በተያያዘ የሚከሰተውን

መገለልና መድልኦ አተኩሮ መረጃ የሚሰጥና

አስፈላጊው የባህርይ ለውጥ እንዲመጣ መከተል

ያለብንን አማራጭ መንገዶች የሚያመላክት ነው።

Page 6: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

6

በኪቱ ውስጥ የተካተቱትን መረጃዎች ለሌሎች

በማሰራጨትና እንዲያውቋቸው በማድረግ የመረጃ

ተደራሽነቱን ማስፋት ከሁላችንም የሚጠበቅ ተግባር

ነው።

በዚህ IEC/BCC ኪት ውስጥ የተካተቱትን ነጥቦች

ታሳቢ በማድረግ የተለያዩ መረጃዎችን መሰብሰብና

የዕውቀት አድማስን ማስፋት ያስፈልጋል።

መልካም ንባብ!

Page 7: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

7

የኤች አይ ቪ ምንነት

የአለም ጤና ድርጅት የኤድስ ፕሮግራም ዳይሬክተር

የነበሩት ጆናታን ማን ኤች አይ ቪ ሶስት የክስተት

ደረጃዎች እንዳሉት ያብራራሉ።

አንደኛ፤ የቫይረሱ የክስተት ደረጃ ወይም የኤች አይ

ቪ ክስተት ሲሆን ይህም የሰው ልጅን የበሽታ

መከላከያ አቅም የሚያዳክም Human Immune

Deficiency Virus የተባለ ሰውን ብቻ የሚያጠቃ

ቫይረስ በደም ውስጥ መከሰቱን የሚያመለክት ነው።

ኤች አይ ቪ በማንኛውም ዓይነት ሰው ውስጥ ሊከሰት

የሚችል እና ባህሪው ከሌሎች ተውሳኮችም ይሁን

ከቫይረሶች ይልቅ አስቸጋሪና ተለዋዋጭ ከመሆኑ

Page 8: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

8

የተነሳ በአስተማማኝ ሁኔታ ለማስወገድ የሚያስችል

መድሃኒት ያልተገኘለት ነው፡፡

አንድ ሰው በደሙ ውስጥ ኤች አይ ቪ ተገኘበት

ማለት በሽታን ለመከላከል የሚያስችለውን አቅም አጣ

ማለት አይደለም። ለበሽታ ወይም ህመም የሚጋለጠው

ወደ ቀጣዩ ደረጃ ሲሸጋገር ነው።

ቀጣዩና ሁለተኛው ደረጃ የኤድስ ደረጃ ነው። ኤድስ

ከእንግሊዝኛ የተወሰደ ምህፃረ ቃል ሲሆን

እንደሚከተለው ሊተነተን ይችላል፡

AIDS:

A=Acquired

I=Immune

D=Deficiency

S=Syndrome

Page 9: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

9

Acquired ማለት አብሮን ያልተፈጠረ ወይም ያልቆየና

ከሌሎች የመጣ ወይም የተላለፈ ማለት ነው።

Immune ማለት የሰውነታችን በሽታን የመከላከል

አቅም ወይም የበሽታ መከላከያ ማለት ነው።

Deficiency ማለት እጥረት ወይም መመናመን ማለት

ነው።

Syndrome ማለት የበሽታ ምልክቶች ጥርቅም ማለት

ነው።

ስለዚህም ኤድስ በኤች አይ ቪ ምክንያት የበሽታ

መከላከያ አቅማችን ሲመናመንና ሲዳከም የሚከሰት

የተለያዩ የበሽታ ምልክቶች ወይም የህመም ስሜቶች

ጥርቅም ነው።

Page 10: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

10

ምንም እንኳን በተለምዶ ኤች አይ ቪን ከኤድስ ጋር

አንድ እና ተመሳሳይ አድርጎ የማየት ሁኔታ ቢኖርም

ኤድስ ቫይረሱ በደም ውስጥ ከተከሰተ በኋላ ቆይቶ

የሚከሰትና በሽታን ወይም ጤናማ ሰው

የሚቋቋማቸውን ህመሞች ያለመቋቋም ችግር ነው።

ሶስተኛው የክስተት ደረጃ የኤች አይ ቪ ማህበራዊ

ውጤቱን የሚያሳይ ነው። ይህም ውጤት በዋናነት

ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ባለባቸውና በኤድስ

በተያዙት እንዲሁም በቤተሰቦቻቸው ላይ የሚደርስ

መገለልና መድልኦ ነው።

መገለልና መድልኦ ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ ሰዎችን

ዝቅ አድርጎ የማየትና በማህበራዊ ህይወት ውስጥ

ዝቅተኛ ተጠቃሚነትና ሚና እንዲኖራቸው የማድረግ

ሁኔታ ነው።

Page 11: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

11

ቀደም ብሎ በአዕምሮ በሽተኞች፣ በአካል ጉዳተኞች፣

ወዘተ. ላይ የሚከሰተው መገለልና መድልኦ ቅርጹን

ቀይሮና በተጽዕኖ ደረጃም አድጎ ከኤች አይ ቪ ጋር

በተያያዘ እየተከሰተ እንደሆነ ጥናቶች ያሳያሉ።

Page 12: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

12

መልመጃ 1

1. ኤች አይ ቪ ምንድነው?

2. ኤድስ ከኤች አይ ቪ የሚለየው በምንድነው?

3. ሶስቱ ዋና ዋና የኤች አይ ቪ የክስተት ደረጃዎች

ምንድን ናቸው?

4. ኤች አይ ቪን በተመለከተ የሚከሰት መገለልና

መድልኦ ምክንያቱ ምንድነው ትላላችሁ?

Page 13: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

13

ኤች አይ ቪን መከላከል

ኤች አይ ቪ/ኤድስ ክትባትም ሆነ መድሃኒት

የለውም፡፡ኤች አይ ቪ ኤድስ ካብዛኞቹ በቫይረስ

ምክንያት ከሚመጡ በሽታዎች የሚለየው ባህርይን

በማስተካከልና በብልህነት መከላከል የሚቻል

መሆኑ ነው፡፡

ኤች አይ ቪ ኤድስን ለመከላከል ዋናውና

መሰረታዊው መፍትሄ ከወሲብ ታቅቦ መቆየት

ነው፡፡ በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ ወሲብ

ሳይፈፅሙ በመቆየት ለማግባትና ትዳር

ለመመስረት በሚታስብብት ወቅት ተመርምሮ

ራስን ማወቅና ከትዳር አጋር ጋር ብቻ ወሲብ

መፈፀም ኤች አይ ቪን ለመከላከልም ሆነ

ለአጠቃላይ ጤናማ ህይወት መፍትሄ ነው፡፡

Page 14: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

14

ከፍቅረኛ ወይም ከትዳር ጓደኛ ጋር በመተማመን

መኖርና ከጓደኛ ውጭ ከማንም ጋር ወሲብ

አለመፈፀም ሁለተኛ አማራጭ ነው፡፡

ከላይ የተጠቀሱትን አማራጮች ማሟላትና

መጠቀም ካልቻልንና ወሲብ ለመፈፀም ከወሰንን

ኮንዶምን መቶ በመቶ መጠቀም አለብን፡፡ኮንዶምን

መቶ በመቶ መጠቀም ማለት በአጠቃቀሙ ላይ

ዝንፈት ሳያሳዩ በትክክልና በአስተማማኝ ሁኔታ

መጠቅም ማለት ነው፡፡

ለወንዶችም ሆነ ለሴቶችም የተዘጋጀ ኮንዶም ያለ

ሲሆን በተለይ የወንዶች ኮንዶም ሰፊ የስርጭትና

የአጠቃቀም መሰረት ያለው በመሆኑ በቀላሉ

መጠቀም ይገባቸዋል፡፡

Page 15: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

15

ኮንዶምን ደራርቦ ለመጠቀም መሞከር በሁለቱ

ኮንዶሞች መከላከል የመፋተግ ሂደትን

ስለሚፈጥርና ይህም በኮንዶሙ ደህንነት ላይ

የመላላጥና የመበጣጠስ ችግር ስላለው ኮንዶምን

ደራርቦ መጠቀም ፍፁም ተገቢ አይደለም፡፡

በኮንዶሙ ላይ ያለው ቅባት ፍትጊያን

በመካላከልና ቀላልና ለስላሳ ሂደትን በመፍጠር

ቫይረሱን ለመከላከል ስለሚያስችል ጠቃሚነቱን

መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

አንድን ኮንዶም ካንድ ጊዜ በላይ መጠቀም

አይገባም፡፡

Page 16: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

16

መልመጃ 2

1. ከወሲብ ታቅቦ መቆየት የመጀመሪያው

ተመራጭ የኤች አይ ቪ መከላከያ መንገድ ነው።

እውነት/ሃሰት

2. በአገራችን የሚሸጡ የኮንዶም ዓይነቶችን ዘርዘሩ፡

3. ስለኮንዶም ከጓደኞቻችሁ፤ከቤተሰባችሁ ወይም

ከሌላ ሰው ጋር ተወያይታችሁ ታውቃላችሁ?

4. ስለ ኮንዶም አጠቃቀም ታውቃላችሁ?

5. ስለ ኮንዶም መወያየት ምን ጥቅም አለው

ብላችሁ ታስባላችሁ?

Page 17: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

17

ህይወትና ባህርይ

የሰው ልጅ ህይወት በሁለት መሪዎች ይሽከረከራል።

አንደኛው ደመ-ነፍስ ሲሆን ይህ እንስሳትን

የሚመራቸው የተፈጥሮ የመቆየት (Survival)

ሚስጥር ሲሆን ሁለተኛው ለሰው ልጅ ብቻ የተሰጠው

የአዕምሮ መሪ ነው።

በሁለቱ መሪዎች የሚመራው ህይወታችን በስሜትና

በህሊና ጎዳናዎች ይሮጣል። የስሜትና የህሊና ጉዟችን

የተመጣጠነ ካልሆነ ህይወታችን ሀሴትና ደስታ

ይርቃታል።

ስሜት ጊዜያዊ ፈንጠዝያ ወዳለበት አቅጣጫ ሁሉ

ሲያቻኩለን በአዕምሯችን ካልታገዘ ነገን ለዛሬ

መስዋዕት የሚሰጥ ይሆናል። በተመሳሳይ መልኩ

Page 18: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

18

አዕምሮ ብቻውን የሚመራው ህይወት ከደስታ የራቀና

ዛሬን ለነገ መስዋዕት የሚያቀርብ ነው።

ነገንም ዛሬንም ያጤነና የተመጣጠነ የህይወት

አቅጣጫ ደስተኛና ጤናማ ህይወትን ይፈጥራል።

እያንዳንዱ የህይወታችን ክፍል በደስታና በኃሴት

የተሞላ እንዲሆን ስሜታችንና ህሊናችን ሊመጣጠኑ

ይገባል።

Page 19: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

19

ኤች አይ ቪ እና የወሲብ ባህርይ

ከኤች አይ ቪ መተላለፊያ መንገዶች መካከል ጥንቃቄ

የጎደለው የግብረ-ስጋ ግንኙነት ከ80 በመቶ በላይ

በመያዝ ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳል። ለዚህም

የወሲብ ደመ-ነፍስ ትልቅ ሚና ይጫወታል። የወሲብ

ደመ-ነፍስ በሰው ልጅ የደመ-ነፍስ የህይወት አቅጣጫ

ውስጥ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ጥናቶች ያሳያሉ።

በዚህ ዘመን በእጅጉ እየተስፋፉ የመጡት የፊልምና

የማስታወቂያ ስራዎች የወሲብ ይዘት ያዘሉ

መሆናቸው በወሲብ ባህርይ ላይ ተጽዕኖ ይፈጥራሉ።

በተለይም ወሲብን ብቻ አልመው የሚወጡት ልቅ

የወሲብ ፊልሞች (የፖርኖግራፊክ ፊልሞች) በወሲብ

ባህርይ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ያሳድራሉ።

Page 20: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

20

የወሲብ ባህርይ በአግባቡና በጥንቃቄ የሚመራ

ካልሆነና ከአዕምሮ ቁጥጥር ውጭ ከሆነ ለጤናማና

ደስተኛ ህይወት እንቅፋት ይሆናል።

ብዙ ሰዎች የወሲብ ስሜት ከአዕምሮ የራቀ ነው

ብለው ያምናሉ። ነገር ግን ወሲብ ምንም እንኳን

ከደመ-ነፍስ የሚመነጭ እንስሳዊ ወይም ተፈጥሯዊ

ሁኔታ ቢሆንም የሰው ልጅ የሚመራው በደመ-ነፍስና

በአዕምሮ ህብር በመሆኑ ምክንያት ወሲብም በአዕምሮ

ቁጥጥር ስር ያለና መነሻውም ከአዕምሯችን ነው።

ህፃናት ለወሲብ የሚነሳሱት በስነ-ህይወታዊ፣

ማህበራዊ፣ ስነ-ልቦናዊ፣ ወዘተ. ዕድገታቸው ለወሲብ

ዝግጁ ሲሆኑ ነው።

ጥንቃቄ የሌለው ወሲብ ለበርካታ ችግሮች ያጋልጣል።

Page 21: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

21

ጥንቃቄ የጎደለው ወሲብ ኤች አይ ቪን ጨምሮ

በወሲብ የሚተላለፉ በሽታዎች እንዲስፋፉ፣ ሰዎች

ከዓላማ ጋር የሚጋጭ የህይወት ዘይቤ እንዲኖራቸውና

ዓላማቸውን እንዲረሱ፣ያለ ዕቅድ የሚከሰት ወይም

አላስፈላጊ እርግዝና እንዲገጥማቸው፣ ወዘተ. ሊያደርግ

ይችላል።

አላስፈላጊ ወይም ያለ ዕቅድ የተከሰተ እርግዝና

በወሲብ ወቅት አስፈላጊውን ጥንቃቄ ባለማድረግና

የእርግዝና መከላከያ ዘዴዎችን ከሚመለከታቸው

ባለሞያዎች ጋር እየተመካከሩ ባለመጠቀም፣ ኮንዶምን

በአግባቡ ባለመጠቀም ወዘተ. ሊመጣ ይችላል።

በተጨማሪም ከሰዎች ቁጥጥር ውጭ በሆነ በአስገድዶ

መደፈርና መሰል ጉዳዮች ሊከሰት ይችላል።

Page 22: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

22

ከአላስፈላጊ እርግዝና ጋር በተያያዘ ብዙ ሴቶች

ለጤና አስጊ ወደ ሆነ የፅንስ ማስወረድ እርምጃ

ይገባሉ።

ጥናቶች እንደሚጠቁሙት 54 በመቶ የሚሆኑ

ሴቶች ያለ ዕቅድ የመጣን ፅንስ ለማስወረድ

በህክምና ሙያ ያልሰለጠኑ ሰዎችን/ልማዳዊ የውርጃ

ዘዴን ይከተላሉ።

ይህም በእናቶች ጤንነት ላይ ከሚያሳድረው

የጤንነት ችግር ባሻገር ንፅህናና ጥንቃቄ በጎደላቸው

መሳሪያዎች ምክንያት ኤች አይ ቪ በቀላሉ

እንዲተላለፍ ያደርጋል።

Page 23: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

23

መልመጃ 3

ስለ ወሲብ ምንነትና እንዴት ወሲብን መቆጣጠር

እንደሚቻል ከጓደኞቻችሁ ጋር ተወያዩ።

Page 24: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

24

የኤች አይ ቪ መተላለፊያ መንገዶች

ኤች አይ ቪ በሰውነታችን ውስጥ ባሉ ፈሳሾች ሁሉ

ሊገኝ የሚችል ሲሆን ለመተላለፍ በቂ የሆነ ቫይረስ

የሚገኘው በዋናነት በደም ውስጥ፣ በወንድ የብልት

ፈሳሽ ውስጥ ፣ በሴት የብልት ፈሳሽ ውስጥና በጡት

ወተት ውስጥ ነው።

በዚህም ምክንያት ኤች አይ ቪ ጥንቃቄ በጎደለው

የግብረ ሥጋ ግንኙነት፣ ስለታማ ነገሮችን አብሮ

በመጠቀም፣ በእናት ጡት ወተት፣ በህክምና ወቅት

በቫይረሱ የተያዘ ደም በመቀበል ሊተላለፍ ይችላል።

ኤች አይ ቪ ከሰው ልጅ ሰውነት ውጭ የመቆየት

አቅም ስለሌለው ከደም ግንኙነት፣ ከብልት ፈሳሽና

ከእናት ጡት ወተት ውጭ የመተላለፍ ሁኔታው

Page 25: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

25

እጅግ ደካማ ነው። ስለዚህም ጥንቃቄ የጎደለው

ወሲብ፣ ስለታማ ነገሮችን ካለአግባብ በጋራ መጠቀም፣

በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ የሚከሰት የደም መቀላቀል

እና ከእናት ወደ ልጅ በወተት፣ በውልደትና በእርግዝና

ወቅት የመተላለፍ ሁኔታን በጥንቃቄ በመከላከልና

በማስወገድ የኤች አይ ቪን የመተላለፍና የስርጭት

ሁኔታ መግታት ይቻላል።

ኤች አይ ቪ በዋናነት በስስ የቆዳችን ክፍሎች አካባቢ

(Mucus Membrane) የመተላለፍ ዕድሉ ሰፊ ነው።

ይህም የብልት አካባቢንና የአፍ አካባቢን ያጠቃልላል።

በግብረ-ሥጋ ግንኙነት ወቅት ኤች አይ ቪ

የሚተላለፈው በብልት ፈሳሾች ብቻ ሳይሆን በግንኙነቱ

ምክንያትም ሆነ በሌላ ምክንያት በሚከሰት የብልት

መላላጥና መፋተግ የተነሳ የደም መቀላቀል ሊከሰት

Page 26: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

26

ስለሚችል በመሆኑ በወንድ እና በሴት ብልት

ከሚደረጉ ግብረ ስጋ ግንኙነቶች ባሻገር በፊንጢጣ

ወይም በአፍ አካባቢ በሚደረግ የወሲብ ግንኙነት

ምክንያት ኤች አይ ቪ በእጅጉ ሊተላለፍ ይችላል።

በተለይም በፊንጢጣ የሚደረግ የግብረ ስጋ ግንኙነት

ለኤች አይ ቪ መተላለፍ እጅግ ምቹ ሲሆን ይህም

ፊንጢጣ እንደሌሎቹ የወሲብ አካላት የመለጠጥ

ባህርይ ስለሌለው በቀላሉ የመሰንጠቅና የመድማት

ባህርይ ስላለው ነው።

ሴቶች ከወንዶች የበለጠ በቫይረሱ የመያዝ ዕድላቸው

የሰፋ ሲሆን ይህም የወንዱ ብልት (ቁላ) ፈሳሽ (ምንም

እንኳን የሴቷ ፈሳሽም ወደ ወንዱ ብልት ቢገባም)

በቀላሉ ወደ ሴቷ ብልት (እምስ) የመግባት ዕድል

ስላለው ነው።

Page 27: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

27

በተጨማሪም የሴቷ ብልት (እምስ) ሰፊ ስስ ቆዳ/ክፍል

ስላለውና የስስነት መጠኑም እጅግ በጣም ከፍተኛ

መሆኑ፣ ሴቶች ከወንዶች ይበልጥ ለሌሎች በወሲብ

የሚተላለፉ በሽታዎች ተጋላጭ በመሆናቸውና ይህም

በብልት አካባቢ ቁስለት በመፍጠር ቫይረሱ በቀላሉ

እንዲተላለፍ ማድረጉ፣ ከስርዓተ-ፆታ ጋር በተያያዘ

በሴቶች ላይ የሚሰነዘር ወሲባዊ ጥቃትና ዝሙት

አዳሪነት ውስጥ እንዲሰማሩ መሆናቸው፣ በሴት

ህፃናት ላይ የሚፈፀሙ የተለያዩ ጎጂ ልማዳዊ

ድርጊቶች፣ ማህራዊና ስነ-ልቦናዊ ተፅዕኖዎች፣

የትምህርት ዕጥረት፣ ወዘተ. ሴቶችን ከወንዶች በበለጠ

ለቫይረሱ እንዲጋለጡ ያደርጋቸዋል።

በወሲብ የሚተላለፉ ሌሎች በሽታዎች ኤች አይ ቪ

በቀላሉ እንዲተላለፍ ምክንያት ይሆናሉ። በበሽታዎቹ

Page 28: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

28

ምክንያት በወሲብ አካላት ላይ የሚፈጠረው የመላላጥና

የመቁሰል ሁኔታ ቫይረሱ በቀላሉ እንዲተላለፍ

ያደርጋል።

በወሲብ ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎች ምንም

እንኳን ሴቶችን የበለጠ ቢያጠቁም በወንዶች ላይም

ይከሰታሉ።

በወሲብ ምክንያት የሚተላለፉት በሽታዎች ሁለት

ዓይነት ናቸው፡

1ኛ. በባክቴሪያ ምክንያት የሚከሰቱ

2ኛ. በቫይረስ ምክንያት የሚከሰቱ

በባክቴሪያ ምክንያት የሚከሰቱት በመድሃኒት ህክምና

መፈወስ የሚችሉ ሲሆን በቫይረስ ምክንያት

የሚከሰቱት ግን በፀረ-ቫይረስ መድሃኒቶች አማካኝነት

Page 29: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

29

ምልክቶች ቀድመው እንዳይከሰቱ ወይም እንዳይጠነክሩ

ከማድረግ ባለፈ ፈውስ የሚሰጥ መድሃኒት

አልተገኘላቸውም።

አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግና የበሽታዎቹን

ምልክቶች አስቀድመው ሲያውቁ ወይም ሲጠራጠሩ

ወደ ህክምና ባለሞያዎች በመሄድ አስፈላጊውን ሙያዊ

እርዳታ ማድረግ ያስፈልጋል።

በሴቶች ላይ በሽንትና በግብረ-ስጋ ግንኙነት ወቅት

ያልተለመደ የህመም ስሜት መሰማት፣ ያልተለመደ

ከባድ የወር አበባ መፍሰስ፣ በወሲብ አካላት ላይ

የሚከሰት ህመም፣ ወዘተ. ሲያጋጥም ባለሙያ

በማማከር ችግሩን ማወቅ ያስፈልጋል።

Page 30: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

30

በወንዶች ላይም በሽንት ወቅት ያልተለመደ የህመም

ስሜትና በወሲብ አካላት ዙሪያ እንግዳ ስሜት/ለውጥ

ከታዬ ባለሙያ ማማከር ያስፈልጋል።

Page 31: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

31

መልመጃ 4

1. ኤች አይ ቪ የሚተላለፍባቸውን ዋና ዋና

መንገዶች ዘርዝሩ፡፡

2. ኤች አይ ቪ በቀላሉ የሚተላለፍባቸው የአካል

ክፍሎች የትኞቹ ናቸው? ለምን ይመስላችኋል?

3. ሴቶች ከወንዶች ይልቅ ቫይረሱ በቀላሉ

የሚተላለፍባቸው ለምን ይመስላችኋል?

4. ያልተጠቀሱ የኤች አይ ቪ መተላለፊያ መንገዶች

አሉ ብላችሁ ታስባላችሁ? በዝርዝር አብራሩ።

5. ከኤች አይ ቪ ውጭ ያሉ በወሲብ የሚተላለፉ

በሽታዎች በኤች አይ ቪ የመተላለፍ ዕድል ላይ

ተፅዕኖ የሚያሳድሩት እንዴት ነው?

Page 32: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

32

ኤች አይ ቪ የማይተላለፍባቸው መንገዶች

ለቫይረሱ በሚሰጥ የተሳሳተ ግምትና የመተላለፊያ

መንገዶቹን ጠንቅቆ ካለማወቅ የተነሳ ብዙ ሰዎች

በዕየለቱ በሚደረግ ማንኛውም ዓይነት ግንኙነት

ውስጥ በቫይረሱ የመያዝ ስጋት ያድርባቸዋል።

የሚከተሉት ሁኔታዎች ተደጋግመው የሚነሱና ሰዎች

የሚሰጉባቸው ነገር ግን ቫይረሱ ፈጽሞ

ሊተላለፍባቸው የማይችልባቸው መንገዶች ናቸው።

የመመገቢያ ዕቃዎችን በጋራ በመጠቀም ወይም

አብሮ በመመገብ

እጅ በመጨባበጥ፣ በመተቃቀፍ፣ ጉንጭ

ለጉንጭ በመሳሳም

በወባ ትንኝ ንክሻ

Page 33: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

33

ሽንት ቤት በጋራ በመጠቀም ወይም በመቀመጥ

በሽንት፣ በላብ፣ በትንፋሽ፣ በእንባ፣ በምራቅ

ደሙን በእጅ መንካት (እጅ ተቆርጦ ወይም

ተልጦ ደም መቀላቀል እስካልቻለ ድረስ)፤ የኤች አይ

ቪ ቫይረስ በቆዳ ላይ የመሰንጠቅ ወይም የመላጥ

ሁኔታ ከሌለ ወደ ሰውነታችን ሊገባ አይችልም፤

ቫይረሱ ወደ ሰውነታችን በቀላሉ ለመግባት የሚችለው

በስስ የሰውነታችን ክፍሎች ማለትም በብልት አካባቢና

በአፍ አካባቢ ነው። ነገር ግን በእጆቻችን አካባቢ

የተላጠ ወይም የተሰነጠቀ ነገር አለመኖሩን እርግጠኛ

መሆን አለብን።

በልብስ

በማበጠሪያ

Page 34: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

34

አብሮ በመተኛት

ቫይረሱ ከሰው አካል ወጥቶ ብዙ መቆየት

ስለማይችል ከደም ንክኪ ውጭ በተለያዩ ቁሳቁሶች

አብሮ በመጠቀምና የአካል ንክኪ በማድረግ

ይተላለፋል ብሎ መስጋት በፍፁም አያስፈልግም።

Page 35: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

35

መልመጃ 5

1. ኤች አይ ቪ የማይተላለፍባቸው መንገዶች ምን

ምን ናቸው?

2. በቫይረሱ የተያዘን ሰው ደም በእጅ መንካት

ቫይረሱን የማያስተላልፈው ለምን ይመስላችኋል?

3. ኤች አይ ቪ እስከ ሰባት ቀን ድረስ ከሰው አካል

ውጭ ሆኖ መቆየት ይችላል (እውነት/ሀሰት)፤

ምክንያታችሁን አብራሩ።

Page 36: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

36

ኤች አይ ቪ እና ማህበራዊ ችግሮች

ኤች አይ ቪ በርካታ ማህበራዊ ጎኖች ያሉት የጤና

ችግር በመሆኑ ከማህበራዊ ችግሮች እንደ አንዱ

ተደርጎ ይቆጠራል።

ከማህበራዊ ችግሮች ውስጥ እጅግ በጣም መሰረታዊና

ማህበራዊ ደህንነትን የሚያናጉት (ማህበራዊ ጠንቆች)

የሚከተሉት ናቸው፡-

ሴተኛ አዳሪነት፣

የአደገኛ እጾችና የአልኮል ጥገኝነት፣

ቦዘኔነት፣

ወጣት ጥፋተኝነት፣

ለምኖ አዳሪነት፣

Page 37: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

37

የጎዳና ተዳዳሪነት፣

ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እና

ኤች አይ ቪ/ኤድስ ናቸው።

ማህበራዊ ችግሮች እርስ በርስ የተቆላለፉና አንዱ

የሌላኛው ደጋፊ በመሆን የህብረተሰቡን ኑሮ በእጅጉ

የሚያናጉ በመሆናቸው ምክንያት በተናጠል ለመፍታት

እጅግ አስቸጋሪ ናቸው።

ስለዚህም እያንዳንዱን ማህበራዊ ችግር በመከላከልና

ራሳችንን በመጠበቅ ከኤች አይ ቪ ነፃ የሆነ ጤናማ

ህይወት መኖር እንችላለን።

በአደገኛ ሱሶች መጠመድ ጥንቃቄ ወደጎደለው ወሲብ

ሊመራን ይችላል፤ ይህም በኤች አይ ቪ እንድንያዝና

ጤናማ ህይወት እንዲርቀን ሊያደርግ ይችላል።

Page 38: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

38

በተመሳሳይ ሌሎችም ችግሮች በአንድ ወይም በሌላ

መንገድ ወደ ኤች አይ ቪ ስለሚወስዱን ጥንቃቄ

ማድረግና ጓደኞቻችንም ማስተማር ከእኛ የሚጠበቅ

ተግባር ነው።

Page 39: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

39

ኤች አይ ቪ፣ ሥርዓተ-ጾታና ጎጅ ልማዳዊ

ድርጊቶች

ጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች በህብረተሰቡ ውስጥ በልማድ

የሚፈጸሙና በአካል፣ በአዕምሮ፣ በስነ-ልቦና፣

በኢኮኖሚ፣ ወዘተ. ህይወታችን ውስጥ ጉዳት

የሚያደርሱ የህብረተሰቡ የወግና የባህል መጥፎ

ገፅታዎች ናቸው።

ጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች በዋናነት በሴቶችና በህጻናት

ላይ የሚደርሱ ሲሆኑ በህብረተሰቡ ውስጥ ለረጅም

ጊዜ የቆየው የተሳሳተ ስርዓተ-ፆታ ትልቁ ምክንያት

ተደርጎ ይጠቀሳል።

ስርዓተ-ፆታ ማለት ማህበረሰቡ ለሴትና ወንድ ፆታዎች

የሚሰጠው የወንድነት እና የሴትነት መለያ ባህርይ

Page 40: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

40

ሲሆን ይህም በሰው ልጅ ማህበራዊ ኑሮ ውስጥ

በሂደት የሚፈጠርና የፆታን ማህበራዊና ባህላዊ ገፅታ

የሚያሳይ ነው።

ፆታ ስነ-ህይወታዊ ወይም ተፈጥሯዊ የወንድነት እና

የሴትነት መለያ ባህሪ ነው።

በቅርብ ጊዜ በሳይንሱ ዓለም ፆታን በህክምና የመቀየር

ሁኔታዎች ቢስተዋሉም በዋናነት ጾታ ሊቀየር

የማይችል ተፈጥሯዊ ባህርይ ነው።

የተሳሳተና ፍትሃዊ ያልሆነ የስርዓተ-ፆታ መኖር

ፆታዊነት ጎልቶ እንዲወጣ ማለትም ለአንዱ ፆታ

የተጋነነ ግምት የመስጠትና ሌላውን የመናቅ ወይም

የማንቋሸሽ ዝንባሌ እንዲኖርና እንዲስፋፋ አድርጓል።

Page 41: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

41

ሴቶች በተለያዩ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ

ሂደቶች ውስጥ ያላቸው ተሳትፎ በተሳሳተ ስርዓተ-ጾታ

ምክንያት እጅግ የተገደበ ነው። ይህን ተከትሎ ከቅርብ

ጊዜ ወዲህ የሴቶች መብት አቀንቃኞች (Feminists)

የተለያዩ ሀሳቦችን በማራመድ የሴቶችን የፆታ

እኩልነት ለማረጋገጥ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ፡፡

ስለሆነም የስርዓተ-ፆታው የተሳሳተ መሆን ሴቶች

የጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች ዋነኛ ዒላማ እንዲሆኑ

አድርጓል።

ጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች እጅግ በጣም ዘርፈ ብዙ

ገጽታና ባህርይ ቢኖራቸውም በዋናነት ግን በሳይንሳዊ

መረጃ ላይ ያልተደገፉ ትውፊታዊ ስነ-ስርዓቶች

የሚንጸባረቁባቸው ናቸው።

Page 42: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

42

በተለያዩ ቦታዎችና አገራት የተለያዩ ጎጅ ልማዳዊ

ድርጊቶች ቢኖሩም በአገራችን ላይ ጎልተው

የሚስተዋሉ ዋና ዋና ድርጊቶች ግን ከዚህ

የሚከተሉት ናቸው።

የሴት ልጅ «ግርዛት»፡ የሴት ልጅ ግርዛት የሴት

ህጻናትን ብልት በከፊል ወይም በሙሉ የመቁረጥ

ተግባር ሲሆን ይህም ከቦታ ቦታ የተለያየ ዓይነትና

መጠን ይይዛል። የሴት ልጅ «ግርዛት» ባብዛኛው

በሶስት ዓይነት ሊከፈል ይችላል።

አንደኛው፤ ሱና በመባል የሚታወቀው ከወንድ ልጅ

ግርዛት ጋር የሚመሳሰል እና የላይኛውን የብልት

ክፍል (ላቢያ ማጆራ) በከፊል ወይም በሙሉና

የቂንጥርን ጫፍ የመቁረጥ ሁኔታ ነው።

Page 43: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

43

ሁለተኛው፤ ክላይትሮዴክቶሚ የሚባለው ዓይነት

ሲሆን ይህም በብዙ ቦታዎች የተለመደ ነው። ይህ

ድርጊት የብልትን የውስጥ ክፍል (ላቢያ ማይኖራ) እና

ቂንጥርን ሙሉ ለሙሉ የመቁረጥ ሁኔታ ነው።

ሶስተኛውና በአገራችን ውስጥ በተወሰኑ ቦታዎች ብቻ

የሚፈጸመው ኢንፉቡሌሽን በመባል የሚታወቀው

እጅግ አሰቃቂ ድርጊት ነው። በዚህ ድርጊት ከላይ

የተጠቀሱት ድርጊቶች እንደተጠበቁ ሆነው

በተጨማሪነት የላይኛው የብልት ክፍል ፈፅሞ

የሚወገድበትና የሴቷ ብልት ለሽንት ቀዳዳ ብቻ

በመተው የሚሰፋበት እንዲሁም በኣንዳንድ ቦታዎች

የተለያዩ ባዕድ ቁሶች የሚሰኩበት ሁኔታ ነው።

ሶስተኛውን ዓይነት «ግርዛት» በተመለከተ

ኢትዮጵያዊቷ የአለም ሞዴል ሊያ ከበደ በተወነችበት

Page 44: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

44

“The Desert Flower” በሚል ፊልም ላይ የችግሩ

ስፋት በሰፊው ይታያል።

የሴት ልጅ «ግርዛት» ስነ-ልቦናዊ፣ አካላዊና ወሲባዊ

ችግሮችን የሚያስከትል ሲሆን ይህም በወደፊቱ የሴቷ

ህይወት ላይ ከባድ ጠባሳ ይፈጥራል።

የድርጊቱ ዋና መንስኤ ወሲብን በአዕምሮ ቁጥጥር ስር

ያልሆነ የደመ-ነፍስ ውጤት ብቻ እንደሆነ አድርጎ

መመልከት ሲሆን ይህም ወሲብን ለመቆጣጠር በሚል

ሃሳብ ለወሲብ ወሳኝ የሆኑትን የአካል ክፍሎች ወደ

መቁረጥ ያመራል።

በድርጊቱ ምክንያት የተቆረጠው ብልት የመለጠጥ

ባህሪውን ስለሚያጣ በወሲብ ወቅት ከባድ ህመምና

ስቃይ ይፈጥራል። ወደፊትም በወሊድ ጊዜ ከፍተኛ

Page 45: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

45

ችግር እንዲከሰት ያደርጋል፡፡ ይህም ጊዜ ተሻጋሪ

ለሆነው የስነ-ልቦና ችግር ያጋልጣል።

በአጠቃላይ ደህንነት ላይ ከሚያደርሰው ሁለንተናዊ

ችግር ባሻገር ብልትን ለመቁረጥ የሚውሉ ስለታማ

መሳሪያዎች በአግባቡና በጥንቃቄ የማይያዙ

በመሆናቸው ኤች አይ ቪን በቀላሉ ያስተላልፋሉ።

ያለዕድሜ ጋብቻ፡ ህፃናት በአግባቡ ለወሲብ

ሳይደርሱና ዝግጁ ሳይሆኑ እንዲያገቡ የሚገደዱበት

ሁኔታ ነው። ይህ ድርጊት ምንም እንኳን በሁለቱም

ጾታዎች ላይ የሚከሰት ቢሆንም በሴቶች ላይ ግን

በብዛትም በተጽዕኖ ደረጃም ጎልቶ ይስተዋላል።

Page 46: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

46

በትምህርት፣ በማህበራዊ፣ በአካል ወዘተ. ላይ

ከሚያደርሰው ወሰን የለሽ ጫና ባሻገር በህጻናቱ ስነ-

ልቦና ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያሳድራል።

ህፃናት በአግባቡ የልጅነት ጊዜያቸውን ካላሳለፉ

በልጅነታቸው ማግኘትና ማደበር ያለባቸውን ነገር

በሙሉ እንዲያጡ ይሆናሉ። ልጅነቱን የተነጠቀ ሰው

ምንድነው? ምን ዓይነት ስብዕና ይኖረዋል?

ልጅነት የሰው ልጅ ባህርይ የሚወሰንበት ዋና ዘመን

እንደሆነ የባህርይ ጥናቶች በሰፊው ያብራራሉ።

ወንድ ልጅን ማስቀደም፡ ይህ ከጠቅላላ የስርዓተ-

ፆታ ስርዓቱ ጋር የተቆራኘ ቢሆንም በሴት ህፃናት ላይ

የሚፈጸመው አድልኦና የተሳሳተ ግምት እጅግ መጠነ-

ሰፊ ጉዳት ያስከትላል። በአገራችን በውልደት ጊዜ

Page 47: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

47

እንኳን ለሴት ህፃንና ለወንድ ህጻን የተለያየ የእልልታ

ብዛት በማስቆጠር የሴትን ልጅ ማንነት ዝቅ አድርጎ

የማየት ሁኔታ ይስተዋላል።

ጆን ስቱአርት ሚል የተሰኘ ሊቅ በሴት ልጅ ላይ

የሚደርሰው መድልኦና ጭቆና ሳይንሳዊ መሰረት

የሌለውና በአንድ የታሪክ አጋጣሚ ተፈጥሮ በሂደት

የጎለበተ ሁነት እንደሆነ ያብራራል።

በሴቶች ላይ የሚደርሰው ጥቃት በተፅዕኖም ሆነ

በብዛት በህፃንነት ዘመን ላይ የከፋ ቢሆንም በሁሉም

የዕድገት ዘመን ላይ ችግሩ ይስተዋላል።

የአገሪቱ ህገ-መንግስት አንቀፅ 35 ሴቶችን በተመለከተ

የፆታ እኩልነትንና ከመጥፎ ድርጊቶች የመጠበቅ

መብት እንዳላቸው ይደነግጋል።

Page 48: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

48

በአገሪቱ ላይ ያሉት የቤተሰብ ህጎችም በጋብቻ ውስጥ

ሴቶች የወንዶች የበታች እንዳልሆኑና የእኩልነት

መብት እንዳላቸው ያስቀምጣሉ።

የአገሪቱ የወንጀለኛ መቅጫ ህግና ሌሎች ህጎችም

አስገድዶ መድፈር፣ ያለ ዕደሜ ጋብቻ፣ የሴት ልጅ

‹ግርዛት›ና ተያያዥ የሆኑ ጥቃቶች እንዳይፈፀሙ

ይከለክላል።

ሴቶች በማህበረሰቡ ውስጥ የሚኖራቸውን ሁለንተናዊ

ተሳትፎ ለማጎልበትና ለተለያዩ ችግሮች እንዳይጋለጡ

እያንዳንዳችን ለጓደኞቻችን፣ ለቤተሰቦቻችን፣ ወዘተ.

ግንዛቤ ማስጨበጥና ድርጊቱን በመከላከል ሂደቱም

ከህግ አካላት ጋር በመተባበር መስራት ይጠበቅብናል።

Page 49: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

49

በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ በሴቶች ላይ የሚደርስን

በደልና ጥቃት በመከላከልና ትክክለኛ ስርዓተ-ፆታ

እንዲኖር በማድረግ በሴቶች ላይ የሚታየውን የኤች

አይ ቪ ተጋላጭነት መግታትና ተያይዞ የሚመጣውን

መገለልና መድልኦም ማቆም የሚቻልበት ሁኔታን

መፍጠር እንችላለን።

ቀጥሎ የቀረበውን ሰንጠረዥ በመመልከት የችግሩን

ስፋትና አሳሳቢነት መረዳት ይቻላል።

Page 50: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

50

የህይወት ዘመን የጥቃት/በደል/ተፅዕኖ አይነት

ፅንስ ሴትን መርጦ ማስወረድ

አራስ/ጨቅላ/ ስሜታዊና አካላዊ ጥቃት፣

የምግብና የህክምና አቅርቦት

ማጣት፣ ወዘተ.

ህፃን ‹ግርዛት›፣ ወሲባዊ ጥቃት፣

የምግብና ህክምና አቅርቦት

ማጣት፣ ወዘተ.

ቆንጆ/ልጃገረድ ለፆታዊ ግንኙነት መገደድ፣

ማስፈራሪያና ዛቻ መቀበል፣ ተገዶ

መደፈር፣ በግዳጅ ዝሙት አዳሪ

መሆን፣ ያለፍላጎት ዝውውርና

Page 51: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

51

የሌሎች ዓላማ ማስፈፀሚያ

መሆን፣ ወዘተ

አዋቂ በፍቅር/ትዳር ጓደኛ የሚሰነዘር

ጥቃት፣ ስነ-ልቦናዊ ጥቃት፣ በስራ

ቦታዎች የሚደርስ የወሲብ ትንኮሳ

ወይም ጥቃት፣ ወዘተ.

አረጋዊ

ከእርጅና ጋር ተያይዞ የሚመጣ

ጥቃት፣ ዘለፋ፣ ወዘተ.

Page 52: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

52

መልመጃ 6

1. ስርዓተ-ጾታና ጾታ ልዩነታቸው ምንድነው?

2. ዋና ዋናዎቹን ጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች ጥቀሱ፡፡

3. በአካባቢያችሁ የሚስተዋሉ ጎጅ ልማዳዊ

ድርጊቶችን ዘርዝሩ፡፡

4. የሴት ልጅ ግርዛት ምን ምን ዓይነት ደረጃዎች

ሊኖሩት ይችላል?

5. ኤች አይ ቪና ጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች ምን

ዓይነት ዝምድና እንዳላቸው አብራሩ፡፡

Page 53: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

53

አደገኛ ዕፆች፣ አልኮልና ኤች አይ ቪ

አደገኛ ዕጾች ለአካላዊም ሆነ ለአዕምሯዊ ጤንነት

መጥፎ ከመሆናቸውም ባሻገር የውሳኔና በጥልቀት

የማሰብ ክህሎታችንን በማዳከም ወደ ልቅ ወሲብ

በመምራት ለኤች አይ ቪና መሰል በሽታዎች

ያጋልጡናል።

በአገራችን እየተለመደ የመጣው ጫት የመቃም ሁኔታ

በሁለንተናዊ ደህንነታችን ላይ ትልቅ ጫና እየፈጠረ

ይገኛል።

ጫት የአዕምሮ መልዕክት አስተላላፊ የሆኑ

ኬሚካሎችን ስራ በማወክ ጤናማ አስተሳሰብ

እንዳይኖረን ያደርጋል። ከዛም ባሻገር ወደ ሲጋራና

አልኮል በማምራት የከፋ ችግር ይፈጥራል።

Page 54: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

54

የአልኮል አጠቃቀማችን ሶስት ዓይነት ሊሆን

እንደሚችል ባለሙያዎች ያብራራሉ።

አንደኛው አልኮልን በአግባቡ መጠቀም ሲሆን ይህም

ከጤናማና ማህበራዊ አልኮል አወሳሰድ ያላፈነገጠ

የአልኮል አጠቃቀም ነው።

ሁለተኛው የአልኮል ስነ-ልቦናዊ ጥገኝነት ሲሆን ይህ

በብዛትም ሆነ በድግግሞሽ መጠን ከማህበረሰቡና

ከጤናማ አልኮል አወሳሰድ ያፈነገጠ ሲሆን ይህም ስነ-

ልቦናዊ ጥገኝነትን በማስከተል ተጠቃሚው

አጠቃቀሙን ለመቆጣጠር የሚቸገርበት ሁኔታን

ሲፈጥር ነው።

ሶስተኛው አካላዊና ስነ-ልቦናዊ ጥገኝነት ሲፈጠር

የሚከሰት ነው። ተጠቃሚው ከስነ-ልቦናዊ ጥገኝነት

Page 55: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

55

ባሻገር ስነ-ህይወታዊ ሂደቱም ከአልኮል ጋር በመላመድ

ያለ አልኮል በአግባቡና በደህና ሁኔታ መንቀሳቀስ

ሲሳነው የሚፈጠር ሁኔታ ነው።

አልኮል ጠጥቶ መስከር በአስተሳሰብ ሚዛናዊነት ላይ

ጫና በመፍጠር ወደ ደመ-ነፍሳችን እንድናጋድል

ስለሚያደርግ ጥንቃቄ ወደ ጎደለው ወሲብ ያመራናል፤

ይህም ለኤች አይ ቪ በቀላሉ እንድንጋለጥ ያደርገናል።

በመሆኑም የአደገኛ ዕፆችና አልኮል ተገዢነት

ሳይጠነክርና ሳይዳብር ለማስወገድ የሚከተለውን ዘዴ

መጠቀም ይቻላል።

1. ችግርን በአግባቡ መለየት

ለምሳሌ፣ አልኮል መጠጣት

2. ትክክለኛውን አስቸጋሪ ባሕሪ መለየት

Page 56: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

56

ለምሳሌ፣ ከልክ በላይ መጠጣት፣ ደጋግሞ

መጠጣት

3. የባህሪ መለወጫ ዕቅድ ማዘጋጀት

3.1. ከችግሩ ጋር የተያያዙ ነገሮችን ማስወገድ

ለምሳሌ፣ የቢራ ጠርሙስ፣ ወደ

ድራፍት ቤት መሄድ

3.2. አማራጭ ጥሩ ባህሪ ማዳበር

ለምሳሌ፣ ማስቲካ ማኘክ፣ ማኪያቶ

መጠጣት፣ መጽሃፍ ማንበብ፣

መንሸራሸር/የእግር እንቅስቃሴ ማድረግ

3.3. አዲሱን ልማድ ማጠናከር

Page 57: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

57

ለምሳሌ፣ ከሽርሽር መልስ ፊልም ማየት፣

ጓደኞቻቸው በሚበዙበት ወይም የሚወዱት ሰው

ወደሚያዘወትርበት ካፌ መሄድ

3.4. ወደ ነበሩበት ከባቢ/ሁኔታ መመለስ

ለምሳሌ፣ መጠጥ ቤት ገብቶ ወይም አልኮል

እየጠጣ ካለ ሰው ጋር ተቀምጦ ለስላሳ መጠጣት

3.5. ችግሩንና የችግሩን መጠን መመርመርና

ማጥናት

ለምሳሌ፣ በየቀኑ መጠጣት፣ በየሳምንቱ

መጠጣት፣ ሁለት ቢራ መጠጣት፣ አምስት ቢራ

መጠጣት

4. በዕቅዱ ላይ የተቀመጠውን መተግበር

Page 58: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

58

4.1. ቀስ በቀስ ማሻሻል/ ባህሪን መለወጥ

ለምሳሌ፣ የመጠጡን መጠንና ድግግሞሽ

መቀነስ፡ ከአምስት ቢራ ወደ ሶስት፣ ከሶስት ወደ

ሁለት

4.2. ለውጡን መለካት፤ ሁኔታውን በማጤን

እንደገና ማቀድ ወይም ዕቅድን ማስተካከል፤ እንደገና

መተግበር፤ ማምጣት የሚፈልጉትን ባህሪ በምናብ

መቃኘት

4.3. ለውጡን በማረጋገጥ ሂደቱን ማጠናቀቅ

Page 59: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

59

መልመጃ 7

1. የአልኮል ስነ-ልቦናዊ ጥገኝነት ስንል ምን

ማለታችን ነው?

2. አደገኛ ዕፆችና አልኮል ለኤች አይ ቪ ምክንያት

የሚሆኑት እንዴት ነው?

3. በአካባቢያችሁ የአደገኛ ዕፆችና የአልኮል ተጠቃሚ

የሆኑ ሰዎችን በአዕምሯችሁ ዘርዝሩ፤ ምን ዓይነት

ተመሳሳይ ባህርይ አገኛችሁባቸው?

4. ካሁን በፊት የአደገኛ ሱሶችና የአልኮል ተገዢ

ከነበሩ ባህርይዎትን ለማስተካከል ምን አስበዋል?

Page 60: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

60

የበጎ ፈቃድ የስነ-ምክር አገልግሎትና

ኤች አይ ቪ ኤድስ

ስነ-ምክር/Counseling/፡ ስነ-ምክር የሰው ልጅ ስነ-

ልቦናዊ ችግር በሳይንሳዊ መንገድ የሚፈታበት ወይም

መፍትሄ የሚፈለግበት ሂደት ነው።

የሰው ልጅ ባህርይ በተለያዩ ምክንያቶች ጤናማነቱን

ሲያጣና ሰዎች ህይወታቸውን በትክክል መምራት

ሲያቅታቸው ደስተኛና ጤናማ ህይወት ለመምራት

ይቸገራሉ። ስነ-ምክር ይህን ችግር በሳይንሳዊ ሂደት

የምንፈታበት ዘዴ ነው።

ስነ-ምክር ከምክር በእጅጉ ይለያል፤ ምክር (Advice)

ሳይንሳዊ ያልሆነ በቤተሰብ፣ በጓደኛ፣ ወይም በሌላ

ቅርብ ሰው የሚሰጥ የቃል ውይይትን መሰረት ያደረገ

Page 61: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

61

ሂደት ሲሆን በእጅጉ አቅጣጫ የሚያመለክትና ሰዎች

በየት አቅጣጫ መሄድ እንዳለባቸውና ህይወታቸውን

እንዴት መምራት እንዳለባቸው በመካሪው

የሚወሰንበት ሂደት ሲሆን ስነ-ምክር ግን ተመካሪው

ችግሩን በራሱ እንዲፈታ ወደ ትክክለኛ አዕምሯዊ

ሁኔታ የሚመራ ሳይንሳዊ መንገድ ነው።

ስነ-ምክር በትምህርት፣ በእፅና አልኮል ሱስ፣ በሙያ፣

በኤች አይ ቪ፣ በአካል ጉዳተኝነት፣ በወንጀለኝነት፣

ወዘተ. ዙሪያ አተኩሮ ሊሰጥ ይችላል።

ስነ-ምክር ችግር ከመከሰቱም በፊትም ይሁን ከተከሰተ

በኋላ ሊሰጥ ይችላል።

የኤች አይ ቪ የምክር አገልግሎት በዋናነት ሁለት

ደረጃዎች አሉት።

Page 62: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

62

አንደኛው፤ ከደም ምርመራ በፊት የሚሰጥ የቅድመ-

ምርመራ የምክር አገልግሎት (Pre-test Counseling)

ሲሆን ይህም አንድ ሰው የደም ምርመራ ከማድረጉ

በፊት ለምርመራው ዝግጁ እንዲሆንና ውጤቱን በፀጋ

እንዲቀበል ለማድረግ የሚሰጥ አገልግሎት ሲሆን

ያለዚህ አገልግሎት ወደ ምርመራ መግባት አስፈላጊ

ስላልሆነ ወደ ምርመራ ከመግባታችን በፊት ይህን

የስነ-ምክር አገልግሎት ማግኘታችንን ማረጋገጥ

ያስፈልጋል።

በቅድመ-ምርመራ ስነ-ምክር ወቅት በቂ ስነ-ልቦናዊ

ዝግጁነት አላዳበርንም ተብሎ ከታሰበ ከባለሙያው ጋር

በመነጋገር በሚሰጠን አቅጣጫ መሰረት በሌላ ቀጠሮ

ተገኝተን የምክር አገልግሎቱን መውሰድና ዝግጁ

መሆን ይጠበቅብናል።

Page 63: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

63

የስነ-ምክር ባለሙያው ማናቸውንም የሂደቱን

ሚስጥሮችና በሂደቱ የተደረጉ የቃላት ውይይቶችን

ለሌላ አካል አሳልፎ ለመስጠት የሙያ ስነ-ምግባሩ

ስለማይፈቅድለት የባለሙያውን ጥያቄዎች በአግባቡ

መመለስ ያስፈልጋል።

ወሲብ ከፈጸሙ ከሁለት ወይም ሶስት ወራት ያልበለጠ

ጊዜ ከሆነ በምርመራ ሂደቱ ቫይረሱ መኖሩን

ለማረጋገጥ ስለሚያስቸግር (ይህ ጊዜ “Window

Period” ይባላል) ለባለሙያው ጉዳዩን በግልፅ መናገር

ያስፈልጋል።

ሁለተኛው ደረጃ የድህረ-ምርመራ ስነ-ምክር (Post-

test Counseling) ሲሆን የደም ምርመራውን

ተከትሎ የምርመራ ውጤታችን (Sereostatus)

Page 64: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

64

ምንም ይሁን ምን በተረጋጋ መንፈስ ለመቀበል

እንድንችል የሚያግዘን ሂደት ነው።

የምርመራ ውጤቱ ፖዘቲቭ ከሆነ ቀጣይ ህይወታችንን

በጤናማነት ለማስቀጠል ምን ማድረግ እንደሚገባን

ለመወሰን የሚያስችል ስነ-ልቦናዊ ጥንካሬንና

ምክንያታዊነትን ያላብሰናል።

የኤች አይ ቪ የምርመራ ውጤታችን ኔጌቲቭ

የሚያመለክት ከሆነም ለወደፊቱ ምን ዓይነት ጥንቃቄ

ማድረግ እንዳለብንና የህይወት ዘይቤያችን ምን መሆን

እንዳለበት ለማቀድ የሚያስችል ልቦና እንድናዳብር

ያደርገናል።

ከምርመራ በኋላ በምንም ዓይነት ሁኔታ የስነ-ምክር

አገልግሎቱን ሳናገኝ መሄድ የለብንም።

Page 65: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

65

በህይወታችን ውስጥ ማናቸውም ችግሮች ሲገጥሙን

(ለሱስ ስንጋለጥ፣ ውሳኔ ለመስጠት ስንቸገር፣ ወዘተ.)

ለስነ-ምክር ባለሙያዎች ማማከር አስፈላጊ ነው።

የኤች አይ ቪ ምርመራ፡ አንድ ሰው ኤች አይ ቪ

በደሙ ውስጥ መኖሩ የሚረጋገጠው በደም ምርመራ

ብቻ ነው።

በተለያዩ የተሳሳቱ አመለካከቶችና አሉባልታዎች

ምክንያት ብዙ ሰዎች ኤች አይ ቪ በደም ውስጥ

ያለበትን ሰው ያለምርመራ በእይታ ወይም መሰል

ግምት ለመለየት ይሞክራሉ።

የኤች አይ ቪ ምርመራ ማካሄድ ጠቀሜታው እጅግ

የጎላ ነው። መመርመር ውጤቱ ፖዘቲቭ ለሆነ ሰው

ቫይረሱ ወደሌላ እንዳይተላለፍ እንዲጠነቀቅ፣ ጤናውን

Page 66: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

66

ከሚጎዱ ነገሮች ራሱን በመቆጠብ ጤናማ ህይወት

እንዲመራ፣ የድጋፍና እንክብካቤ ተጠቃሚ እንዲሆን፣

ራሱን ከተለያዩ ህመሞች (Opportunistic Infections)

ቀድሞ እንዲከላከል፣ የጸረ-ኤች አይ ቪ መድሃኒት

ተጠቃሚ እንዲሆን፣ ወዘተ. በማድረግ ጤናማ

ህይወት ለመምራት ያስችላል።

የምርመራ ውጤቱ ኔጌቲቭ ለሆነ ሰው ደግሞ የወሲብ

ህይወቱን እንዲፈትሽ፣ አስፈላጊውን ጥንቃቄ

እንዲያደርግ፣ ጤናማነቱን በማረጋገጥ ቀጣይ

ለማድረግ እንዲዘጋጅ፣ ወዘተ. በማድረግ ጤናማ

ህይወትን ለማጽናት ያስችላል።

የኤች አይ ቪ ምርመራ ዕድሜ፣ ጾታ፣ ስራ፣ ወዘተ.

የሚያስፈልገው አይደለም። ማንኛውም ሰው የኤች አይ

ቪ ምርመራ ማካሄድ ይጠበቅበታል።

Page 67: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

67

በተለይም ከጋብቻ በፊት፣ ልጅ ለመውለድ ሲታሰብ፣

ወዘተ. ምርመራን እንደ አንድ ቅድመ-ሁኔታ

ማስቀመጥ ያስፈልጋል።

ህጻናት እንደተወለዱም ሆነ ከተወለዱ በኋላ የኤች

አይ ቪ ምርመራ እንዲያካሂዱ ማድረግ ውጤቱ

ምንም ቢሆን እጅግ በጣም ጠቃሚ ነው።

ህጻናቱ ኤች አይ ቪ በደሙ ውስጥ ካለ ሰው የተወለዱ

ከሆኑና የህጻኑ የምርመራ ውጤት ነጌቲቭ ከሆነ

በጡት ወተት እንዳይተላለፍበት አስፈላጊውን እርምጃ

ለመውሰድ ያስችላል፤ ውጤቱ ፖዘቲቭ ከሆነ ደግሞ

ለህጻኑ የሚያስፈልገውን እንክብካቤ እና ድጋፍ

ለማድረግ ያስችላል።

Page 68: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

68

እናቶች ከእርግዝና በፊት ምርመራ በማድረግ ቫይረሱ

በደሙ ውስጥ ያለበት ህጻን እንዳይወለድ አስፈላጊውን

ሰብዓዊ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል። በእርግዝና ወቅት

ተመርምረው ኤች አይ ቪ ፖዘቲቭ የሆኑ እናቶች

በእርግዝና ሂደቱ ውስጥ ቫይረሱ ወደ ፅንሱ

እንዳይተላለፍ የጤና ባለሙያዎችንና

የሚመለከታቸውን አካላት ማነጋገርና አስፈላጊውን

ምክርና እገዛ ማግኘት ያስፈልጋል።

የኤች አይ ቪ ምርመራ በፈቃደኝነት መካሄድ ያለበት

በመሆኑ ማንም ‹ነፍስ ያወቀ› (መወሰን የሚችል) ሰው

ያለፍላጎቱ ወይም ያለ ዕውቅናው እንዲመረመር

ማድረግ ተገቢ አይደለም።

በአገራችን የኤች አይ ቪ ምርመራ እንዲያደርጉ

የሚገደዱ የወታደራዊ አውሮፕላን አብራሪዎች እና

Page 69: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

69

(በአገሪቱ ህጎች ላይ ባይጠቀስም) ለስራ ወደ ውጭ

አገር የሚሄዱ ሰዎች ብቻ በመሆናቸው ከነዚህ ውጭ

ያለ ግለሰብ ያለ ሙሉ ፈቃዱ የኤች አይ ቪ ምርመራ

እንዲያደርግ መገፋፋት፣ መወትወት፣ ማስገደድ፣ ያለ

ፈቃዱ ምርመራ ማድረግ፣ ወዘተ. ተገቢ አይደለም።

በመሆኑም ሰዎች በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ

የኤች አይ ቪ ምርመራ እንዲያካሂዱና ራሳቸውን

እንዲያውቁ ለማድረግ በኤች አይ ቪ ዙሪያ መረጃ

መለዋወጥ፣ የሚተላለፍባቸውንና

የማይተላለፍባቸውን መንገዶች ለይቶ ማስረዳት፣

መገለልና መድልኦን መግታትና አስፈላጊው የባህሪ

ለውጥ እንዲመጣ ከሚመለከታቸው ባለሙያዎች

ጋር በመተባበር መስራት ከሁላችንም የሚጠበቅ

ተግባር ነው።

Page 70: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

70

መልመጃ 8

1. የኤች አይ ቪ የስነ-ምክር አገልግሎት ለምን

ይጠቅማል?

2. የኤች አይ ቪ ምርመራ ማድረግ ያለባቸው

የህብረተሰብ ክፍሎች የትኞቹ ናቸው?

3. የኤች አይ ቪ ምርመራ ለምን ይጠቅማል?

4. እርስዎ ተመርምረዋል? ስንት ጊዜ?

Page 71: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

71

የስሜት ልዕልና/ማዕምር (Emotional Intelligence)

ከሰው ልጅ አዕምሯዊ ብቃት (IQ) በበለጠ ሁኔታ

ለሰው ልጅ ስኬታማ ህይወት (Self-actualization)

ትልቅ አስተዋፅዖ ያለው የስሜት ልዕልና (EI)

እንደሆነ ምሁራን ይገልፃሉ።

ጎልማን የተባለ ምሁር የስሜት ልዕልና 80 በመቶ

የሚሆነውን የሰው ልጅ አቅም እንደሚለካ ያብራራል።

ስሜታዊ ልዕልና የሚከተሉትን ክሂሎች ያጠቃልላል፡

1. ራስን ማወቅ (Self-awareness)

2. ስሜትን መቆጣጠር (Handling Emotions)

3. ተነሳሽነት (Motivation)

4. ስለ ሌሎች ማሰብ (Empathy)

5. ማህበራዊ ክህሎት (Social Skills)

Page 72: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

72

ስለ ሌሎች ማሰብ (Empathy)

ስለሌሎች ማሰብ ማለት ሌሎች ያሉበትን ሁኔታና

የድርጊታቸውን መንስኤ በአግባቡ መረዳትና እነሱን

ሆኖ ጉዳዩን መመልከት ማለት ነው። ስለ ሌሎች

ማሰብ (Empathy) እና ለሌሎች ማሰብ (Sympathy)

የተለያዩ ነገሮች ናቸው።ስለ ሌሎች ማሰብ ማለት

የሰዎችን ችግር እነሱን ወክሎ ወይም ራሱን በምናቡ

እነሱን ሆኖ ማሰብ ሲሆን ለሌሎች ማሰብ ግን

ለሌሎች የሃዘኔታ ወይም የእንክብካቤ ስሜት ማሳየት

ወይም ያሉበትን ችግር ከውጭ ሆኖ (እነሱን ሳይሆኑ)

መረዳት ማለት ነው።

እያንዳንዳችን ሌሎችን እንደጥፋኛ ስንቆጥር፣ እድለ-

ቢስነታቸውን ስንናገር፣ በሌሎች ላይ መጥፎ ሃሳብ

ስናስብ ወይም መጥፎ ድርጊት ስንፈፅም እነሱን ሆነን

Page 73: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

73

ወይም እነሱ ያሉበት ሁኔታ ውስጥ ራሳችን ብንሆን

ብለን በትክክለኛ ሁኔታ ማሰብ ነው።

ስለሌሎች ማሰብ ሶስት የዕድገት ዓይነቶችን ወይም

ብቃቶችን ይጠይቃል።

አንደኛ፤ በአዕምሮ ማደግ ሲሆን ይህም የምናብ

ችሎታን የሚጠይቅ ነው። በሰዎች ላይ ለመፍረድ

ወይም ስለሰዎች ያለንን አመለካከት ትክክለኝነት

ለማረጋገጥ ራስን በሌሎች ሁኔታ ውስጥ እንዳሉ

አድርጎ ማሰብን ይጠይቃል፡፡ ይህ የአዕምሮ ዕድገት

ወይም ብቃት ነው፡፡

የሚከተሉትን ጥያቄዎች በመመለስ አዕምሯዊ

ዕድገታችሁን መዝኑ፤

Page 74: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

74

1.የምትጠሉትን ወይም የምትጠሏትን

የምትናደዱበትን ወይም የምትናደዱባትን አንድ ሰው

አስታውሱ፡፡

2.ለምን እንደምትጠሏት/እንደምትጠሉት አስቡና

ምክንያታችሁን አስቀምጡ፡፡

3. እናንተ ብትሆኑ ምን ታደርጉ ነበር?

4. ከእናንተ ሃሳብ/ድርጊት የሷ/የሱ የሚለየው

በምንድን ነው?

5.ድጋሜ ስለሷ/ሱ አስቡ፡፡

ሁለተኛ፤ የስሜት እድገት ሲሆን ይህም የሌሎችን

ሁኔታና ችግር ያገናዘበ የሃዘኔታ ወይም የርህራሄ

ስሜት ማዳበር ማለት ነው፡፡የሌሎችን ሁኔታ ወይም

ችግር ማወቅ ወይም ማገናዘብ ብቻ ትርጉም ስሌለለው

Page 75: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

75

ከራሳችን ፍላጎት በመነሳት ልናዝንላቸውና ፍቅር

ልናሳያቸው ይገባል፡፡

ሶስተኛ፤ የማህበራዊ እድገት ሲሆን ከሰዎች ጋር

ያለንን ግንኙነትና ቀረቤታ የሚያመላክት ነው፡፡ስለ

ሰዎች በትክክለኛ መንገድ ለማሰብና ሁኔታዎችን

ተረድቶ ጥሩ ግንኙነት ለመፍጠር ከሰዎች ጋር ያለን

የግንኙነትና የመግባባት ክህሎት የዳበረ መሆን

አለበት፡፡

ስለዚህ ስለ ሌሎች በትክክለኛ መንገድ ለማሰብና ጥሩ

ግንኙነት ለመፍጠር ነገሮችን ባግባቡ ማመዛዘንና

ሰዎች ያሉበትን ሁኔታ መገንዘብና ማሰላሰል፤ለሰዎች

ሰብዓዊና ወንድማዊ/እህታዊ ስሜትና ክብር ማሳየት

እንዲሁም በግልፅነትና በመደማመጥ መግባባት

ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሲሆን ስለ ሌሎች ማሰብ

Page 76: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

76

(empathy) የምንለውን ትልቅ የህይወት መርህ

ወይም እሴት ተላበስን ማለት ነው፡፡

በእያንዳንዱ ድርጊታችንና በሰዎች ላይ በምንፈፅመው

ወይም በምናስበው ድርጊት ሁሉ በቅድሚያ ስለ ጉዳዩ

ማንሰላሰል ያስፈልጋል፡፡

ስለ ሌሎች የሚያስብ ሰው በማንም ላይ አያሾፍም፤

ማንንም አይሳደበም፤ያለ አሳማኝ ምክንያት አይርቅም፤

የሰዎችን ችግር የመረዳት የአዕምሮ፤የስሜትና

ማህበራዊ ችሎታ አለው፤ለመተቸት፣ ለማማት ወይም

ለማንሾካሾክ አይቸኩልም።

Page 77: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

77

መልመጃ 9

1. አይ ቪ በደማቸው ውስጥ ባለባቸው ሰወች

ወይም በቤተሰባቸው ወይም በልጆቻቸው ላይ ሰራን

/አሰብን ያላችሁት መጥፎ ነገር ካለ ለማስታወስ

ሞክሩ፡፡

2. ለምን ያን ስህተት እንደሰራችሁ ምክንያታችሁን

አስታውሱ፡፡

3. አሁን ስለዛ ስህተታችሁ ምን ይሰማችኋል?

4. ከአሁን በኋላ ተመሳሳይ ስህተት ላለመድገም

ምን አሰባችሁ?

5. ወላጆቻቸውን ስላጡና ለችግር ስለተጋለጡ

ህፃናት አስባችሁ ታውቃላችሁ?

6. ወላጆቻቸውን ያጡና ለችግር የተጋለጡ

ህፃናትን በችግራቸው ዙሪያ ቀርባችሁ

አወያይታችኋቸው ታውቃላችሁ?

Page 78: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

78

7. ስለሌሎች በማሰብ ዙሪያ ከጓደኞቻችሁ ጋር

ተወያዩ፤ማንኛችሁ የተሻለ ስለሌሎች ማሰብ

እንደምትችሉ ማስረጃ እያቀረባችሁ ተነጋገሩ፤

ለቀጣይ ምን ማድረግ እንዳለባችሁ ተወያዩ፡፡

Page 79: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

79

መገለልና መድልኦ

መገልና መድልኦ ኤች አይ ቪ በደም ውስጥ መኖሩን

ወይም በኤድስ መያዝን ተከትሎ ቫይረሱ በደማቸው

ውስጥ ባለባቸው እና በቅርብ ዘመዶቻቸው ላይ

የሚመጣ ዝቅ አድርጎ የማየት ሁኔታ ነው።

ይህ ሁኔታ የሚጀምረው በቂ ያልሆነ ወይም የተሳሳተ

መረጃን ተከትሎ እያደገ በሚመጣ ምክንያት የለሽ

ወይም አሉባልታ-ተኮር አስተሳሰብ (Sterotype) ነው።

ይህ አስተሳሰብ በጊዜና በሌሎች ምክንያቶች እየጠነከረ

ሲሄድ በበቂ መረጃ እንኳን ለመቀየር አስቸጋሪ ወደሆነ

የዋልታ አዝማሚነት አስተሳሰብ (Prejudice)

ይቀየራል።

Page 80: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

80

መገለልና መድልኦ ተግባራዊ ጫናዎች ሲሆኑ

የተለያየ ቅርፅና ይዘት ሊኖራቸው ይችላል።

መገለል ኤች አይ ቪ በደማቸው ውስጥ ያለባቸውን

እንዲሁም ከነሱ ጋር ቅርበት ያላቸውን ሰዎች

የማራቅ ወይም የመራቅ ተግባር በመፈፀም በተለያዩ

ማህበራዊ ሁነቶች ውስጥ እንዳይሳተፉ የሚገደዱበት

ወይም የሚዳረጉበት ነው።

መድልኦ ደግሞ ኤች አይ ቪ በደማቸው ውስጥ

ባለባቸውና ለነሱ ቅርብ በሆኑ ሰዎች ላይ የሚፈፀም

የእኩል ተጠቃሚነታቸውን የመጋፋትና

ከአገልግሎቶች የመገደብ ኢ-ፍትሃዊ ሁኔታ ነው።

Page 81: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

81

የመገለልና መድልኦ ዓይነቶች

መገለል እና መድልኦ የሚከተሉትን ዋና ዋና ቅርፆች

ይዞ ሊከሰት ይችላል፡-

1. አካላዊ መገለልና መድልኦ፡- ይህ በአካል

የመራቅ፣ አለመቅረብ፣ ከንክኪ መሸሽ፣ አልጋ

መለየት፣ ወዘተ. የሚያጠቃልል ሲሆን በሰዎቹ

ላይ የሚያሳድረው ስነ-ልቦናዊ ተፅዕኖ እጅግ የጎላ

ነው።

ኤች አይ ቪ ከሚተላለፍባቸው መንገዶች ውጭ

ኤች አይ ቪ ይተላለፋል ብሎ መስጋትና

ስጋትንም በተግባር መግለጽ ከሳይንሳዊ

አስተሳሰብ የራቀ ነው።

Page 82: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

82

ይህ አስተሳሰብ በአንድ በኩል መተላለፊያ

መንገዶቹን በደንብ አጥርቶ ካለማወቅ በሌላ

በኩል ደግሞ በከፊል ህሊና (Sub-concsious)

ምክንያት በሚፈጠር ከምክንያት የራቀ ፍራቻ

የሚመጣ ነው።

2. ማህበራዊ መገለልና መድልኦ፡- ይህ ከማህበራዊ

ተሳትፎ፣ ከማንነትና አካባቢያዊ ሚና የማራቅና

እንደ እንግዳ ደጋግሞ በሰውየው ላይ የማፍጠጥ

ሁኔታ ነው።

በማንኛውም ማህበራዊ ህይወታችን ውስጥ

በእኩልነትና በምክንያታዊነት ላይ ያልተመሰረተና

በፍርሃትና በአሉባልታ የታጠረ ማህበራዊ

ስርዓት ለማንኛችንም የሚጠቅም አይደለም።

Page 83: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

83

3. የቃላት መገለልና መድልኦ፡- ይህ ሁኔታ

በዋናነት ቫይረሱን ከሃጢያትና ከሞራል ህግ

ጥሰት ጋር በማዘመድ የሚመጣ ሲሆን በሰዎቹ

ላይ ማሾፍን፣ መውቀስን፣ ማንሾካሾክን፣

ስድብን፣ ወዘተ. የሚያጠቃልል ነው።

4. ተቋማዊ መገለልና መድልኦ፡- ይህ በተለያዩ

ማህበራዊ፣ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ

ተቋማት በኩል የሚስተዋል ፍትሃዊና ሰብዓዊ

ያልሆነ ድርጊትና እርምጃን የሚያጠቃልል ነው።

ተቋማዊ መገለልና መድልኦ በት/ቤቶች፣ በጤና

ተቋማት፣ በስራ ቦታዎች ወዘተ. ተደጋግሞ

የሚታይ ሲሆን በዋናነት በእኩልነት መብት ላይ

ያነጣጠረና አድሏዊ አሰራርን የሚያመለክት

ነው።

Page 84: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

84

የመገለልና መድልኦ ክስተት የሚነባበርባቸው

ሂደቶችና ሁኔታዎች መኖራቸው ጉዳዩን የበለጠ

አሳሳቢ ያደርገዋል።

ከፆታ፣ ከዕፅና አልኮል ሱሰኝነት፣ ከዝሙት

አዳሪነት፣ ከአካል ጉዳተኝነት፣ ከዘውግ ማንነት

ወዘተ. ጋር በተያያዘ ብዙ ሰዎች የድርብርብ

መገለልና መድልኦ ዒላማዎች ይሆናሉ።

ቫይረሱን ከተለያዩ ማንነቶች ጋር በማያያዝ

የማንነት ውጤት አድርጎ መመልከት ሰፊ ስነ-

ልቦናዊ ጉዳትን የሚያስከትል ከመሆኑ ባሻገር

ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ለሌለባቸውም

የማዘናጊያ ደወል ይሆናል። ከዚህ በተጨማሪም

ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ላለባቸው ነገር ግን

የምርመራ ውጤታቸውን በግልፅ ላላሳወቁ ሰዎች

Page 85: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

85

ውጤታቸውን እንዲሸሽጉ መልዕክት የሚሰጥና

በዚህም ምክንያት የበሽታውን ስርጭት

ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት የሚያዳክም

ነው።

Page 86: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

86

መልመጃ 10

1. መገለል ማለት ምን ማለት ነው?

2. መድልኦ ማለት ምን ማለት ነው?

3. በአካባቢያችሁ ወይም በት/ቤት የታዘባችሁት

መገለልና መድልኦ ካለ አብራሩ፡፡

4. የመገለልና መድልኦ ዓይነቶችን ዘርዝሩ፡፡

Page 87: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

87

የመገለልና መድልኦ ሂደት

ኤች አይ ቪ ከራስ ቁጥጥር ውጭ በሆነ መንገድ ሊተላለፍ ይችላል የሚል ስጋት

ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ የሚኖሩትን መፈረጅ

ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ያለባቸውን ሰዎች ዝቅ አድርጎ ማየት፤ ማግለል

የተገለሉ ሰዎችን የተለያዩ አገልግሎቶች እንዳያገኙ መከልከል፤ በእኩልነት የመጠቀም መብታቸው ላይ መድልኦ መፈፀም

Page 88: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

88

መገለል፣ መድልኦ እና ህፃናት

ህፃንነት

በህፃናት መብቶች ኮንቬንሽንና በአገራችን ህግ መሰረት

ህፃን ማለት ማንኛውም ዕድሜው ከ18 ዓመት በታች

የሆነ ሰው እንደሆነ ተቀምጧል።

በሰው ልጅ እድገትና የባህርይ ጥናቶች መሰረት ከ1-11

ዓመት ያለው ዕድሜ ባብዛኛው የህፃንነት ጊዜ እንደሆነና

ከ12-18 ዓመት የሚሞላቸው ደግሞ በጉርምስና

(Adolescence) ደረጃ ውስጥ እንደሚጠቃለሉ

ይታመናል። ያም ሆኖ የቆይታ ዕድሜ (Chronological

Age) ብቻ የዕድገት ደረጃን ለመወሰን እንደማያስችል

ምሁራን ያብራራሉ። ትክክለኛ የዕድገት ደረጃ

የሁለንተናዊ ለውጦች ድምርና ህብር ውጤት ነው።

Page 89: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

89

ኤች አይ ቪ እና ሕፃናት

በኤች አይ ቪ ምክንያት በርካታ ህጻናት ያለ አሳዳጊና

ተንከባካቢ ለተለያዩ ችግሮች እየተጋለጡ ይገኛሉ።

ወላጆቻቸውን በሞት ያጡ፣ ወይም የታመሙባቸውና

ለአደጋ የተጋለጡ ህፃናት ከሚደርስባቸው ሁለንተናዊ

ችግር ባሻገር የመገለልና መድልኦው ችግር ተካፋይ

ናቸው።

ህፃናት በአካል፣ በአዕምሮ፣ በስሜት፣ በኢኮኖሚ፣

ወዘተ. ሙሉ ለሙሉ ራሳቸውን ያልቻሉ በመሆናቸው

ችግሮችን ለመቋቋም እጅግ ይቸገራሉ።

ስለዚህም እያንዳንዳችን ህፃናቱን ለመታደግና በፍቅርና

በእንክብካቤ ለመጠበቅ ያደረግነውን ግለሰባዊም ሆነ

Page 90: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

90

ማህበራዊ አስተዋፅኦ መፈተሽና ሀገራዊ ኃላፊነታችንን

በአግባቡ መወጣት ይጠበቅብናል።

በህፃናት ላይ የሚደርስን ማናቸውም ተፅዕኖና ከኤች

አይ ቪ ጋር በተያያዘ የሚደርስባቸውን መገለልና

መድልኦ ለመታገል ህፃናት ራሳቸው ትልቁን ድርሻ

መውሰድ አለባቸው።

ወላጆቻቸውን ያጡና ለችግር የተጋለጡ ህፃናት

በት/ቤትና በአካባቢያቸው ንቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸውና

ትምህርታቸውንም በአግባቡ እንዲከታተሉ ከመገለልና

መድልኦ የፀዳ በፍቅርና እንክብካቤ የተሞላ ጤናማ

ግንኙነትና ቀረቤታ ልንፈጥርና ፍቅራችንን ልናሳያቸው

ይገባል።

Page 91: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

91

በተለይም በጉርምስና ዘመን ውስጥ ሊጠቃለሉ የሚችሉ

ህፃናት እርስ በእርሳቸው እንዲማማሩና እንዲተራረሙ

ያስፈልጋል።

የተለያዩ ክበባትን በማዋቀር፣ የህፃናት ፓርላማን

በማጠናከር፣ የውይይት አጀንዳዎችን በማዘጋጀትና

በመወያየት የጋራ የሆነ መብታቸውን በእኩልነትና

በመተባበር መንፈስ ማስከበር ያስፈልጋል።

እርስ በእርስ በሚፈጠር ማህበራዊ ግንኙነትም ስህተት

የሰራውን ሰው ለይቶ የማረምና የመማማር ባህል

ማዳበር ያስፈልጋል።

Page 92: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

92

በአጠቃላይ ህፃናቱ እንዳይገለሉና መድልኦ

እንዳይፈፀምባቸው ብሎም በሁለንተናዊ ተሳትፏቸው

ንቁ እንዲሆኑ እያንዳንዳችን የበኩላችንን ኃላፊነት

መወጣት ይገባናል።

Page 93: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

93

የህፃናት መብቶች ኮንቬንሽን አንቀፅ 2

1. የኮንቬንሽኑ አባል አገሮች በግዛታቸው ክልል የሚገኝ እያንዳንዱ

ህፃን በራሱ ወይም በወላጆቹ ወይም በአሳዳጊው ዘር፣ ቀለም፣

ፆታ፣ ቋንቋ፣ ኃይማኖት፣ የፖለቲካ ወይም ሌላ አስተሳሰብ፣

ዜግነት፣ ነገድ፣ ወይም የትውልድ ስፍራ፣ ሀብት፣ የአካልና

የአዕምሮ ጉድለት፣ ትውልድ ወይም ሌላ የማህበራዊ ኑሮ ደረጃ

ምክንያት ምንም ዓይነት መድልኦ ሳይደረግበት የመብቱ

ተጠቃሚ እንዲሆን በኮንቬንሽኑ የተረጋገጡትን መብቶች

ያከብራሉ፤ ተግባራዊነታቸውንም ያረጋግጣሉ

2. የኮንቬንሽኑ አባል አገሮች ህፃኑ በወላጆቹ በአሳዳጊዎቹ፣ ወይም

በቤተሰቦቹ የማህበራዊ ኑሮ ደረጃ፣ ተግባሮች፣ አመለካከት፣

ወይም እምነት ምክንያት መድልኦ እንዳይደረግበትና አላግባብ

ቅጣት እንዳይደርስበት ለማረጋገጥ ተገቢ የሆኑ እርምጃዎችን

ይወስዳሉ።

Page 94: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

94

መልመጃ 11

1. በህፃናት መብቶች ኮንቬንሽንና በአገራችን ህግ

መሰረት ህፃን ማለት ምን ማለት ነው?

2. ጉርምስና ምንድነው?

3. ከኤች አይ ቪ ጋር በተያያዘ በህፃናት ላይ

የሚደርሰውን መገለልና መድልኦ ለማስቆም

ከመምህራን፣ ከወላጆችና ከተማሪዎች ምን

ይጠበቃል?

Page 95: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

95

የመገለልና መድልኦ ውጤቶች

መገለልና መድልኦ ሰፊና አስከፊ ውጤቶች

የሚያስከትል ሲሆን ኤች አይ ቪን ለመከላከል

በሚደረገው ጥረት እጅግ ትልቅ መሰናክል ነው።

በመገለል ተፅዕኖ ላይ ትኩረት እስካላደረግን ድረስ

የምናደርገው ጥረት ሁሉ ስኬት ሊኖረው አይችልም።

በታሪካችን ከተከሰቱት በሽታዎች ሁሉ ከመገለል ጋር

በመቆራኘት አንደኛው ኤድስ ሳይሆን አይቀርም።

-ኤድዊን ካሜሮን

ኤች አይ ቪ ከተከሰተበት ጊዜ ጀምሮ ለመከላከል

በሚደረገው ጥረት ውስጥ መገለል፣ መድልኦ እና

የተዛባ ስርዓተ-ፆታ ዋናዎቹ መሰናክሎች ናቸው።

-ፒተር ፓዮት

Page 96: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

96

መገለልና መድልኦ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ያለባቸው

ሰዎች ለመከላከል ሂደቱ የሚጫወቱትን ሚና

በማመናመን የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት

የሚደረገውን ጥረት እያደናቀፈ ይገኛል።

የኤች አይ ቪ ምርመራን ተከትሎ የሚመጣን መገለልና

መድልኦ በመፍራት ብዙ ሰዎች የበጎ ፈቃድ የምርመራ

አገልግሎት እንዳያገኙ ምክንያት ከመሆኑ በተጨማሪ

ተመርምረው ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ እንዳለ ያወቁ

ሰዎች በመንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች

ግለሰቦችና ማህበረሰብ አቀፍ-ተቋማት (ዕድሮች፣

ጀምያዎች፣ ወዘተ.) የሚሰጠውን የህክምናና ሌሎች

ድጋፍና እንክብካቤ አገልግሎቶች እንዳይጠቀሙ እያደረገ

ይገኛል።

Page 97: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

97

ህፃናት በመገለልና መድልኦ እጅግ ከሚጎዱ የማህበረሰብ

ክፍሎች ዋነኞቹ ሲሆኑ በአዕምሮ፣ በስነ-ልቦናና

በማህበራዊ ክሂላቸው ውሱንነት ምክንያትም ተፅዕኖው

የጎላ ይሆናል።

ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ያለ እና ወላጆቻቸውን ያጡ/

በህመም ምክንያት ከወላጆቻቸው አስፈላጊውን

እንክብካቤ ማግኘት ያልቻሉ/ ህፃናት በራሳቸውም ሆነ

በቤተሰባቸው ላይ በሚደርሰው መገለልና መድልኦ

ምክንያት ለሰፊ ስነ-ልቦናዊ ጉዳት እየተዳረጉ ይገኛሉ።

በአገራችን የሚገኙ ከአስራ አምስት በላይ የሚሆኑ

ወላጆቻቸውን ያጡና ለችግር የተጋለጡ ህፃናት ዓይነት

(ወላጆቻቸውን ያጡ ህፃናት፣ የቤተሰብ አስተዳዳሪ የሆኑ

ህፃናት፣ በዝሙት አዳሪነት የተሰማሩ ህፃናት፣ ወዘተ.)

እንዲበራከቱና የችግሩ መጠን በስፋትም በጥልቀትም

Page 98: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

98

እንዲጨምር ኤች አይ ቪ ትልቅ ምክንያት ሆኗል።

በመሆኑም በዚህ የችግሩ ልኬት መሰረት ከኤች አይ ቪ

ጋር በተያያዘ የሚፈፀመው መገለልና መድልኦ

መንሰራፋቱ እያንዳንዳችን በጥልቅ ልናስብበት የሚገባን

አንገብጋቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ያመለክታል።

Page 99: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

99

መልመጃ 12

1. መገለልና መድልኦ ምን ውጤት ያስከትላል?

2. በመገለልና መድልኦ ምክንያት ትምህርት

ያቋረጡ፣ ብቸኝነት የሚያበዙ፣ የሚተክዙ

ህፃናት አይታችሁ ተውቃላችሁ?

3. መገለልና መድልኦን መግታት ኤች አይ ቪን

ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ውስጥ ምን

አስተዋፅኦ ይኖረዋል ብላችሁ ታስባላችሁ?

4. በመገለልና መድልኦ ዙሪያ ከአሁን በፊት

የተማራችሁት፣ ያነበባችሁት ወይም በሚዲያ

ያዳመጣችሁት ነገር ካለ በማስታዎሻ

ደብተራችሁ በማስፈር ከጓደኞቻችሁ ጋር

ተወያዩባቸው።

Page 100: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

100

5. በአካባቢያችሁ፣ በት/ቤት ወይም በሌላ ቦታ

የታዘባችሁትን እያነሳችሁ መገለልና መድልኦን

እንዴት መግታት እንዳለባችሁ ተወያዩ።

Page 101: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

101

ስለ ኪቱ ያላችሁን አስተያየት፡

በስልክ ቁ. 0918-74-35-85

በኢሜል አድራሻ [email protected]

ፖ.ሳ.ቁ 970

ወይም

በስልክ ቁ. O58-220-58-89

በኢሜል አድራሻ [email protected]

ፖ.ሳ.ቁ 877

አድርሱን።

Page 102: Ossa-bcc Kit Final

የባህርይ ለውጥ መግባቢያ ኪት

102